በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ተቀናቃኞቹ ነገሥታት በ20ኛው መቶ ዘመን

ተቀናቃኞቹ ነገሥታት በ20ኛው መቶ ዘመን

ምዕራፍ አሥራ አምስት

ተቀናቃኞቹ ነገሥታት በ20ኛው መቶ ዘመን

1. አንድ ታሪክ ጸሐፊ በ19ኛው መቶ ዘመን የነበረችው አውሮፓ መሪ ነበሩ ያሏቸው እነማንን ነው?

“በአሥራ ዘጠነኛው መቶ ዘመን የነበረችው አውሮፓ አቻ የማይገኝለት የለውጥ እንቅስቃሴ አድርጋለች” ሲሉ ታሪክ ጸሐፊው ኖርማን ዴቪስ ዘግበዋል። አያይዘውም “አውሮፓ ከዚያ በፊት ታይቶ በማያውቅ መጠን ቴክኖሎጂያዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ባሕላዊና ክፍለ አሕጉራዊ እንቅስቃሴዎች በማድረግ ተጠምዳ ነበር” ብለዋል። ዴቪስ እንዳሉት ከሆነ “አውሮፓውያን ከፍተኛ ድል የተቀዳጁበት ‘የኃይል ዘመን’ መሪዎች ሆነው ብቅ ያሉት በመጀመሪያ ታላቋ ብሪታንያ . . . በኋለኞቹ አሥርተ ዓመታት ደግሞ ጀርመን ናቸው።”

“ክፋትን ያደርጉ ዘንድ በልባቸው ያስባሉ”

2. አሥራ ዘጠነኛው መቶ ዘመን ሲያበቃ “የሰሜን ንጉሥ” እና “የደቡብ ንጉሥ” የሆኑት የትኞቹ ኃይሎች ናቸው?

2 አሥራ ዘጠነኛው መቶ ዘመን ወደ ፍጻሜው እየተቃረበ ሲመጣ የጀርመን ግዛት “የሰሜን ንጉሥ” ብሪታንያ ደግሞ “የደቡብ ንጉሥ” ሆነው ነበር። (ዳንኤል 11:14, 15) የይሖዋ መልአክ “እነዚህም ሁለት ነገሥታት ክፋትን ያደርጉ ዘንድ በልባቸው ያስባሉ፣ በአንድ ገበታም ተቀምጠው ሐሰት ይናገራሉ” ካለ በኋላ “ነገር ግን ፍጻሜው እስከተወሰነው ጊዜ ነውና አይከናወንላቸውም” ብሏል።—ዳንኤል 11:27

3, 4. (ሀ) የጀርመን ራይክ የመጀመሪያው ንጉሠ ነገሥት የሆነው ማን ነበር? ምንስ ኅብረት ፈጠረ? (ለ) ቄሣር ቪልሄልም ምን ፖሊሲ ተከትሏል?

3 ቀዳማዊ ቪልሄልም ጥር 18 ቀን 1871 የጀርመን ራይክ ወይም ግዛት የመጀመሪያው ንጉሠ ነገሥት ሆነ። ኦቶ ቮን ቢስማርክንም ቻንስለር አድርጎ ሾመው። ቢስማርክ ትኩረት ያደረገው አዲሱን ግዛት በማጎልበት ላይ ስለነበር ከሌሎች ብሔራት ጋር የነበረውን ቅራኔ ወደጎን በመተው ከኦስትሪያ-ሃንጋሪና ከኢጣሊያ ጋር ትሪፕል አሊያንስ በመባል የሚታወቅ ሕብረት ፈጠረ። ይሁን እንጂ ብዙም ሳይቆይ የዚህ አዲስ የሰሜን ንጉሥ ፍላጎት ከደቡቡ ንጉሥ ፍላጎቶች ጋር የሚቃረን ሆኗል።

4 ከቀዳማዊ ቪልሄልምና እርሱን ከተካው ከሳልሳዊ ፍሬድሪክ ሞት (1888) በኋላ የ29 ዓመቱ ዳግማዊ ቪልሄልም ዙፋኑን ተቆናጠጠ። ዳግማዊ ቪልሄልም ወይም ቄሣር ቪልሄልም ቢስማርክ ሥልጣኑን እንዲለቅ በማስገደድ ጀርመን በዓለም መድረክ ላይ ያላትን ተጽዕኖ የሚያስፋፋ ፖሊሲ ማራመድ ጀመረ። አንድ ታሪክ ጸሐፊ እንዳሉት “በዳግማዊ ቪልሄልም አመራር [ጀርመን] የዕብሪተኛነትና የጠብ ጫሪነት መንፈስ አራምዳለች።”

5. ሁለቱ ነገሥታት ‘በአንድ ማዕድ’ የተቀመጡት እንዴት ነው? ምንስ ተነጋገሩ?

