በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይሖዋ የተሰበረ ልብ ያላቸውን ሰዎች መንፈስ ያነቃቃል

ይሖዋ የተሰበረ ልብ ያላቸውን ሰዎች መንፈስ ያነቃቃል

ምዕራፍ አሥራ ስምንት

ይሖዋ የተሰበረ ልብ ያላቸውን ሰዎች መንፈስ ያነቃቃል

ኢሳይያስ 57:​1-21

1. ይሖዋ ምን ዋስትና ሰጥቷል? ይህስ የትኞቹን ጥያቄዎች ያስነሳል?

“ለዘላለም የሚኖር ስሙም ቅዱስ የሆነ፣ ከፍ ያለው ልዑል እንዲህ ይላል:- የተዋረዱትን ሰዎች መንፈስ ሕያው አደርግ ዘንድ፣ የተቀጠቀጠውንም ልብ ሕያው አደርግ ዘንድ፣ የተቀጠቀጠና የተዋረደ መንፈስ ካለው ጋር በከፍታና በተቀደሰ ስፍራ እቀመጣለሁ።” (ኢሳይያስ 57:15) ነቢዩ ኢሳይያስ ይህን የጻፈው በስምንተኛው መቶ ዘመን ከዘአበ ነው። ይህ መልእክት እጅግ አጽናኝ የሆነው በይሁዳ ምድር ምን ተፈጽሞ ስለነበረ ነው? በመንፈስ አነሳሽነት የተጻፉት እነዚህ ቃላት በዘመናችን ያሉትን ክርስቲያኖች የሚጠቅሟቸውስ እንዴት ነው? ኢሳይያስ ምዕራፍ 57⁠ን መመርመራችን ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ እንድናገኝ ይረዳናል።

‘እናንተ ሰዎች ወደዚህ ቅረቡ’

2. (ሀ)በ⁠ኢሳይያስ ምዕራፍ 57 ላይ የሰፈሩት ቃላት የተነገሩት የትኛውን ጊዜ በማስመልከት መሆን አለበት? (ለ) በኢሳይያስ ዘመን ጻድቃን በምን ዓይነት ሁኔታ ላይ ይገኙ ነበር?

2 ይህ የኢሳይያስ ትንቢት ክፍል በራሱ በኢሳይያስ ዘመን የነበረውን ሁኔታ አስመልክቶ የተነገረ ይመስላል። በዚያ ዘመን ክፋት ምን ያህል ሥር ሰድዶ እንደነበረ ተመልከት:- “ጻድቅ ይሞታል፣ በልቡም ነገሩን የሚያኖር የለም፤ ምሕረተኞችም ይወገዳሉ፣ ጽድቅም ከክፋት ፊት እንደ ተወገደ ማንም አያስተውልም። ወደ ሰላም ይገባል፤ በቅንነት የሄደ በአልጋው ላይ ያርፋል።” (ኢሳይያስ 57:1, 2) ጻድቅ ሰው ቢሞት ግድ የሚሰጠው አይኖርም። ያለዕድሜው መቀጨቱን ልብ የሚል የለም። በሞት ማንቀላፋቱ አምላክ የለሽ ሰዎች ከሚያደርሱበት ስቃይና መከራ እንዲያርፍና ሰላም እንዲያገኝ ያደርገዋል። አምላክ የመረጠው ሕዝብ እጅግ አሳዛኝ በሆነ መጥፎ ሁኔታ ላይ ይገኝ ነበር። ይሁን እንጂ በታማኝነት የጸኑት ሰዎች ይሖዋ እየተፈጸመ ያለውን ሁኔታ እንደሚያይ ብቻ ሳይሆን እነሱንም እንደሚደግፋቸው ማወቃቸው ሊያጽናናቸው ይገባል!

3. ይሖዋ በይሁዳ የነበረውን ክፉ ትውልድ ምን ብሎታል? ለምንስ?

3 ይሖዋ በይሁዳ ለነበረው ክፉ ትውልድ የሚከተለውን ጥሪ አስተላለፈ:- “እናንተ የአስማተኛይቱ ልጆች፣ የአመንዝራውና የጋለሞታይቱ ዘር፣ ወደዚህ ቅረቡ።” (ኢሳይያስ 57:3) በዘመኑ የነበሩት ሰዎች የአስማተኛ ልጆች እንዲሁም የአመንዝራና የጋለሞታ ዘር ተብለው እጅግ በሚያዋርድ መንገድ መጠራታቸው ተገቢ ነው። የሐሰት አምልኳቸው ጸያፍ የሆነ የጣዖት አምልኮንና መናፍስታዊ ድርጊቶችን እንዲሁም የጾታ ብልግና መፈጸምን ያካተተ ነበር። በመሆኑም ይሖዋ እነዚህን ኃጢአተኞች እንዲህ ሲል ጠየቃቸው:- “በማን ታላግጣላችሁ? በማንስ ላይ አፋችሁን ታላቅቃላችሁ? ምላሳችሁንስ በማን ላይ ታስረዝማላችሁ? እናንተ በአድባር ዛፎች መካከል በለመለመም ዛፍ ሁሉ በታች በፍትወት የምትቃጠሉ፣ እናንተም በሸለቆች ውስጥ በዓለትም ስንጣቂዎች በታች ሕፃናትን የምታርዱ፣ የዓመፅ ልጆችና የሐሰት ዘር አይደላችሁምን?”​—⁠ኢሳይያስ 57:4, 5

4. ክፉዎቹ የይሁዳ ነዋሪዎች በምን ነገር ተጠያቂዎች ናቸው?

