በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይሖዋ የሚያስተምረን ለጥቅማችን ነው

ይሖዋ የሚያስተምረን ለጥቅማችን ነው

ምዕራፍ ዘጠኝ

ይሖዋ የሚያስተምረን ለጥቅማችን ነው

ኢሳይያስ 48:​1-22

1. ብልህ የሆኑ ሰዎች ለይሖዋ ቃል ምን አመለካከት አላቸው?

ብልህ የሆኑ ሰዎች ይሖዋ በሚናገርበት ጊዜ ቃሉን በታላቅ አክብሮት በማዳመጥ ተግባራዊ ያደርጋሉ። ይሖዋ ደህንነታችን በእጅጉ ስለሚያሳስበው ማንኛውንም መመሪያ የሚሰጠን ለእኛው ጥቅም ነው። ለምሳሌ ያህል ይሖዋ በጥንት ዘመን ለነበሩት የቃል ኪዳን ሕዝቡ “ትእዛዜን ብትሰማ ኖሮ” ሲል የተናገራቸው ቃላት ምንኛ ልብ የሚነኩ ናቸው! (ኢሳይያስ 48:​18) ይሖዋ የሚሰጠው ትምህርት ምን ያህል ጠቃሚ እንደሆነ በተግባር የታየ መሆኑን ማወቃችን የሚናገረውን ቃል እንድንሰማና መመሪያውን እንድንከተል ሊገፋፋን ይገባል። ቀደም ባሉት ዘመናት ስለተፈጸመው ትንቢት የሚናገረው ዘገባ ይሖዋ የገባውን ቃል ለመፈጸም የማያወላውል መሆኑን በሚገባ ያረጋግጥልናል።

2. በኢሳይያስ 48 ላይ የሰፈሩት ቃላት የተጻፉት ለእነማን ነው? እነማንስ ከእነዚህ ቃላት ጥቅም ማግኘት ይችላሉ?

2 በኢሳይያስ መጽሐፍ 48ኛ ምዕራፍ ላይ የሰፈሩት ቃላት የተጻፉት በባቢሎን ለሚማረኩት አይሁዳውያን እንደሆነ የታወቀ ነው። ይሁንና እነዚህ ቃላት በአሁኑ ጊዜ ያሉ ክርስቲያኖችም ሊያጤኑት የሚገባ መልእክት ይዘዋል። መጽሐፍ ቅዱስ በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 47 ላይ ስለ ባቢሎን አወዳደቅ ተንብዮአል። አሁን ደግሞ ይሖዋ በዚያች ከተማ ለሚኖሩት አይሁዳውያን ግዞተኞች ሊያደርግ ያሰበውን ነገር ይገልጻል። ይሖዋ የመረጣቸው ሕዝቦቹ ግብዞች መሆናቸውና የገባውን ቃል ለማመን አሻፈረን ማለታቸው በእጅጉ አሳዝኖታል። ያም ሆኖ ለእነርሱው ጥቅም በማሰብ ያስተምራቸዋል። አይሁዳውያን በመከራ የሚፈተኑበት ጊዜ እንደሚመጣና ታማኝ ሆነው የተገኙ ቀሪዎች ወደ ትውልድ አገራቸው እንደሚመለሱ አስቀድሞ ተናገረ።

3. የይሁዳ አምልኮ ምን ጉድለት ይታይበት ነበር?

3 የይሖዋ ሕዝቦች ከንጹሕ አምልኮ ምንኛ ርቀው ነበር! ኢሳይያስ በምዕራፉ መግቢያ ላይ የተናገራቸው ቃላት ቆም ብለን እንድናስብ የሚያደርጉ ናቸው:- “እናንተ በእስራኤል ስም የተጠራችሁ ከይሁዳም ውኆች የወጣችሁ፣ በእግዚአብሔር ስም የምትምሉ፣ በእውነት ሳይሆን በጽድቅም ሳይሆን የእስራኤልን አምላክ የምትጠሩ፣ በቅድስት ከተማ ስም የተጠራችሁ፣ ስሙም የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር በሚባል በእስራኤል አምላክ የምትደገፉ፣ የያዕቆብ ቤት ሆይ፣ ይህን ስሙ።” (ኢሳይያስ 48:1, 2) እንዴት ያለ ግብዝነት ነው! ‘በይሖዋ ስም በሚምሉበት’ ጊዜ የአምላክን ስም የሚጠሩት እንዲያው ለይስሙላ ነበር። (ሶፎንያስ 1:​5) አይሁዳውያን ተማርከው ወደ ባቢሎን ከመወሰዳቸው በፊት ‘በቅድስቲቷ ከተማ’ በኢየሩሳሌም ይሖዋን ያመልኩ ነበር። ሆኖም አምልኳቸው ከልብ የመነጨ አልነበረም። ልባቸው ከአምላክ ርቆ የነበረ ሲሆን የአምልኮ ሥርዓታቸውም ‘በእውነትና በጽድቅ’ ላይ የተመሠረተ አልነበረም። እንደ አብርሃም፣ ይስሐቅ ወይም ያዕቆብ ዓይነት እምነት አልነበራቸውም።​—⁠ሚልክያስ 3:​7

4. ይሖዋን የሚያስደስተው ምን ዓይነት አምልኮ ነው?

