በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ለሰዎች የሚያበስሩት ምሥራች

ለሰዎች የሚያበስሩት ምሥራች

ለሰዎች የሚያበስሩት ምሥራች

ኢየሱስ ምድር ላይ በነበረበት ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ወደ እሱ ቀርበው ‘የመገኘትህና የዚህ ሥርዓት መደምደሚያ ምልክት ምንድን ነው?’ ብለው ጠይቀውት ነበር። ኢየሱስም ሲመልስላቸው ብዙ ብሔራት የሚካፈሉባቸው ጦርነቶች፣ ረሃብ፣ ቸነፈርና የምድር ነውጥ እንደሚኖር፣ ክፋት እንደሚስፋፋ፣ ሐሰተኛ የሃይማኖት አስተማሪዎች ብዙዎችን እንደሚያሳስቱ፣ እውነተኛ ተከታዮቹ እንደሚጠሉና ስደት እንደሚደርስባቸው እንዲሁም ብዙዎች ለጽድቅ ያላቸው ፍቅር እንደሚቀዘቅዝ ተናግሮ ነበር። እነዚህ ነገሮች መከሰታቸው ክርስቶስ በማይታይ ሁኔታ መገኘቱንና የአምላክ መንግሥት መቅረቡን የሚያሳይ ምልክት ይሆናል። በእርግጥም ይህ ሊነገር የሚገባው ምሥራች ነው! ስለሆነም ኢየሱስ “ይህ የመንግሥቱ ምሥራች ለሕዝቦች ሁሉ ምሥክር እንዲሆን በመላው ምድር ይሰበካል፤ ከዚያም መጨረሻው ይመጣል” በማለት የምልክቱን ተጨማሪ ክፍል ተናግሯል።—ማቴዎስ 24:3-14

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዓለም ላይ እየተከናወኑ ያሉት ነገሮች በራሳቸው ጥሩ ባይሆኑም የሚያመለክቱት ነገር ጥሩ ነው፤ ምክንያቱም እነዚህ ነገሮች የሚያመለክቱት የክርስቶስን መገኘት ነው። ከላይ የተጠቀሱት ነገሮች መፈጸም የጀመሩት ብዙ በተነገረለት ዓመት ማለትም በ1914 ነው! ይህ ዓመት የአሕዛብ ዘመን አልቆ ከሰብዓዊ አገዛዝ ወደ ክርስቶስ የሺህ ዓመት ግዛት የሚያሸጋግረው ዘመን የጀመረበት ዓመት ነው።

መዝሙር 110:1, 2 እንዲሁም ራእይ 12:7-12 የሽግግር ዘመን እንደሚኖር ይጠቁማሉ። ክርስቶስ ንጉሥ የሚሆንበት ጊዜ እስኪደርስ በሰማይ በአምላክ ቀኝ ተቀምጦ እንደሚቆይ ተገልጿል። ከዚያ በኋላ በሰማይ ጦርነት ይደረግና ሰይጣን ወደ ምድር ይጣላል፤ ይህም በምድር ላይ ወዮታ ያስከትላል፤ ክርስቶስም በጠላቶቹ መካከል መግዛት ይጀምራል። ‘ታላቁ መከራ’ በአርማጌዶን ጦርነት የሚደመደም ሲሆን በዚህ ወቅት ክፋት ሙሉ በሙሉ ተጠራርጎ ይጠፋል፤ ከዚያም የክርስቶስ የሺህ ዓመት የሰላም ግዛት ይጀምራል።—ማቴዎስ 24:21, 33, 34፤ ራእይ 16:14-16

ከዚህም ሌላ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “በመጨረሻዎቹ ቀኖች ለመቋቋም የሚያስቸግር በዓይነቱ ልዩ የሆነ ዘመን እንደሚመጣ ይህን እወቅ። ምክንያቱም ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ፣ ገንዘብ የሚወዱ፣ ጉረኞች፣ ትዕቢተኞች፣ ተሳዳቢዎች፣ ለወላጆች የማይታዘዙ፣ የማያመሰግኑ፣ ታማኝ ያልሆኑ፣ ተፈጥሯዊ ፍቅር የሌላቸው፣ ለመስማማት ፈቃደኞች ያልሆኑ፣ ስም አጥፊዎች፣ ራሳቸውን የማይገዙ፣ ጨካኞች፣ ጥሩ ነገር የማይወዱ፣ ከዳተኞች፣ ግትሮች፣ በኩራት የተወጠሩ፣ አምላክን ከመውደድ ይልቅ ሥጋዊ ደስታን የሚወዱ ይሆናሉ፤ ለአምላክ ያደሩ መስለው ይታያሉ፣ ኃይሉን ግን ይክዳሉ፤ ከእነዚህ ደግሞ ራቅ።”—2 ጢሞቴዎስ 3:1-5