4 ክፉዎቹ የይሁዳ ነዋሪዎች ዘግናኝ የሆነ የአረማውያን አምልኮ በመፈጸም ‘ያላግጡ’ ነበር። እንዲያርሟቸውና እንዲያስተካክሏቸው ለተላኩት የአምላክ ነቢያት ያላቸውን ንቀት በሚያሳይ ሁኔታ ያለአንዳች ኀፍረት ምላሳቸውን በማውጣት ይሳለቁባቸው ነበር። የአብርሃም ልጆች ቢሆኑም እንኳ ድርጊታቸው የዓመፅ ልጆችና የሐሰት ዘር እንዲሆኑ አድርጓቸዋል። (ኢሳይያስ 1:​4፤ 30:​9፤ ዮሐንስ 8:​39, 44) ገጠራማ በሆኑ ቦታዎች በአድባር ዛፎች መካከል የጣዖት አምልኮ በመፈጸም እጅግ የጦፈ ሃይማኖታዊ ስሜት ይቀሰቅሳሉ። አምልኳቸው ደግሞ በጭካኔ ድርጊቶች የተሞላ ነው! ይሖዋ ጸያፍ በሆኑ ድርጊቶቻቸው የተነሳ ከምድሪቱ ያጠፋቸው ሕዝቦች ያደርጉት እንደነበረው ልጆቻቸውን እስከ መሠዋት ደርሰዋል!​—⁠1 ነገሥት 14:​23፤ 2 ነገሥት 16:​3, 4፤ ኢሳይያስ 1:​29

ለድንጋዮች የመጠጥ ቁርባን ማቅረብ

5, 6. (ሀ) የይሁዳ ነዋሪዎች ይሖዋን ማምለክ ሲገባቸው ምን ማድረግ መርጠዋል? (ለ) የጣዖት አምልኮ በይሁዳ ውስጥ ምን ያህል ተስፋፍቶ ነበር?

5 የይሁዳ ነዋሪዎች በጣዖት አምልኮ ምን ያህል እንደተዘፈቁ ተመልከት:- “በሸለቆው ውስጥ ያሉ የለዘቡ ድንጋዮች እድል ፈንታሽ ናቸው፣ እነርሱም ዕጣሽ ናቸው፤ ለእነርሱም የመጠጥ ቁርባን አፍስሰሻል፣ የእህልንም ቁርባን አቅርበሻል። እንግዲህ በዚህ ነገር አልቈጣምን?” (ኢሳይያስ 57:6) አይሁዳውያን የአምላክ የቃል ኪዳን ሕዝብ እንደመሆናቸው መጠን እሱን ማምለክ ሲገባቸው ከወንዝ በወሰዷቸው ድንጋዮች አማልክት ሠርተዋል። ዳዊት እድል ፈንታው ይሖዋ እንደሆነ ተናግሯል፤ እነዚህ ኃጢአተኞች ግን በድን የሆኑ የድንጋይ ጣዖታትን ዕጣቸው አድርገው በመምረጥ የመጠጥ ቁርባን አቅርበዋል። (መዝሙር 16:​5፤ ዕንባቆም 2:​19) ይሖዋ ስሙን የተሸከሙ ሕዝቦቹ እንዲህ ያለ ብልሹ አምልኮ ሲፈጽሙ እንዴት አይቆጣ!

6 ይሁዳ በተገኘው ሥፍራ ሁሉ ማለትም በአድባር ዛፎች ሥር፣ በሸለቆዎች፣ በተራሮችና በከተሞች ውስጥ የጣዖት አምልኮ ትፈጽማለች። ሆኖም ይሖዋ የምታደርገውን ነገር ሁሉ ይመለከት ስለነበር ብልሹ ምግባሯን በኢሳይያስ በኩል አጋልጧል:- “ከፍ ባለውም በረዘመውም ተራራ ላይ መኝታሽን አደረግሽ፣ መሥዋዕትንም ትሠዊ ዘንድ ወደዚያ ወጣሽ። ከመዝጊያውና ከመቃኑ በኋላ መታሰቢያሽን አደረግሽ።” (ኢሳይያስ 57:​7-8ሀ) ይሁዳ በከፍታ ቦታዎች ላይ መንፈሳዊ ርኩሰት የምትፈጽምበትን መኝታ አዘጋጅታ ለባዕድ አማልክት መሥዋዕት ታቀርባለች። * የግል መኖሪያ ቤቶች እንኳ ሳይቀሩ ከበሮቻቸውና ከመቃኖቻቸው ጀርባ የተንጠለጠሉ ጣዖታት አሏቸው።

7. ይሁዳ ብልሹ በሆነ አምልኮ እንድትዘፈቅ ያደረጋት ምንድን ነው?