4 ይሖዋ የተናገራቸው ቃላት አምልኳችን እንዲያው ለስሙ የሚደረግ መሆን እንደሌለበት ያሳስቡናል። ከዚህ ይልቅ ከልብ የመነጨ መሆን ይኖርበታል። ‘ለአምላክ ያደርን’ መሆናችንን የምናሳየው ለታይታ የሚደረግ ብሎም ሌሎችን ለማስደሰት ወይም የሰዎችን ትኩረት ለመሳብ ተብሎ የሚከናወን አገልግሎት በማቅረብ አይደለም። (2 ጴጥሮስ 3:​11 NW ) አንድ ሰው ራሱን ክርስቲያን ብሎ መጥራቱ ብቻ አምልኮው በአምላክ ፊት ተቀባይነት እንዲያገኝ አያደርገውም። (2 ጢሞቴዎስ 3:​5) ይሖዋ መኖሩን አምኖ መቀበል በጣም አስፈላጊ ቢሆንም ይህ ብቻውን በቂ አይደለም። ይሖዋ ለእርሱ ባለን ጥልቅ ፍቅርና አድናቆት ተገፋፍተን በሙሉ ነፍሳችን እንድናመልከው ይፈልጋል።​—⁠ቆላስይስ 3:​23

አዳዲስ ነገሮችን አስቀድሞ መናገር

5. ‘የቀድሞው ነገር’ ከተባሉት መካከል አንዳንዶቹ ምንድን ናቸው?

5 በባቢሎን ያሉት አይሁዳውያን ቀደም ባሉት ዘመናት የተፈጸ​ሙትን ነገሮች ማስታወስ ሳያስፈልጋቸው አልቀረም። በመሆኑም ይሖዋ እውነተኛ ትንቢት የሚናገር አምላክ መሆኑን ዳግመኛ አሳስቧቸዋል:- “የቀድሞውን ነገር ከጥንት ተናግሬአለሁ፣ ከአፌም ወጥቶአል አሳይቼውማለሁ፤ ድንገት አድርጌዋለሁ ተፈጽሞማል።” (ኢሳይያስ 48:3) ‘የቀድሞው ነገር’ ከተባሉት መካከል አምላክ ቀደም ባሉት ዘመናት እስራኤላውያንን ከግብጽ ነፃ በማውጣትና ተስፋይቱን ምድር ርስት አድርጎ በመስጠት ያከናወናቸው ነገሮች ይገኙበታል። (ዘፍጥረት 13:​14, 15፤ 15:​13, 14) እንዲህ ያሉት ትንቢቶች ከአምላክ አፍ የወጡና መለኮታዊ ምንጭ ያላቸው ናቸው። አምላክ ያወጣውን ሥርዓት ሰዎች እንዲሰሙት ያደረገ ሲሆን እነሱም የሰሙት ነገር እንዲታዘዙ ሊገፋፋቸው ይገባል። (ዘዳግም 28:​15) ይሖዋ አስቀድሞ የተናገረውን ነገር ለመፈጸም ድንገት እርምጃ ይወስዳል። ሁሉን ማድረግ የሚችል አምላክ መሆኑ ዓላማው ፍጻሜውን ማግኘቱ እንደማይቀር ዋስትና ይሆናል።​—⁠ኢያሱ 21:​45፤ 23:​14

6. አይሁዳውያን ምን ያህል “እልከኞችና ዐመፀኞች” ሆነው ነበር?

6 የይሖዋ ሕዝቦች “እልከኞችና ዐመፀኞች” ሆነው ነበር። (መዝሙር 78:​8 አ.መ.ት ) በመሆኑም ይሖዋ እንዲህ ሲል በግልጽ ነግሯቸዋል:- “አንተ እልከኛ፣ አንገትህም የብረት ጅማት ግምባርህም ናስ [ነው]።” (ኢሳይያስ 48:​4) አይሁዳውያን እንደ ብረት ድርቅ ያሉ ግትሮች ነበሩ። ይሖዋ አንዳንድ ሁኔታዎች ከመፈጸማቸው በፊት በመንፈሱ አማካኝነት ለመግለጥ የተነሳሳበት አንዱ ምክንያት ይህ ነው። አለዚያ ሕዝቡ ይሖዋ ያከናወናቸውን ነገሮች በተመለከተ እንዲህ ሊሉ ይችላሉ:- “ጣዖቴ ይህን አድርጎአል፣ የተቀረጸው ምስሌና ቀልጦ የተሠራው ምስሌ ይህን አዘዙኝ።” (ኢሳይያስ 48:5) ይሖዋ እየተናገረው ያለው ነገር በከዳተኞቹ አይሁዶች ላይ ለውጥ ያመጣ ይሆን? አምላክ እንዲህ ይላቸዋል:- “ሰምተሃል፤ ይህን ሁሉ ተመልከት፤ እናንተም የምትናገሩት አይደላችሁምን? የተሰወሩትን ያላወቅሃቸውንም አዲሶች ነገሮችን ከዚህ ጀምሬ አሳይቼሃለሁ። እነርሱም አሁን እንጂ ከጥንት አልተፈጠሩም፤ አንተም:- እነሆ፣ አውቄአቸዋለሁ እንዳትል ከዛሬ በፊት አልሰማሃቸውም።”​—⁠ኢሳይያስ 48:6, 7

7. በግዞት ያሉት አይሁዶች ሊክዱት የማይችሉት ነገር ምንድን ነው? በእምነት ሊጠብቁት የሚችሉትስ ነገር ምንድን ነው?

7 ኢሳይያስ ስለ ባቢሎን መውደቅ የሚናገረውን ትንቢት የጻፈው ከብዙ ዘመናት አስቀድሞ ነው። አሁን በባቢሎን በግዞት ያሉት አይሁዶች የዚህን ትንቢት ፍጻሜ በጥሞና እንዲያሰላስሉ በትንቢት ታዝዘዋል። ይሖዋ በትክክል ፍጻሜያቸውን የሚያገኙ ትንቢቶችን የሚናገር አምላክ መሆኑን ሊክዱ ይችላሉን? ከዚህም በተጨማሪ የይሁዳ ነዋሪዎች ይሖዋ የእውነት አምላክ መሆኑን ያዩና የሰሙ በመሆኑ ይህን እውነት ለሌሎች ማስታወቅ አይገባቸውምን? ይሖዋ በመንፈሱ የገለጠው ቃል ቂሮስ በባቢሎን ላይ የሚቀዳጀውን ድልና አይሁዳውያን የሚያገኙትን ነፃነት የመሳሰሉ ገና ያልተፈጸሙ አዳዲስ ነገሮችንም ይዞ ነበር። (ኢሳይያስ 48:​14-16) እንዲህ ያሉት አስገራሚና አስደንጋጭ ክስተቶች ባልታሰበና ባልተጠበቀ ሁኔታ የሚፈጸሙ ናቸው። በዓለም ላይ ያሉት ወቅታዊ ሁኔታዎች ወዴት እንደሚያመሩ በመገመት ብቻ እነዚህን ክንውኖች መተንበይ የሚችል አልነበረም። በራሳቸው የተከሰቱ ያህል በድንገት ብቅ ይላሉ። እነዚህ ክስተቶች እንዲፈጸሙ የሚያደርገው ማን ነው? ይሖዋ 200 ዓመት ገደማ አስቀድሞ እነዚህ ነገሮች እንደሚከሰቱ ተንብዮ የነበረ በመሆኑ እንዲፈጸሙ የሚያደርገውም ማን እንደሆነ ግልጽ ነው።