አንዳንዶች እነዚህ ነገሮች ድሮም የነበሩ ናቸው ብለው ይከራከሩ ይሆናል፤ ይሁን እንጂ ይህን በሚያክል መጠንና ስፋት ተከስተው አያውቁም። የታሪክ ተመራማሪዎችና ተንታኞች ከ1914 ወዲህ ያለው ዘመን ከዚያ በፊት ከነበሩት ዘመናት ሁሉ በዓይነቱ እጅግ የተለየ እንደሆነ ይናገራሉ። (ገጽ 7⁠ን ተመልከት።) በምድር ላይ ከምንጊዜውም ይበልጥ መጠነ ሰፊ የሆኑ ችግሮች ተከስተዋል። ከዚህም በላይ ክርስቶስ ስለ መጨረሻው ዘመን ሲናገር ከዘረዘራቸው ሌሎች የምልክቱ ገጽታዎች ጋር በተያያዘ የሚከተሉትን እውነታዎች ልብ ማለት ይገባል፦ ስለ ክርስቶስ መገኘትና ስለ መንግሥቱ የሚታወጀው መልእክት ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ በምድር ዙሪያ በስፋት ተዳርሷል። የይሖዋ ምሥክሮች ይህን መልእክት በመስበካቸው ምክንያት ይህ ነው የማይባል ስደት ደርሶባቸዋል። በመቶዎች የሚቆጠሩ የይሖዋ ምሥክሮች በናዚ የማጎሪያ ካምፖች ውስጥ ተገድለዋል። ዛሬም በአንዳንድ አገሮች የይሖዋ ምሥክሮች እገዳ ተጥሎባቸዋል፤ በሌሎች አገሮች ደግሞ ይታሰራሉ፣ ብዙ ሥቃይ ይደርስባቸዋል እንዲሁም ይገደላሉ። እነዚህ ሁሉ ኢየሱስ ስለ መጨረሻው ዘመን የተናገረው ምልክት ገጽታዎች ናቸው።

በ⁠ራእይ 11:18 ላይ ያለው ትንቢት እንደሚገልጸው ሕዝቦች በይሖዋ ታማኝ ምሥክሮች ላይ ‘ተቆጥተዋል፤’ ይህ ደግሞ የይሖዋ “ቁጣ” በእነዚህ ሕዝቦች ላይ ሊወርድ እንደተቃረበ ያመለክታል። ይኸው ጥቅስ አምላክ ‘ምድርን እያጠፉ ያሉትን እንደሚያጠፋ’ ይናገራል። ምድር በላይዋ ላይ ያሉትን ፍጥረታት በሕይወት የማቆየት አቅሟ የአሁኑን ያህል አደጋ ላይ የወደቀበት ጊዜ የለም። የአሁኑ ፈጽሞ የተለየ ነው! ብዙ ሳይንቲስቶች የሰው ልጅ ምድርን መበከሉን ካላቆመ ምድር ጨርሶ ሕይወት አልባ እንደምትሆን አስጠንቅቀዋል። ይሁን እንጂ ይሖዋ ‘ምድርን ያበጃት የሰው መኖሪያ እንድትሆን ነው፤’ በመሆኑም ምድርን እየበከሉ ያሉ ሰዎች ፕላኔታችንን ሙሉ በሙሉ ከማበላሸታቸው በፊት ያጠፋቸዋል።—ኢሳይያስ 45:18

የአምላክ መንግሥት በምድር ላይ የሚያመጣቸው በረከቶች

ሰዎች የአምላክ መንግሥት ተገዥዎች ሆነው ምድር ላይ ይኖራሉ የሚለው ሐሳብ፣ የዳኑ ሁሉ ወደ ሰማይ ይሄዳሉ ብለው ለሚያስቡ በርካታ የመጽሐፍ ቅዱስ አማኞች እንግዳ ሊሆን ይችላል። መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ሰማይ የሚሄዱት የተወሰነ ቁጥር ያላቸው ብቻ እንደሆኑ፣ ምድር ላይ ለዘላለም የሚኖሩት ግን ቁጥራቸው ያልተወሰነ እጅግ ብዙ ሰዎች እንደሆኑ ያመለክታል። (መዝሙር 37:11, 29፤ ራእይ 7:9፤ 14:1-5) የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነው የዳንኤል መጽሐፍ በክርስቶስ የሚተዳደረው የአምላክ መንግሥት ምድርን እንደሚሞላ ብሎም እንደሚገዛ ይጠቁማል።