7 አንዳንዶች ይሁዳ ርኩስ በሆነ አምልኮ ይህን ያህል ልትዘፈቅ የቻለችው ለምንድን ነው ብለው ሊጠይቁ ይችላሉ። አንድ የበላይ የሆነ ኃይል ይሖዋን እንድትተው አስገድዷት ነው? በፍጹም። ይህን ያደረገችው ራሷ ፈልጋና ወድዳ ነው። ይሖዋ እንዲህ ሲል ገልጿል:- “እኔን ትተሽ ለሌላ ተገልጠሻል፣ ወጥተሽ መኝታሽን አስፍተሻል፤ ቃል ኪዳንም ተጋባሻቸው፣ ባየሽበትም ስፍራ ሁሉ መኝታቸውን ወደድሽ [“ዕርቃናቸውንም አየሽ፣” አ.መ.ት ]።” (ኢሳይያስ 57:8ለ) ይሁዳ ከሐሰት አማልክቷ ጋር ቃል ኪዳን የተጋባች ከመሆኑም በላይ ከእነሱ ጋር በመሠረተችው ሕገወጥ ዝምድና ተደስታለች። በተለይም በዚያ የሚፈጸሙት አስጸያፊ የብልግና ድርጊቶች ማርከዋታል። ይህ ደግሞ የእነዚህ አማልክት አምልኮ መለያ የሆነውን የወንድ ብልት ተምሳሌቶችን የመጠቀም ልማድን እንደሚጨምር መገመት ይቻላል።

8. በይሁዳ የጣዖት አምልኮ በይበልጥ የተስፋፋው በየትኛው ንጉሥ ዘመን ነው?

8 ፈጽሞ ከሥነ ምግባር ውጭ የሆነውንና ጭካኔ የተሞላበትን የጣዖት አምልኮ በተመለከተ የተሰጠው ይህ መግለጫ አንዳንድ ክፉ የይሁዳ ነገሥታትን አስመልክቶ ከሰፈረው ዘገባ ጋር ይስማማል። ለምሳሌ ያህል ምናሴ የኮረብታ መስገጃዎችን ገንብቷል፣ ለበኣል መሠዊያዎችን ሠርቷል እንዲሁም በሁለቱ የቤተ መቅደስ አደባባዮች የሐሰት ሃይማኖት መሠዊያዎችን አቁሟል። ልጆቹን በእሳት ከመሠዋቱም በላይ አስማተኛና መተተኛ ሆኗል፤ እንዲሁም መናፍስታዊ ድርጊቶች እንዲስፋፉ አድርጓል። ከዚህም በተጨማሪ ንጉሥ ምናሴ የሠራውን የማምለኪያ ዐፀድ የተቀረጸ ምስል በይሖዋ ቤተ መቅደስ ውስጥ አቁሟል። * ይሖዋ “ካጠፋቸው ከአሕዛብ ይልቅ ክፉ ይሠሩ ዘንድ” ይሁዳን አሳተ። (2 ነገሥት 21:​2-9) የምናሴ ስም በ⁠ኢሳይያስ 1:​1 ላይ ያልተጠቀሰ ቢሆንም እንኳ አንዳንዶች ኢሳይያስን ያስገደለው ምናሴ እንደሆነ ይናገራሉ።

‘መልእክተኞችሽንም ላክሽ’

9. ይሁዳ መልእክተኞችን “ወደ ሩቅ” የላከችው ለምንድን ነው?

9 ይሁዳ የይሖዋን ሕግ የተላለፈችው የሐሰት አማልክትን በማገልገል ብቻ አይደለም። ይሖዋ ኢሳይያስን እንደ ቃል አቀባይ አድርጎ በመጠቀም እንዲህ አለ:- “ዘይትም ይዘሽ ወደ ንጉሡ ሄድሽ፣ ሽቱሽንም አበዛሽ፣ መልእክተኞችሽንም ወደ ሩቅ ላክሽ፣ እስከ ሲኦልም ድረስ ተዋረድሽ።” (ኢሳይያስ 57:9) ከዳተኛዋ የይሁዳ መንግሥት በዘይትና በሽቱ የተወከሉትን ውድና የሚማርኩ ስጦታዎች ይዛ ወደ “ንጉሡ” ማለትም ወደ ባዕድ አገር ንጉሥ ሄዳለች። ይሁዳ በሩቅ ወዳሉ ቦታዎች መልእክተኞች ልካለች። ለምን? የአሕዛብ ብሔራት ከእሷ ጋር ፖለቲካዊ ኅብረት እንዲፈጥሩ ለማግባባት ስትል ነው። ለይሖዋ ጀርባዋን በመስጠት በባዕድ ነገሥታት ታምናለች።

10. (ሀ) ንጉሥ አካዝ ከአሦር ንጉሥ ጋር ኅብረት ለመፍጠር የሞከረው እንዴት ነው? (ለ) ይሁዳ ‘እስከ ሲኦል ድረስ የምትዋረደው’ በምን መንገድ ነው?