8. ዛሬ ያሉ ክርስቲያኖች የትኞቹን አዳዲስ ነገሮች በተስፋ ይጠባበቃሉ? በይሖዋ ትንቢታዊ ቃል ላይ ሙሉ በሙሉ የሚተማመኑትስ ለምንድን ነው?

8 በተጨማሪም ይሖዋ ቃሉን የሚፈጽመው ራሱ ባቀደው ጊዜ ነው። ቀደም ባሉት ጊዜያት የተፈጸሙት ትንቢቶች ለጥንቶቹ አይሁዳውያን ብቻ ሳይሆን ዛሬ ላሉት ክርስቲያኖችም ይሖዋ እውነተኛ አምላክ መሆኑን የሚያሳዩ ጥሩ ማረጋገጫዎች ናቸው። ‘የቀድሞው ነገር’ ማለትም ቀደም ባሉት ዘመናት ፍጻሜያቸውን ስላገኙት በርካታ ትንቢቶች የሚናገረው ዘገባ ይሖዋ ቃል የገባቸው አዳዲስ ነገሮችም እንደሚፈጸሙ ዋስትና ይሆነናል። ይሖዋ በቅርቡ ‘ታላቅ መከራ’ እንደሚመጣ፣ “እጅግ ብዙ ሰዎች” መከራውን በሕይወት እንደሚያልፉና “አዲስ ምድር” እንደሚመጣ የገባው ቃልም ሆነ ሌሎቹ ተስፋዎች ፍጻሜያቸውን እንደሚያገኙ እርግጠኞች መሆን እንችላለን። (ራእይ 7:​9, 14, 15፤ 21:​4, 5፤ 2 ጴጥሮስ 3:​13) በዘመናችን ያሉ ቅን ልብ ያላቸው ሰዎች ይህን ዋስትና ማግኘታቸው ስለ ይሖዋ በቅንዓት እንዲናገሩ ይገፋፋቸዋል። “በታላቅ ጉባኤ ጽድቅን አወራሁ፤ እነሆ፣ ከንፈሮቼን አልከለክልም” በማለት የተናገረው መዝሙራዊ የተሰማው ዓይነት ስሜት ይሰማቸዋል።​—⁠መዝሙር 40:9

ይሖዋ ራሱን ይገዛል

9. የእስራኤል ሕዝብ ‘ከማኅፀን ጀምሮ ተላላፊ’ የነበረው እንዴት ነው?

9 አይሁዳውያን ይሖዋ በተናገራቸው ትንቢቶች አለማመናቸው ማስጠንቀቂያውን እንዳይሰሙ እንቅፋት ሆኖባቸዋል። እንደሚከተለው ሲል የተናገራቸውም በዚህ ምክንያት ነው:- “አልሰማህም፣ አላወቅህም፣ ጆሮህ ከጥንት አልተከፈተችም፤ አንተ ፈጽሞ ወንጀለኛ [“አታላይ፣” አ.መ.ት ] እንደ ሆንህ ከማኅፀንም ጀምረህ ተላላፊ ተብለህ እንደ ተጠራህ አውቄአለሁና።” (ኢሳይያስ 48:8) ይሁዳ ይሖዋ የሚናገረውን የምሥራች ላለመስማት ጆሮዋን ደፍና ነበር። (ኢሳይያስ 29:​10) የአምላክ የቃል ኪዳን ሕዝቦች ያደርጉት የነበረው ነገር የእስራኤል ብሔር ‘ከማኅፀን ጀምሮ ተላላፊ’ እንደነበረ የሚያሳይ ነው። የእስራኤል ሕዝብ ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ በኖረበት ዘመን ሁሉ ያስመዘገበው ታሪክ በዓመፅ ድርጊት የተሞላ ነው። እስራኤላውያን በተደጋጋሚ ጊዜያት ሕጉን ይተላለፉ የነበረ ከመሆኑም በላይ የክህደት አባዜ የተጠናወታቸው ነበሩ።​—⁠መዝሙር 95:​10፤ ሚልክያስ 2:​11

10. ይሖዋ ራሱን የሚገታው ለምንድን ነው?

10 ታዲያ ምንም ተስፋ አልነበራቸውም ማለት ነው? እንደዚያ ማለት አይደለም። ምንም እንኳ ይሁዳ ዓመፀኛና በቃልዋ የማትገኝ አታላይ የነበረች ቢሆንም ይሖዋ ምንጊዜም ሐቀኛና ታማኝ ነው። ለታላቅ ስሙ ክብር ሲል ቁጣውን ይገታል። እንዲህ ሲል ተናገረ:- “ስለ ስሜ ቁጣዬን አዘገያለሁ፣ እንዳላጠፋህም ስለ ምስጋናዬ እታገሣለሁ።” (ኢሳይያስ 48:9) በይሖዋና በሕዝቡ መካከል እጅግ የጎላ ልዩነት አለ! እስራኤልም ሆነች ይሁዳ ለይሖዋ ታማኝ ሆነው አልተገኙም። ሆኖም ይሖዋ ለስሙ ምስጋናና ክብር የሚያመጣ እርምጃ በመውሰድ ስሙን ይቀድሳል። በዚህም ምክንያት የመረጣቸውን ሕዝቦቹን ከማጥፋት ይታቀባል።​—⁠ኢዩኤል 2:​13, 14

11. አምላክ ሕዝቡ ሙሉ በሙሉ እስኪጠፉ ድረስ ዝም ብሎ የማይመለከተው ለምንድን ነው?