በዚህ መጽሐፍ ላይ የክርስቶስ መንግሥት የይሖዋን ሉዓላዊነት ከሚወክል ተራራ ተፈንቅሎ በወጣ ድንጋይ ተመስሏል። ይህ ድንጋይ የምድርን ኃያላን ብሔራት የሚወክለውን ምስል መትቶ አደቀቀው፤ “ምስሉን የመታው ድንጋይ . . . ታላቅ ተራራ ሆነ፤ ምድርንም ሞላ።” ትንቢቱ በመቀጠል እንዲህ ይላል፦ “በነዚያ ነገሥታት ዘመን፣ የሰማይ አምላክ ፈጽሞ የማይፈርስና ለሌላም ሕዝብ የማይሰጥ መንግሥት ይመሠርታል፤ እነዚያን መንግሥታት ሁሉ ያደቃል፤ እስከ መጨረሻውም ያጠፋቸዋል፤ ይህ መንግሥት ራሱ ግን ለዘላለም ጸንቶ ይኖራል።”—ዳንኤል 2:34, 35, 44

የይሖዋ ምሥክሮች ሊነግሩህ የሚፈልጉት ስለዚህ መንግሥት ነው፤ በተጨማሪም የሰው ልጆች በጸዳችና በተዋበች ምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ እንዳላቸው የሚገልጸውን የመጽሐፍ ቅዱስ መልእክት ሊነግሩህ ይፈልጋሉ። በአሁኑ ጊዜ በሕይወት ያሉ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችና በመቃብር ውስጥ የሚገኙ በብዙ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሙታን በዚህች ምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ አላቸው። ያን ጊዜ ይሖዋ ምድርን የፈጠረበትና የመጀመሪያዎቹን ሰብዓዊ ጥንዶች ምድር ላይ ያኖረበት የመጀመሪያ ዓላማ በክርስቶስ ኢየሱስ የሺህ ዓመት ግዛት ሥር ፍጻሜውን ያገኛል። በዚህ ምድራዊ ገነት ውስጥ መኖር ፈጽሞ አሰልቺ አይሆንም። አዳም በኤደን ገነት ውስጥ የሚሠራው ሥራ ተሰጥቶት እንደነበረ ሁሉ የሰው ልጆችም ምድርንና በምድር ላይ የሚኖሩትን ዕፅዋትና እንስሳት የመንከባከብ አስደሳች ሥራ ይጠብቃቸዋል። “በእጃቸው ሥራ ለረጅም ዘመን ደስ ይላቸዋል።”—ኢሳይያስ 65:22፤ ዘፍጥረት 2:15

ኢየሱስ “መንግሥትህ ይምጣ። ፈቃድህ በሰማይ እየሆነ እንዳለ ሁሉ በምድርም ላይ ይሁን” በማለት እንድንጸልይ ያስተማረን ጸሎት በሚፈጸምበት ጊዜ የሚኖረውን ሁኔታ የሚያሳዩ ብዙ ጥቅሶች መጥቀስ ይቻላል። (ማቴዎስ 6:10) ለአሁኑ ግን ከእነዚህ ጥቅሶች መካከል አንዱን ብቻ መመልከት በቂ ነው፦ “ከዙፋኑ አንድ ታላቅ ድምፅ እንዲህ ሲል ሰማሁ:- ‘እነሆ፣ የአምላክ ድንኳን ከሰዎች ጋር ነው፤ እሱም ከእነሱ ጋር ይኖራል፤ እነሱም ሕዝቦቹ ይሆናሉ። አምላክ ራሱም ከእነሱ ጋር ይሆናል። እሱም እንባን ሁሉ ከዓይኖቻቸው ላይ ይጠርጋል፤ ከእንግዲህ ወዲህ ሞት አይኖርም፤ ሐዘንም ሆነ ጩኸት እንዲሁም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይኖርም። ቀድሞ የነበሩት ነገሮች አልፈዋል።’ በዙፋኑም ላይ የተቀመጠው ‘እነሆ፣ ሁሉንም ነገር አዲስ አደርጋለሁ’ አለ። ደግሞም ‘እነዚህ ቃላት እምነት የሚጣልባቸውና እውነት ስለሆኑ ጻፍ’ አለ።”—ራእይ 21:3-5

[በገጽ 15 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

“ለመቋቋም የሚያስቸግር በዓይነቱ ልዩ የሆነ ዘመን”፤

ይሁንና ‘ከዚያ በኋላ መጨረሻው ይመጣል’

[በገጽ 18 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ኔዘርላንድ

[በገጽ 18 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ናይጄሪያ