10 በንጉሥ አካዝ ዘመን የተፈጸመው ሁኔታ ለዚህ ምሳሌ ይሆነናል። ይህ ከሃዲ የይሁዳ ንጉሥ እስራኤልና ሶርያ የፈጠሩት ጥምረት ስጋት ስላሳደረበት “እኔ ባሪያህና ልጅህ ነኝ፤ መጥተህ ከተነሡብን ከሶርያ ንጉሥና ከእስራኤል ንጉሥ እጅ አድነኝ” ብሎ ወደ አሦር ንጉሥ ወደ ሳልሳዊ ቴልጌልቴልፌልሶር መልእክተኞች ላከ። አካዝ ለአሦሩ ንጉሥ ገጸ በረከት አድርጎ ብርና ወርቅ የሰደደለት ሲሆን ንጉሡም በሶርያ ላይ መጠነ ሰፊ ጥቃት በመሰንዘር ብድራቱን መልሷል። (2 ነገሥት 16:​7-9) ይሁዳ ከአሕዛብ ብሔራት ጋር ግንኙነት በመመሥረቷ ‘እስከ ሲኦል ድረስ ትዋረዳለች።’ ከአሕዛብ ጋር በፈጠረችው ኅብረት የተነሳ ከህልውና ውጪ ትሆናለች ወይም በራሷ ንጉሥ የምትመራ ሉዓላዊት አገር መሆኗ ያከትማል።

11. ይሁዳ ምን ዓይነት ከንቱ የሆነ የደህንነት ስሜት አድሮባታል?

11 ይሖዋ እንደሚከተለው በማለት ለይሁዳ መናገሩን ቀጠለ:- “በመንገድሽም ብዛት ደከምሽ፣ ነገር ግን:- ተስፋ የለም አላልሽም፤ የጉልበትን መታደስ አገኘሽ፣ ስለዚህም አልዛልሽም።” (ኢሳይያስ 57:10) አዎን፣ ይሁዳ በተከተለችው የክህደት ጎዳና ብዙ የደከመች ሲሆን ድካሟ ሁሉ ተስፋ ቢስ መሆኑን ሳታስተውል ቀርታለች። ከዚህ ይልቅ በራሷ ኃይል ያሰበችው እንደተሳካላት አድርጋ በማመን ራሷን አታልላለች። ጉልበቷ እንደታደሰና ጤናማ እንደሆነች አድርጋ አስባለች። እንዴት ያለ ሞኝነት ነው!

12. ሕዝበ ክርስትናን ከይሁዳ ጋር የሚያመሳስሏት ሁኔታዎች ምንድን ናቸው?

12 በዘመናችንም በኢሳይያስ ዘመን ከነበረችው ከይሁዳ ጋር የሚመሳሰል ድርጊት በመፈጸም ላይ የምትገኝ ድርጅት አለች። ሕዝበ ክርስትና በኢየሱስ ስም የምትጠቀም ቢሆንም እንኳ ከብሔራት ጋር ኅብረት ለመፍጠር የምትጣጣር ከመሆኑም በላይ የአምልኮ ቦታዎቿ በጣዖታት የተሞሉ ናቸው። ተከታዮቿ ሳይቀሩ በቤታቸው ውስጥ ለአምልኮ የሚጠቀሙባቸው ምስሎች አሏቸው። ሕዝበ ክርስትና ብሔራት ባካሄዷቸው ጦርነቶች ወጣት አማኞቿን መሥዋዕት አድርጋ አቅርባለች። ይህ ሁሉ ድርጊት “ጣዖትን ከማምለክ ሽሹ” ሲል ያዘዘውን እውነተኛውን አምላክ ምንኛ የሚያስቆጣ ነው! (1 ቆሮንቶስ 10:​14) ሕዝበ ክርስትና በፖለቲካ ጉዳዮች ውስጥ ጣልቃ በመግባት ‘ከምድር ነገሥታት ጋር ሴስናለች።’ (ራእይ 17:​1, 2) እንዲያውም የተባበሩት መንግሥታት ቀንደኛ አጫፋሪ ነች። ይህች ሃይማኖታዊ ጋለሞታ ምን ይጠብቃታል? በቅድሚያ ይሖዋ የሕዝበ ክርስትናን ጥንታዊ አምሳያ ማለትም በዋና ከተማዋ በኢየሩሳሌም የተወከለችውን ከዳተኛዋን ይሁዳ ምን እንዳላት እንመልከት።

‘የሰበሰብሻቸው አያድኑሽም’

13. ይሁዳ በምን ዓይነት “ሐሰት” ተሞልታለች? የይሖዋንስ ትዕግሥት እንደምን ቆጥራዋለች?

13 ይሖዋ “ሐሰትን የተናገርሺው . . . ማንን ሰግተሽ ነው? ማንንስ ፈርተሽ ነው?” ሲል ጥያቄ አቅርቧል። ይህ ተገቢ ጥያቄ ነው! ይሁዳ ለይሖዋ ጤናማ የሆነ አምላካዊ ፍርሃት እንዳላሳየች የተረጋገጠ ነው። እንዲህ ያለ ጤናማ ፍርሃት ቢኖራት ኖሮ የሐሰት አማልክትን በሚያመልኩ ውሸታም ሰዎች ባልተሞላች ነበር። ይሖዋ በመቀጠል እንዲህ አለ:- ‘እኔን አላሰብሽም። በልብሽም ነገሩን አላኖርሽም። እኔ ብዙ ጊዜ ዝም አልሁ፣ አንቺም አልፈራሽም።’ (ኢሳይያስ 57:​11) ይሖዋ በይሁዳ ላይ አፋጣኝ የሆነ የቅጣት እርምጃ ከመውሰድ በመቆጠብ ሁኔታውን ረዘም ላለ ጊዜ ዝም ብሎ ተመልክቷል። ይሁዳ ይህን በልቧ አኑራለችን? በፍጹም፤ ከዚህ ይልቅ የአምላክን ትዕግሥት እንደ ቸልተኝነት አድርጋ ቆጥራዋለች። ለይሖዋ የነበራት ፍርሃት ሁሉ ጠፍቷል።

14, 15. ይሖዋ ይሁዳ ስለፈጸመችው ድርጊትና ‘ስለ ሰበሰበቻቸው ነገሮች’ ምን ተናግሯል?