11 በግዞት ካሉት አይሁዳውያን መካከል ቅን ልብ ያላቸው አንዳንድ ግለሰቦች አምላክ በሰነዘረው ወቀሳ በመባነን ትምህርቶቹን ተግባራዊ ለማድረግ ቁርጥ አቋም ይወስዳሉ። እንዲህ ላሉት ሰዎች የሚከተለው መግለጫ እጅግ አጽናኝ ይሆንላቸዋል:- “እነሆ፤ እንደ ብር ባይሆንም አንጥሬሃለሁ፤ በመከራ እቶን ፈትኜሃለሁ። ስለ ራሴ፣ ስለ ራሴ ስል አደርጋለሁ፤ ራሴን ለውርደት እንዴት አሳልፌ እሰጣለሁ? ክብሬን ለማንም አልሰጥም።” (ኢሳይያስ 48:10, 11 አ.መ.ት ) ይሖዋ በሕዝቡ ላይ እንዲደርስ የፈቀደው ‘የመከራ እቶን’ ማለትም ፈታኝ አበሳ ሕዝቡ ተፈትነው እንዲጠሩና በልባቸው ውስጥ ያለው ነገር ገሃድ እንዲወጣ አድርጓል። ከብዙ መቶ ዘመናት በፊት ሙሴ ለቀድሞ አባቶቻቸው የሚከተለውን ቃል በተናገረ ጊዜ ተመሳሳይ ሁኔታ ተፈጽሞ ነበር:- “አምላክህ እግዚአብሔር ይፈትንህ ዘንድ፣ በልብህም ያለውን . . . ያውቅ ዘንድ፣ ሊያስጨንቅህ በእነዚህ በአርባ ዓመታት በምድረ በዳ [መራህ]።” (ዘዳግም 8:2) በዚያን ጊዜ የነበሩት ሰዎች የዓመፀኝነት ዝንባሌ የነበራቸው ቢሆንም ይሖዋ ሕዝቡን አላጠፋም፤ በዚህም ጊዜ ቢሆን ሕዝቡን ሙሉ በሙሉ አያጠፋም። በዚህ መንገድ ስሙና ክብሩ እንዲጠበቅ ያደርጋል። ሕዝቡ በባቢሎናውያን እጅ ከምድረ ገጽ የሚጠፉ ከሆነ ቃል ኪዳኑን እንዳጠፈ ሊያስቆጥርበትና ስሙን ሊያስነቅፍበት ይችላል። በተጨማሪም የእስራኤል አምላክ ሕዝቡን መታደግ እንደተሳነው ተደርጎ ሊታይ ይችላል።​—⁠ሕዝቅኤል 20:​9

12. እውነተኛ ክርስቲያኖች በአንደኛው የዓለም ጦርነት ወቅት የጠሩት እንዴት ነው?

12 በዘመናችንም የይሖዋ ሕዝቦች መንጠርና መጥራት አስፈልጓቸው ነበር። በ20ኛው መቶ ዘመን መጀመሪያ ላይ በቁጥር አነስተኛ ከነበሩት የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች መካከል ብዙዎቹ አምላክን ያገለግሉ የነበረው እሱን ለማስደሰት በነበራቸው ልባዊ ፍላጎት ተገፋፍተው ቢሆንም አንዳንዶቹ ግን እውቅና ለማግኘት የሚፈልጉና መጥፎ ዝንባሌ ያላቸው ነበሩ። ይህ አነስተኛ ቡድን በፍጻሜው ዘመን በዓለም ዙሪያ እንደሚከናወን አስቀድሞ የተነገረለትን የምሥራቹን ስብከት ሥራ በግንባር ቀደምትነት ማካሄድ ከመጀመሩ በፊት መጥራት አስፈልጎት ነበር። (ማቴዎስ 24:​14) ነቢዩ ሚልክያስ ይሖዋ ወደ ቤተ መቅደሱ በሚመጣበት ጊዜ እንዲህ ያለ የማጥራት ሥራ እንደሚከናወን ተንብዮአል። (ሚልክያስ 3:​1-4) ይህ የሚልክያስ ትንቢት በ1918 ተፈጽሟል። አንደኛው የዓለም ጦርነት በከፍተኛ ደረጃ በተፋፋመበት ወቅት እውነተኛ ክርስቲያኖች ከባድ ፈተና የደረሰባቸው ሲሆን በዚህ ሳቢያ በወቅቱ የመጠበቂያ ግንብ ማኅበር ፕሬዚዳንት የነበረው ጆሴፍ ኤፍ ራዘርፎርድና ሌሎች በኃላፊነት ቦታ ላይ ይሠሩ የነበሩ ወንድሞች ለእስር ተዳርገዋል። እነዚህ ቅን ልብ የነበራቸው ክርስቲያኖች በዚህ መንገድ መጥራታቸው በእጅጉ ጠቅሟቸዋል። አንደኛው የዓለም ጦርነት ካበቃ በኋላ ይሖዋ የሚሰጣቸውን ማንኛውንም መመሪያ በመከተል ታላቁን አምላካቸውን ለማገልገል ከምንጊዜውም ይበልጥ ቆርጠው እንዲነሱ ገፋፍቷቸዋል።

13. የይሖዋ ሕዝቦች ከአንደኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ የደረሰባቸው ስደት ምን አላደረጋቸውም?