14 ይሁን እንጂ የይሖዋ ትዕግሥት የሚያበቃበት ዘመን ይመጣል። ይሖዋ ያን ጊዜ አሻግሮ በመመልከት እንዲህ አለ:- “እኔ ጽድቅሽን እናገራለሁ፣ ሥራሽም አይረባሽም። ወደ አንቺ የሰበሰብሻቸው በጮኽሽ ጊዜ ይታደጉሽ፤ ንፋስ ግን ይወስዳቸዋል ሽውሽውታም ሁሉን ያስወግዳቸዋል።” (ኢሳይያስ 57:12, 13ሀ) ይሖዋ የይሁዳን የይስሙላ ጽድቅ ያጋልጠዋል። የግብዝነት ድርጊቷ የሚፈይድላት ነገር አይኖርም። ‘የሰበሰበቻቸው ነገሮች’ ማለትም ያከማቸቻቸው ጣዖታት አያድኗትም። ጥፋት በሚመጣበት ጊዜ የታመነችባቸው አማልክት በንፋስ ሽውታ ብን ብለው ይጠፋሉ።

15 ይሖዋ የተናገራቸው ቃላት በ607 ከዘአበ ተፈጽመዋል። የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር ኢየሩሳሌምን ያወደመው፣ ቤተ መቅደሱን ያቃጠለውና አብዛኛውን ነዋሪ የማረከው በዚያ ወቅት ነው። “እንዲሁ ይሁዳ ከአገሩ ተማረከ።”​—⁠2 ነገሥት 25:​1-21

16. ሕዝበ ክርስትናም ሆነች የተቀረው ‘የታላቂቱ ባቢሎን’ ክፍል ምን ይጠብቃቸዋል?

16 በተመሳሳይም ሕዝበ ክርስትና ያከማቸቻቸው በርካታ ጣዖታት በይሖዋ የቁጣ ቀን አያድኗትም። (ኢሳይያስ 2:​19-22፤ 2 ተሰሎንቄ 1:​6-10) ሕዝበ ክርስትና የዓለም የሐሰት ሃይማኖት ግዛት ከሆነው ከተቀረው ‘የታላቂቱ ባቢሎን’ ክፍል ጋር ትጠፋለች። ምሳሌያዊው ቀይ አውሬና አሥር ቀንዶቹ “[ታላቂቱ ባቢሎንን] ባዶዋንና ራቁትዋንም ያደርጓታል፣ ሥጋዋንም ይበላሉ፣ በእሳትም ያቃጥሉአታል።” (ራእይ 17:​3, 16, 17) “ሕዝቤ ሆይ፣ በኃጢአትዋ እንዳትተባበሩ ከመቅሠፍትዋም እንዳትቀበሉ ከእርስዋ ዘንድ ውጡ” የሚለውን ትእዛዝ በማክበራችን ምንኛ ደስተኞች ነን! (ራእይ 18:4, 5) ዳግመኛ ወደ እሷ መመለስም ሆነ በመንገዶቿ መመላለስ አይኖርብንም።

‘በእኔ የታመነ ምድሪቱን ይወርሳል’

17. ‘በይሖዋ ለሚታመን ሰው’ ምን ተስፋ ተሰጥቷል? ይህስ ፍጻሜውን የሚያገኘው መቼ ነው?

17 ይሁንና ቀጥሎ ስለተጠቀሱት የኢሳይያስ ትንቢታዊ ቃላት ምን ለማለት ይቻላል? “በእኔ የታመነ ግን ምድሪቱን ይገዛል፣ የተቀደሰውንም ተራራዬን ይወርሳል።” (ኢሳይያስ 57:13ለ) ይሖዋ እዚህ ላይ እየተናገረ ያለው ለማን ነው? በይሁዳ ላይ እያንዣበበ ካለው ታላቅ ጥፋት በኋላ የሚኖረውን ሁኔታ አሻግሮ በመመልከት ሕዝቡ ከባቢሎን ነፃ እንደሚወጡና ንጹሕ አምልኮ በቅዱስ ተራራው በኢየሩሳሌም ዳግመኛ እንደሚቋቋም እየተነበየ ነው። (ኢሳይያስ 66:​20፤ ዳንኤል 9:​16) ይህ ትንቢት በታማኝነት ለጸኑ አይሁዳውያን ሁሉ እንዴት ያለ ማበረታቻ ነው! በመቀጠል ይሖዋ እንዲህ አለ:- “እርሱም:- ጥረጉ፣ መንገድን አዘጋጁ፣ ከሕዝቤም መንገድ ዕንቅፋትን አውጡ ይላል።” (ኢሳይያስ 57:14) አምላክ ሕዝቡን ነፃ የሚያወጣበት ጊዜ ሲደርስ እንቅፋቱ ሁሉ ተወግዶ ጥርጊያው ይዘጋጃል።​—⁠2 ዜና መዋዕል 36:​22, 23

18. ይሖዋ እጅግ ከፍ ያለ መሆኑ የተገለጸው እንዴት ነው? ይሁንና ምን ፍቅራዊ አሳቢነት አሳይቷል?

18 ነቢዩ ኢሳይያስ መግቢያችን ላይ የተጠቀሱትን ቃላት የዘገበው እዚህ ነጥብ ላይ ሲደርስ ነው:- “ለዘላለም የሚኖር ስሙም ቅዱስ የሆነ፣ ከፍ ያለው ልዑል እንዲህ ይላል:- የተዋረዱትን ሰዎች መንፈስ ሕያው አደርግ ዘንድ፣ የተቀጠቀጠውንም ልብ ሕያው አደርግ ዘንድ፣ የተቀጠቀጠና የተዋረደ መንፈስ ካለው ጋር በከፍታና በተቀደሰ ስፍራ እቀመጣለሁ።” (ኢሳይያስ 57:15) የይሖዋ ዙፋን የሚገኘው በሰማየ ሰማያት ነው። ከዚያ የበለጠ ከፍታ ያለው ቦታ የለም። ከዚያ ሆኖ ማንኛውንም ነገር ማለትም ክፉዎች የሚሠሩትን ኃጢአት ብቻ ሳይሆን እሱን ለማገልገል የሚጣጣሩ ሰዎች የሚያከናውኗቸውን የጽድቅ ሥራዎችም እንደሚመለከት ማወቃችን ምንኛ የሚያጽናና ነው! (መዝሙር 102:​19፤ 103:​6) ጭቆና የደረሰባቸው ሰዎች የሚያሰሙትን የሲቃ ድምፅ የሚሰማ ከመሆኑም በላይ የተሰበረ ልብ ያላቸውን ሰዎች መንፈስ ያነቃቃል። እነዚህ ቃላት በጥንት ዘመን የነበሩትን ንስሐ የገቡ አይሁዳውያን ልብ በእጅጉ ነክተው መሆን አለበት። በዚህ ዘመን ያለነውንም ሰዎች ልብ እንደሚነኩ ጥርጥር የለውም።

19. የይሖዋ ቁጣ የሚበርደው መቼ ነው?

19 ይሖዋ ቀጥሎ የተናገራቸው ቃላትም በጣም የሚያጽናኑ ናቸው:- “መንፈስም የፈጠርሁትም ነፍስ ከፊቴ እንዳይዝል ለዘላለም አልጣላም፣ ሁልጊዜም አልቈጣም።” (ኢሳይያስ 57:16) የይሖዋ ቁጣ ዘላለማዊና ማብቂያ የሌለው ቢሆን ኖሮ ከአምላክ ፍጥረታት መካከል በሕይወት መቀጠል የሚችል አይኖርም ነበር። ደግነቱ ግን የአምላክ ቁጣ የሚቆየው ለተወሰነ ጊዜ ነው። አንዴ ዓላማውን ካከናወነ በኋላ ቁጣው ይበርዳል። በአምላክ መንፈስ የተገለጠውን ይህን ጥልቅ ማስተዋል ማግኘታችን ይሖዋ ለፍጥረታቱ ያለውን ፍቅር በእጅጉ እንድናደንቅ ይገፋፋናል።

20. (ሀ) ይሖዋ ንስሐ የማይገባ ኃጢአተኛን በተመለከተ ያለው አቋም ምንድን ነው? (ለ) ይሖዋ በድርጊቱ የተጸጸተውን ሰው የሚያጽናናው እንዴት ነው?

20 ይሖዋ አክሎ የተናገረውን ቃል ስንመለከት ደግሞ ሌላ ተጨማሪ ማስተዋል እናገኛለን። በመጀመሪያ እንዲህ አለ:- “ስለ ኃጢአቱ [“ኀጢአት ስለ ሞላበት ስግብግብነቱ፣” አ.መ.ት ] ጥቂት ጊዜ ተቈጥቼ ቀሠፍሁት፣ ፊቴን ሰውሬ ተቈጣሁ፤ እርሱም በልቡ መንገድ እያፈገፈገ ሄደ።” (ኢሳይያስ 57:17) በስግብግብነት የተፈጸመ ኃጢአት አምላክን እንደሚያስቆጣው የታወቀ ነው። አንድ ሰው ልቡ እስካልተመለሰ ድረስ የይሖዋ ቁጣ አይበርድም። ይሁን እንጂ ከይሖዋ ሥርዓት ያፈገፈገው ሰው ቅጣቱን ተቀብሎ ቢስተካከልስ? በዚህ ጊዜ ይሖዋ በፍቅርና በርኅራኄ ተገፋፍቶ የሚወስደውን እርምጃ እንዲህ ሲል ገልጿል:- “መንገዱን አይቻለሁ እፈውሰውማለሁ፣ እመራውማለሁ፣ ለእርሱና ስለ እርሱም ለሚያለቅሱ መጽናናትን እመልሳለሁ።” (ኢሳይያስ 57:18) ይሖዋ የቅጣት እርምጃ ከወሰደ በኋላ በድርጊቱ የተጸጸተውን ሰው የሚፈውሰው ከመሆኑም በላይ እሱንም ሆነ ለእርሱ የሚያለቅሱትን ያጽናናል። በ537 ከዘአበ አይሁዳውያን ወደ ትውልድ አገራቸው መመለስ የቻሉት ለዚህ ነው። እርግጥ ነው፣ ከዚያን ጊዜ በኋላ ይሁዳ የዳዊት ዘር በሆነ ንጉሥ የምትመራ ሉዓላዊት አገር መሆን አልቻለችም። ያም ሆኖ በኢየሩሳሌም የነበረው ቤተ መቅደስ ዳግመኛ የተገነባ ከመሆኑም ሌላ እውነተኛው አምልኮ እንደገና ተቋቁሟል።