13 ከዚያን ጊዜ አንስቶ የይሖዋ ምሥክሮች እጅግ አስከፊ የሆኑ በርካታ ስደቶች ደርሰውባቸዋል። ሆኖም ይህ ሁኔታ የፈጣሪያቸውን ቃል እንዲጠራጠሩ አላደረጋቸውም። ከዚህ ይልቅ ሐዋርያው ጴጥሮስ በዘመኑ ስደት ይደርስባቸው ለነበሩ ክርስቲያኖች የጻፋቸውን ቃላት እንዲያስተውሉ አድርጓቸዋል:- “የተፈተነ እምነታችሁ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ፣ ለምስጋናና ለክብር ለውዳሴም ይገኝ ዘንድ . . . በልዩ ልዩ ፈተና አዝናችኋል።” (1 ጴጥሮስ 1:​6, 7) ከባድ ስደት እውነተኛ ክርስቲያኖችን ከአቋማቸው ፍንክች ሊያደርጋቸው አይችልም። ከዚህ ይልቅ ይሖዋን የሚያገለግሉት በንጹሕ ልቦና ተነሳስተው እንደሆነ በይፋ ይረጋገጣል። የተፈተነ እምነት እንዲኖራቸው የሚያደርግ ከመሆኑም በላይ ለአምላክ ያላቸውን የጠለቀ አክብሮትና ፍቅር ያሳያል።​—⁠ምሳሌ 17:​3

“እኔ ፊተኛው ነኝ እኔም ኋለኛው ነኝ”

14. (ሀ) ይሖዋ “ፊተኛው” እና “ኋለኛው” የሆነው በምን መንገድ ነው? (ለ) ይሖዋ ‘በእጁ’ ምን ድንቅ ሥራዎች አከናውኗል?

14 ይሖዋ በመቀጠል የቃል ኪዳን ሕዝቡን ስሜት በሚነካ መንገድ እንዲህ ሲል ተናገረ:- “ያዕቆብ ሆይ፣ የጠራሁህም እስራኤል ሆይ፣ ስማኝ፤ እኔ ነኝ፤ እኔ ፊተኛው ነኝ እኔም ኋለኛው ነኝ። እጄም ምድርን መሥርታለች ቀኜም ሰማያትን ዘርግታለች፤ በጠራኋቸው ጊዜ በአንድነት ይቆማሉ።” (ኢሳይያስ 48:12, 13) አምላክ ዘላለማዊና የማይለወጥ በመሆኑ ከሰው ልጆች ፈጽሞ የተለየ ነው። (ሚልክያስ 3:​6) ይሖዋ በራእይ መጽሐፍ ላይ “አልፋና ዖሜጋ፣ ፊተኛውና ኋለኛው፣ መጀመሪያውና መጨረሻው እኔ ነኝ” ሲል ተናግሯል። (ራእይ 22:13) ከይሖዋ በፊት ሁሉን ቻይ የሆነ አምላክ አልነበረም፤ ከእሱም በኋላ ሊኖር አይችልም። የሁሉ የበላይ የሆነ ዘላለማዊ አምላክና ፈጣሪ ነው። ይሖዋ ‘እጁን’ ማለትም ኃይሉን በመጠቀም ምድርን መሥርቷል፣ በከዋክብት ያሸበረቁትን ሰማያትም ዘርግቷል። (ኢዮብ 38:​4፤ መዝሙር 102:​25) ፍጥረታቱን ሲጠራቸው እሱን ለማገልገል በፊቱ ይቆማሉ።​—⁠መዝሙር 147:​4

15. ይሖዋ ቂሮስን “የወደደው” በምን መንገድ ነው? ለምንስ ዓላማ?

15 አይሁዶችም ሆኑ አይሁድ ያልሆኑ ሰዎች አንድ ትልቅ ጥሪ ቀርቦላቸዋል:- “እናንተ ሁሉ፣ በአንድነት ተሰብስባችሁ ስሙ፤ ከእነርሱ ይህን የተናገረ ማን ነው? እግዚአብሔር የወደደው ፈቃዱን በባቢሎን ላይ ያደርጋል፣ ክንዱም በከለዳውያን ላይ ይሆናል። እኔ ራሴ ተናግሬአለሁ፤ እኔ ጠርቼዋለሁ፤ አምጥቼዋለሁ፣ መንገዱም ትከናወንለታለች።” (ኢሳይያስ 48:14, 15) ሁሉን ለማድረግ የሚያስችል ኃይል ያለውና ወደፊት የሚሆኑትን ነገሮች በትክክል ሊተነብይ የሚችለው ይሖዋ ብቻ ነው። “ከእነርሱ” ማለትም ከንቱ ከሆኑት ጣዖታት መካከል እነዚህን ነገሮች ሊተነብይ የሚችል የለም። ቂሮስን “የወደደው” ይኸውም ለአንድ የተለየ ዓላማ የመረጠው ይሖዋ እንጂ ጣዖታት አይደሉም። (ኢሳይያስ 41:​2፤ 44:​28፤ 45:​1, 13፤ 46:​11) ቂሮስ ወደ ዓለም መድረክ ብቅ እንደሚል አስቀድሞ የተናገረውና ባቢሎንን ድል እንዲያደርግ የሾመው ይሖዋ ነው።

16, 17. (ሀ) አምላክ ትንቢቶቹን የተናገረው በምስጢር አይደለም የምንለው ለምንድን ነው? (ለ) በአሁኑ ጊዜ ይሖዋ ዓላማዎቹን በግልጽ እያስታወቀ ያለው እንዴት ነው?