21. (ሀ) ይሖዋ በ1919 የቅቡዓን ክርስቲያኖችን መንፈስ ያነቃቃው እንዴት ነው? (ለ) በግለሰብ ደረጃ የትኛውን ባሕርይ ማዳበር ይኖርብናል?

21 ‘ከፍ ያለው ልዑሉ’ አምላክ ይሖዋ በ1919 በምድር ላይ ለነበሩት ቅቡዓን ቀሪዎች ደህንነትም ያለውን አሳቢነት አሳይቷል። በቀድሞ ድርጊታቸው በመጸጸታቸውና የትሕትና መንፈስ በማሳየታቸው ታላቁ አምላክ ይሖዋ የደረሰባቸውን መከራ በመመልከት ከባቢሎናዊ ግዞት ነፃ አወጣቸው። ንጹሕ አምልኮ ሊያቀርቡለት እንዲችሉ እንቅፋቶቹን ሁሉ በማስወገድ ወደ ነፃነት ጎዳና መራቸው። በዚህ መንገድ ይሖዋ በኢሳይያስ በኩል የተናገራቸው ቃላት በዚያ ወቅት ፍጻሜያቸውን ሊያገኙ ችለዋል። እነዚህ ቃላት እያንዳንዳችን ልንሠራባቸው የሚገቡ ዘላለማዊ የሆኑ መሠረታዊ ሥርዓቶችን የያዙ ናቸው። ይሖዋ የሚቀበለው ትሑት የሆኑ ሰዎች የሚያቀርቡትን አምልኮ ብቻ ነው። በተጨማሪም አንድ የአምላክ አገልጋይ ኃጢአት ቢሠራ ወዲያውኑ ስህተቱን ማመን፣ የሚሰጠውን ወቀሳ መቀበልና አካሄዱን ማስተካከል አለበት። ይሖዋ ትሑታንን እንደሚፈውስና እንደሚያጽናና፣ ‘ትዕቢተኞችን ግን እንደሚቃወም’ ፈጽሞ አንዘንጋ።​—⁠ያዕቆብ 4:​6

‘በሩቅም ሆነ በቅርብ ላለው ሰላም ይሁን’

22. ይሖዋ (ሀ) ንስሐ የሚገቡ ሰዎች (ለ) ክፉዎች ምን እንደሚገጥማቸው ተንብዮአል?

22 ይሖዋ ንስሐ የሚገቡ ሰዎች የሚገጥማቸውን ሁኔታ በክፉ መንገዳቸው የሚገፉ ሰዎች ከሚገጥማቸው ዕጣ ጋር በማነጻጸር እንዲህ አለ:- “የከንፈሮችን ፍሬ እፈጥራለሁ፤ በሩቅም በቅርብም ላለው ሰላም ሰላም ይሁን፣ እፈውሰውማለሁ፣ . . . ክፉዎች ግን እንደሚንቀሳቀስ ባሕር ናቸው፤ ጸጥ ይል ዘንድ አይችልምና፣ ውኆቹም ጭቃና ጉድፍ ያወጣሉና። ለክፉዎች ሰላም የላቸውም።”​—⁠ኢሳይያስ 57:19-21

23. የከንፈሮች ፍሬ የተባለው ምንድን ነው? ይሖዋ ይህን ፍሬ ‘የሚፈጥረውስ’ በምን መንገድ ነው?

23 የከንፈሮች ፍሬ የተባለው ለአምላክ የሚቀርብ የምስጋና መሥዋዕት ማለትም ለስሙ የሚደረግ ምሥክርነት ነው። (ዕብራውያን 13:​15) ይሖዋ ይህን ለሰዎች የሚሰጥ ምሥክርነት ‘የሚፈጥረው’ እንዴት ነው? አንድ ሰው የምስጋና መሥዋዕት ለማቅረብ በቅድሚያ ስለ አምላክ መማርና በእርሱ ማመን ያስፈልገዋል። የአምላክ መንፈስ ፍሬ የሆነው እምነት ግለሰቡ የሰማውን ለሌሎች እንዲናገር ይገፋፋዋል። በሌላ አባባል በሕዝብ ፊት ምሥክርነት ይሰጣል። (ሮሜ 10:​13-15፤ ገላትያ 5:​22) በተጨማሪም አገልጋዮቹ ምስጋናውን እንዲናገሩ የሚልካቸው ይሖዋ እንደሆነ መዘንጋት የለበትም። እንዲሁም ሕዝቡን ነፃ በማውጣት እንዲህ ያለ የምስጋና መሥዋዕት እንዲያቀርቡ የሚያስችላቸው ይሖዋ ነው። (1 ጴጥሮስ 2:​9) በመሆኑም ይህን የከንፈሮች ፍሬ የሚፈጥረው ይሖዋ ነው ሊባል ይችላል።

24. (ሀ) የአምላክን ሰላም የሚያገኙት እነማን ናቸው? ይህስ ምን ውጤት ይኖረዋል? (ለ) የአምላክን ሰላም የማያገኙት እነማን ናቸው? ይህስ ምን ውጤት ያስከትላል?