16 ይሖዋ የሚጋብዝ ዓይነት አነጋገር በመጠቀም እንዲህ አለ:- “ወደ እኔ ቅረቡ ይህንም ስሙ፤ እኔ ከጥንት ጀምሬ በስውር አልተናገርሁም፤ ከሆነበት ዘመን ጀምሮ እኔ በዚያ ነበርሁ።” (ኢሳይያስ 48:16ሀ) ይሖዋ በምስጢር የተናገረው ትንቢት የለም፤ ትንቢቱን የሚያስታውቀውም ለጥቂት የተመረጡ ግለሰቦች ብቻ አይደለም። የይሖዋ ነቢያት አምላክን በመወከል ቃሉን በቀጥታ ያስተላልፉ ነበር። (ኢሳይያስ 61:​1) የአምላክን ፈቃድ በይፋ አውጀዋል። ለምሳሌ ያህል ከቂሮስ ጋር በተያያዘ የተከናወኑት ሁኔታዎች ለአምላክ አዲስ አልነበሩም። ወደ 200 የሚጠጉ ዓመታት አስቀድሞ እነዚህ ሁኔታዎች እንደሚፈጸሙ በኢሳይያስ በኩል በግልጽ ተንብዮ ነበር።

17 ዛሬም በተመሳሳይ ይሖዋ ዓላማዎቹን አይደብቅም። በብዙ አገሮችና ደሴቶች የሚኖሩ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ከቤት ወደ ቤት በመሄድ፣ በመንገድ ላይና ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ በመጠቀም በቅርቡ በዚህ ሥርዓት ላይ ስለሚመጣው ጥፋት ማስጠንቀቂያ እየሰጡ ከመሆኑም በላይ የአምላክ መንግሥት አገዛዝ ስለሚያመጣቸው በረከቶች የሚገልጸውን የምሥራች እያወጁ ነው። በእርግጥም ይሖዋ ዓላማዎቹን ለሰዎች የሚገልጥ አምላክ ነው።

‘ትእዛዜን ስሙ’

18. ይሖዋ ሕዝቡ ምን እንዲያደርጉ ይፈልጋል?

18 ነቢዩ በይሖዋ መንፈስ ተሞልቶ እንዲህ ሲል ተናገረ:- “ጌታ እግዚአብሔርና መንፈሱ ልከውኛል። ታዳጊህ፣ የእስራኤል ቅዱስ፣ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል:- እኔ የሚረባህን ነገር የማስተምርህ በምትሄድባትም መንገድ የምመራህ አምላክህ እግዚአብሔር ነኝ።” (ኢሳይያስ 48:16ለ, 17) ይህ ፍቅራዊ መግለጫ ይሖዋ ከባቢሎን ነፃ እንደሚያወጣቸው ለእስራኤላውያን ጥሩ ማረጋገጫ ሊሆንላቸው ይገባል። ይሖዋ ታዳጊያቸው ነው። (ኢሳይያስ 54:​5) የይሖዋ ምኞት ሕዝቡ ዳግመኛ ከእሱ ጋር ጥሩ ዝምድና እንዲመሠርቱና ትእዛዛቱን እንዲያከብሩ ነው። እውነተኛ አምልኮ መለኮታዊ መመሪያዎችን በመታዘዝ ላይ የተመካ ነው። ‘ሊሄዱበት የሚገባቸውን መንገድ’ እስካልመራቸው ድረስ እስራኤላውያን በትክክለኛው ጎዳና ላይ ሊጓዙ አይችሉም።

19. ይሖዋ ምን ፍቅራዊ ግብዣ አቅርቧል?

19 ይሖዋ ቀጥሎ የተናገራቸው ልብ የሚነኩ ቃላት ሕዝቡ ከመከራ እንዲጠበቁና በደስታ እንዲኖሩ የሚፈልግ መሆኑን የሚያመለክቱ ናቸው:- “ትእዛዜን ብትሰማ ኖሮ፣ ሰላምህ እንደ ወንዝ ጽድቅህም እንደ ባሕር ሞገድ በሆነ ነበር።” (ኢሳይያስ 48:18) ሁሉን ቻይ ከሆነው ፈጣሪ የቀረበ እንዴት ያለ ፍቅራዊ ግብዣ ነው! (ዘዳግም 5:​29፤ መዝሙር 81:​13) እስራኤላውያን ትእዛዙን ቢሰሙ ወደ ግዞት በመሄድ ፋንታ እንደ ወንዝ ውኃ የተትረፈረፈ ሰላም ሊያገኙ ይችላሉ። (መዝሙር 119:​165) የጽድቅ ሥራዎቻቸውም እንደ ባሕር ሞገድ ሥፍር ቁጥር የሌላቸው ይሆናሉ። (አሞጽ 5:​24) ይሖዋ ለእነሱ ካለው አሳቢነት የተነሳ ሊሄዱበት የሚገባውን መንገድ በማሳየት እንዲሰሙት ተማጽኗቸዋል። ቢሰሙት ምንኛ ይጠቀሙ ነበር!

20. (ሀ) አምላክ እስራኤላውያን ዓመፀኞች ቢሆኑም እንኳ ምን እንዲደርስባቸው አልፈለገም? (ለ) ይሖዋ ለሕዝቡ የነበረው ስሜት ስለ እሱ ምን ያስተምረናል? (ገጽ 133 ላይ የሚገኘውን ሣጥን ተመልከት።)

20 እስራኤላውያን ንስሐ ቢገቡ ምን በረከቶችን ያገኛሉ? ይሖዋ እንዲህ ይላል:- “ዘርህም እንደ አሸዋ የሆድህም ትውልድ እንደ ምድር ትቢያ በሆነ ነበር፣ ስሙም ከፊቴ ባልጠፋና ባልፈረሰ ነበር።” (ኢሳይያስ 48:19) ይሖዋ ሕዝቡ የአብርሃም ዘር “እንደ ሰማይ ከዋክብትና በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ” እንደሚበዛ የገባውን ቃል እንዲያስታውሱ አድርጓቸዋል። (ዘፍጥረት 22:​17፤ 32:​12) ይሁን እንጂ እነዚህ የአብርሃም ዝርያዎች ዓመፀኞች በመሆናቸው የዚህን ተስፋ ፍጻሜ የመውረስ መብት የላቸውም። መጥፎ ታሪክ ያስመዘገቡ ሰዎች በመሆናቸው የራሱ የይሖዋ ሕግ እንኳ በብሔር ደረጃ ከምድረ ገጽ እንዲጠፉ ሊያስፈርድባቸው ይችላል። (ዘዳግም 28:​45) ያም ሆኖ ይሖዋ ሕዝቡን እስከ ወዲያኛው በመተው ከናካቴው እንዲጠፉ ማድረግ አልፈለገም።

21. በዘመናችን የይሖዋን መመሪያ ለማግኘት መጣራችን ምን በረከቶች ሊያስገኝልን ይችላል?