24 አይሁዳውያን ወደ ትውልድ አገራቸው ሲመለሱ ለይሖዋ የውዳሴ መዝሙር በመዘመር እጅግ አስደሳች የሆነ የከንፈሮች ፍሬ ያቀርባሉ። “በሩቅ” ሆነው ማለትም ከይሁዳ ርቀው ወደ ትውልድ አገራቸው የሚመለሱበትን ጊዜ እየተጠባበቁም ይሁን “በቅርብ” ሆነው ማለትም በትውልድ አገራቸው የአምላክን ሰላም ማግኘታቸው ከፍተኛ ደስታ ይሰጣቸዋል። ክፉዎች የሚገጥማቸው ሁኔታ ግን ከዚህ እጅግ የተለየ ነው! የይሖዋን የቅጣት እርምጃ ተቀብለው የማይስተካከሉ በየትም ሥፍራ የሚኖሩ ክፉዎች በሙሉ ፈጽሞ ሰላም አያገኙም። እንደሚንቀሳቀስ ባሕር በመናወጥ የከንፈሮች ፍሬ ሳይሆን “ጭቃና ጉድፍ” ይኸውም ቆሻሻ የሆነ ነገር ያፈራሉ።

25. በሁሉም ሥፍራ የሚገኙ ሰዎች ሰላም እያገኙ ያሉት እንዴት ነው?

25 በዛሬው ጊዜም የይሖዋ አምላኪዎች የአምላክን መንግሥት ምሥራች በሁሉም ቦታ ያውጃሉ። በዓለም ዙሪያ ከ230 በሚበልጡ አገሮች የሚገኙ ክርስቲያኖች እውነተኛውን አንድ አምላክ በማወደስ የከንፈሮቻቸውን ፍሬ ያቀርባሉ። የውዳሴ መዝሙራቸው ‘ከምድር ዳርቻ’ ይሰማል። (ኢሳይያስ 42:​10-12) የይሖዋ ምሥክሮች የሚያውጁትን ቃል ሰምተው አዎንታዊ ምላሽ የሚሰጡ ሰዎች የአምላክ ቃል የሆነውን የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት እየተቀበሉ ነው። እነዚህ ሰዎች ‘ሰላም የሚሰጠውን አምላክ’ በማገልገል ሰላም እያገኙ ነው።​—⁠ሮሜ 16:​20

26. (ሀ) ክፉዎች ምን ይጠብቃቸዋል? (ለ) ገሮች ምን ታላቅ ተስፋ ተሰጥቷቸዋል? ውሳኔያችንስ ምን መሆን ይገባዋል?

26 ክፉዎች የመንግሥቱን መልእክት እንደማይቀበሉ የታወቀ ነው። ሆኖም የጻድቃንን ሰላም እያደፈረሱ እንዲኖሩ አይፈቀድላቸውም። በቅርቡ አምላክ እርምጃ ይወስድባቸዋል። ይሖዋ “ገና ጥቂት፣ ኃጢአተኛም አይኖርም” ሲል ቃል ገብቷል። ይሖዋን መጠጊያቸው የሚያደርጉ ሰዎች አስደናቂ በሆነ መንገድ ምድርን ይወርሳሉ። “ገሮች ግን ምድርን ይወርሳሉ፣ በብዙም ሰላም ደስ ይላቸዋል።” (መዝሙር 37:​10, 11, 29) በዚያን ጊዜ ምድራችን እጅግ አስደሳች መኖሪያ ትሆናለች! ሁላችንም የአምላክን ውዳሴ ለዘላለም ዓለም መዘመር እንችል ዘንድ የአምላክን ሰላም እንዳናጣ ቁርጥ ውሳኔ እናድርግ።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.6 “መኝታ” የሚለው ቃል አረማዊ አምልኮ የሚፈጸምበትን መሠዊያ አሊያም ቦታ የሚያመለክት መሆን አለበት። መኝታ ተብሎ መጠራቱ እንዲህ ያለው አምልኮ መንፈሳዊ ግልሙትና እንደሆነ እንድናስተውል ያደርገናል።

^ አን.8 የማምለኪያ ዐፀዶች አንስታይ ጾታን የሚወክሉ ሊሆኑ ይችላሉ። የማምለኪያ ሐውልቶቹ ደግሞ የወንድ ብልት ተምሳሌቶች ሊሆኑ ይችላሉ። ከሃዲ የሆኑት የይሁዳ ነዋሪዎች ሁለቱንም ለአምልኮ ይጠቀሙባቸው ነበር።​—⁠2 ነገሥት 18:​4፤ 23:​14

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 263 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ይሁዳ በለመለመ ዛፍ ሁሉ በታች ወራዳ የሆነ አምልኮ ፈጽማለች

[በገጽ 267 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ይሁዳ በመላ ምድሪቱ መሠዊያ ሠርታለች

[በገጽ 275 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

“የከንፈሮችን ፍሬ እፈጥራለሁ”