21 ዛሬ ያሉት የይሖዋ አምላኪዎችም ኃይለኛ መልእክት ባዘለው በዚህ ምንባብ ውስጥ የሰፈሩትን መሠረታዊ ሥርዓቶች ማክበር ይኖርባቸዋል። ይሖዋ የሕይወት ምንጭ በመሆኑ ሕይወታችንን እንዴት ልንጠቀምበት እንደሚገባ ከማንም በላይ የሚያውቀው እርሱ ነው። (መዝሙር 36:​9) ያወጣቸው መመሪያዎች ደስታችንን የሚሰርቁ ሳይሆኑ ለእኛው ሕይወት የሚበጁ ናቸው። እውነተኛ ክርስቲያኖች ከይሖዋ ለመማር ጥረት በማድረግ ለዚህ ያላቸውን አድናቆት ያሳያሉ። (ሚክያስ 4:​2) ይሖዋ የሚሰጠን መመሪያ መንፈሳዊነታችን እና ከእርሱ ጋር ያለን ዝምድና እንዲጠበቅ የሚያደርግ ከመሆኑም ሌላ አቋማችንን ሊያበላሽ የሚችለውን የሰይጣን ተጽዕኖ መቋቋም እንድንችል ይረዳናል። የአምላክ ሕግጋት የተመሠረቱባቸውን መሠረታዊ ሥርዓቶች ጠለቅ ብለን ስናስተውል ይሖዋ የሚያስተምረን ለእኛው ጥቅም እንደሆነ እንገነዘባለን። ‘ትእዛዛቱም ከባዶች እንዳልሆኑ’ እንረዳለን። ይህም ከጥፋት እንድንጠበቅ ይረዳናል።​—⁠1 ዮሐንስ 2:​17፤ 5:​3

“ከባቢሎን ውጡ”

22. ታማኝ አይሁዳውያን ምን እንዲያደርጉ ታዝዘዋል? ምን ዋስትናስ ተሰጥቷቸዋል?

22 ባቢሎን በምትወድቅበት ጊዜ ትክክለኛ የልብ ዝንባሌ የሚያሳዩ አይሁዶች ይገኙ ይሆን? አምላክ በሚሰጣቸው ነፃነት በመጠቀም ወደ ትውልድ አገራቸው ተመልሰው ንጹሕ አምልኮን እንደገና ያቋቁሙ ይሆን? አዎን። ይሖዋ ቀጥሎ የተናገራቸው ቃላት ይህ እንደሚፈጸም ሙሉ እምነት እንዳለው የሚያሳዩ ናቸው። “ከባቢሎን ውጡ ከከለዳውያንም ኰብልሉ፤ በእልልታ ድምፅ ተናገሩ ይህንም ንገሩ እስከ ምድርም ዳርቻ ድረስ አውሩና:- እግዚአብሔር ባሪያውን ያዕቆብን ታድጎታል በሉ። በምድረ በዳ በኩል በመራቸው ጊዜ አልተጠሙም፤ ውኃንም ከዓለቱ ውስጥ አፈለቀላቸው፣ ዓለቱንም ሰነጠቀ ውኃውም ፈሰሰ።” (ኢሳይያስ 48:20, 21) የይሖዋ ሕዝቦች ምንም ጊዜ ሳያጠፉ ከባቢሎን እንዲወጡ ጥብቅ ማሳሰቢያ ተሰጥቷቸዋል። (ኤርምያስ 50:​8) ይሖዋ ከጠላቶቻቸው እንደተቤዣቸው እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ መታወቅ ይኖርበታል። (ኤርምያስ 31:​10) ሕዝቡ ከግብጽ ምድር ወጥተው በበረሃ ይጓዙ በነበረበት ወቅት የሚያስፈልጋቸውን ነገር ሁሉ አሟልቶ ሰጥቷቸዋል። በተመሳሳይም ከባቢሎን ነፃ ወጥተው ወደ አገራቸው በሚመለሱበት ጊዜ የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ ያሟላላቸዋል።​—⁠ዘዳግም 8:​15, 16

23. አምላክ የሚሰጠውን ሰላም የማያገኙት እነማን ናቸው?

23 አይሁዳውያን ይሖዋ እነሱን ለማዳን የሚወስዳቸውን እርምጃዎች በተመለከተ አንድ ሊዘነጉት የማይገባ በጣም አስፈላጊ የሆነ መሠረታዊ ሥርዓት ነበር። የጽድቅ ዝንባሌ ያላቸው ሰዎች በኃጢአታቸው ምክንያት ለመከራ ሊዳረጉ ቢችሉም እንኳ ጥፋት አይደርስባቸውም። ክፉ የሆኑ ሰዎችን በተመለከተ ግን ሁኔታው ከዚህ ፈጽሞ የተለየ ነው። “ለክፉዎች ሰላም የላቸውም ይላል እግዚአብሔር።” (ኢሳይያስ 48:22) ንስሐ የማይገቡ ኃጢአተኞች አምላክ ለሚወዳቸው ሰዎች ያቆየውን ሰላም አያገኙም። ይሖዋ ከክፋት ድርጊታቸው የማይመለሱትን ወይም የማያምኑትን ሰዎች አያድንም። ይሖዋ የሚያድነው እምነት ያላቸውን ሰዎች ብቻ ነው። (ቲቶ 1:​15, 16፤ ራእይ 22:​14, 15) አምላክ ለክፉዎች ሰላም አይሰጥም።

24. በዘመናችን ያሉትን የአምላክ ሕዝቦች እንዲደሰቱ ያደረጋቸው ነገር ምንድን ነው?

24 ታማኝ እስራኤላውያን በ537 ከዘአበ ከባቢሎን መውጣት የሚችሉበትን አጋጣሚ በማግኘታቸው በደስታ ፈንጥዘዋል። በ1919ም የአምላክ ሕዝቦች ከባቢሎናዊ ግዞት መላቀቅ በመቻላቸው እጅግ ተደስተዋል። (ራእይ 11:​11, 12) በተስፋ ተሞልተው ያገኙትን አጋጣሚ ሥራቸውን ይበልጥ ለማስፋፋት ተጠቀሙበት። እርግጥ ነው፣ በዚያን ጊዜ የነበሩት በቁጥር አነስተኛ የሆኑ ክርስቲያኖች ያገኟቸውን አዳዲስ አጋጣሚዎች በመጠቀም በክፉ ዓይን በሚያያቸው ዓለም ውስጥ ለመስበክ ትልቅ ድፍረት ጠይቆባቸዋል። ይሁን እንጂ በይሖዋ እርዳታ በመታገዝ የምሥራቹን ስብከት ሥራ ማካሄድ ችለዋል። ይሖዋም ጥረታቸውን እንደባረከው ታሪክ በሚገባ ይመሰክራል።

25. የአምላክን የጽድቅ ሕግጋት በጥብቅ መከተላችን አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

25 ይህ የኢሳይያስ ትንቢት ክፍል ይሖዋ የሚያስተምረን ለጥቅማችን እንደሆነ ጠበቅ አድርጎ ይገልጻል። የአምላክን የጽድቅ ሕግጋት በጥብቅ መከተላችን በጣም አስፈላጊ ነው። (ራእይ 15:​2-4) አምላክ ጥበበኛና አፍቃሪ እንደሆነ ዘወትር ማስታወሳችን ይሖዋ አድርጉ ያለንን ነገር እንድናደርግ ይገፋፋናል።0 ማንኛውንም ትእዛዝ የሚሰጠን ለእኛው ጥቅም ነው።​—⁠ኢሳይያስ 48:​17, 18

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 133 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕሎች]

ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ ራሱን ይገታል

ይሖዋ ከሃዲዎቹን እስራኤላውያን “ቁጣዬን አዘገያለሁ፣ . . . እታገሣለሁ” ብሏቸው ነበር። (ኢሳይያስ 48:9) እንዲህ ያሉት መግለጫዎች አምላክ ኃይሉን አላግባብ እንደማይጠቀምና በዚህ ረገድ ፍጹም ምሳሌ እንደሆነ እንድንገነዘብ ይረዱናል። ከይሖዋ አምላክ የበለጠ ኃይል ያለው አካል እንደሌለ እሙን ነው። ምንም ነገር የማይሳነውና በሁሉ ላይ ሥልጣን ያለው አምላክ እንደሆነ የምንናገረው ለዚህ ነው። ራሱን “ሁሉን ቻይ” ብሎ መጥራቱ የተገባ ነው። (ዘፍጥረት 17:​1) ሁሉን ለማድረግ የሚያስችል ኃይል ያለው ከመሆኑም በላይ በፈጠረው ጽንፈ ዓለም ውስጥ ሉዓላዊ ጌታ በመሆኑ በሁሉ ላይ ሥልጣን አለው። በመሆኑም እጁን ሊከለክል ወይም “ምን ታደርጋለህ?” ብሎ ሊጠይቀው የሚደፍር የለም።​—⁠ዳንኤል 4:​35

ይሁን እንጂ አምላክ ኃይሉን በጠላቶቹ ላይ መግለጥ በሚያስፈልገው ጊዜ እንኳ ለቁጣ የዘገየ ነው። (ናሆም 1:​3 አ.መ.ት ) ይሖዋ ቁጣውን መግታት የሚችል ሲሆን ዋነኛው ባሕርይው ፍቅር እንጂ ቁጣ ባለመሆኑ “ለቁጣ የዘገየ” ተብሎ መገለጹ ተገቢ ነው። ቁጣውን የሚገልጸውም ትክክለኛ፣ ፍትሐዊና አግባብ በሆነ መንገድ ብቻ ነው።​—⁠ዘጸአት 34:​6፤ 1 ዮሐንስ 4:​8

ይሖዋ እንዲህ ያለ ባሕርይ የሚያሳየው ለምንድን ነው? ሁሉን ማድረግ የሚያስችለውን ኃይሉን ከሌሎች ሦስት ዋና ዋና ባሕርያቱ ማለትም ከጥበቡ፣ ከፍትሑና ከፍቅሩ ጋር ፍጹም ሚዛናዊ በሆነ መንገድ ስለሚጠቀምበት ነው። ምንጊዜም ኃይሉን የሚጠቀምበት ከእነዚህ ባሕርያቱ ጋር በሚጣጣም መንገድ ነው።

[በገጽ 122 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ኢሳይያስ ወደ ትውልድ አገራቸው እንደሚመለሱ የተናገረው ቃል በግዞት ለነበሩት ታማኝ አይሁዳውያን ተስፋ ፈንጥቆላቸዋል

[በገጽ 124 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

አይሁዳውያን ይሖዋ ያከናወናቸውን ነገሮች ጣዖታት እንደሠሯቸው አድርገው የመናገር ዝንባሌ ነበራቸው

1. ኢሽታር  2. ባቢሎናውያን በበዓላት ቀን በሰልፍ ይጓዙበት በነበረ መንገድ ላይ የሚገኝ ከጡብ የተሠራ የሚያብረቀርቅ ምስል 3. በማርዱክ የተሰየመ የደራጎን ምስል

[በገጽ 127 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

‘የመከራ እቶን’ ይሖዋን የምናገለግለው በንጹሕ ልቦና መሆን አለመሆኑን በግልጽ ሊያሳይ ይችላል

[በገጽ 128 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

እውነተኛ ክርስቲያኖች እጅግ አስከፊ የሆኑ ስደቶች ደርሰውባቸዋል