5 የሩሲያው ዛር ዳግማዊ ኒኮላስ ነሐሴ 24, 1898 በኔዘርላንድስ ዘ ሄግ ከተማ አንድ የሰላም ኮንፈረንስ እንዲደረግ ሲጠራ ወቅቱ ዓለም አቀፍ ውጥረት የነገሠበት ነበር። ይህ ኮንፈረንስና በ1907 የተደረገው ቀጣዩ ኮንፈረንስ ቋሚ የዳኝነት ችሎት ዘ ሄግ ውስጥ አቋቁሟል። የጀርመኑ ራይክና ታላቋ ብሪታንያ የዚህ ችሎት አባላት ሆነው በአንድ ጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጠው ስለነበር ለሰላም የቆሙ መስለው ታይተዋል። ሰላማውያን መስለው ‘በአንድ ገበታ ዙሪያ’ ይቀመጡ እንጂ ‘በልባቸው የሚያስቡት ግን ክፋትን’ ነበር። ‘በአንድ ገበታ ተቀምጦ የመዋሸት’ ዲፕሎማሲያዊ ስልት እውነተኛ ሰላም ለማምጣት የሚፈይደው ነገር የለም። የሁለቱ ነገሥታት ፍጻሜ ‘ይሖዋ እስከወሰነው ጊዜ’ በመሆኑ በፖለቲካው፣ በንግዱና በወታደራዊ መስክ የሚጓጉለት ነገር ምንም ‘አይከናወንላቸውም።’

‘በተቀደሰው ቃል ኪዳን ላይ ይነሳል’

6, 7. (ሀ) የሰሜኑ ንጉሥ ‘ወደ ምድሩ የተመለሰው’ በምን መንገድ ነው? (ለ) የደቡብ ንጉሥ ለሰሜን ንጉሥ የመስፋፋት እንቅስቃሴ ምላሽ የሰጠው እንዴት ነው?

6 የአምላክ መልአክ በመቀጠል እንዲህ ብሏል:- “[የሰሜንም ንጉሥ] ከብዙም ሀብት ጋር ወደ ምድሩ ይመለሳል፣ ልቡም በተቀደሰው ቃል ኪዳን ላይ ይሆናል፤ ፈቃዱንም ያደርጋል፣ ወደ ገዛ ምድሩም ይመለሳል።”—ዳንኤል 11:28

7 ቄሣር ቪልሄልም ወደ ‘ምድሩ’ ወይም በምድር ወደ ተመሰለው የጥንቱ የሰሜን ንጉሥ ሁኔታ ይመለሳል። እንዴት? የጀርመንን ራይክ ለማስፋፋትና የተጽዕኖውንም አድማስ ለማስፋት በማሰብ ንጉሠ ነገሥታዊ አገዛዝ በመገንባት ነው። ዳግማዊ ቪልሄልም የቅኝ ግዛት ዓላማ ይዞ በአፍሪካና በሌሎች ቦታዎችም ተንቀሳቅሷል። ብሪታንያ በባሕር ላይ ያላትን የበላይነት ለመቀናቀን በማሰብ ጠንካራ የባህር ኃይል መገንባቱን ተያይዞት ነበር። ዘ ኒው ኢንሳይክለፒዲያ ብሪታኒካ እንዳለው “የጀርመን የባሕር ኃይል ከተናቀበት ዝቅተኛ ደረጃ ተነሥቶ ከአሥር ዓመታት ብዙም በማይበልጥ ጊዜ ውስጥ ከብሪታንያ ቀጥሎ ያለውን ደረጃ ለመያዝ በቅቷል።” ብሪታንያም የበላይነቷን ለማስጠበቅ የባሕር ኃይሏን ይበልጥ ማጠናከር አስፈልጓት ነበር። በተጨማሪም ብሪታንያ ኦንቶንት ኮርዲያል (በጋራ መተሳሰብ ላይ የተመሠረተ መግባባት) የተባለውን ውል ከፈረንሳይና ከሩሲያ ጋር በመፈራረሟ ትሪፕል ኦንቶንት የተባለው ጥምረት ሊመሠረት ችሏል። በዚህ ወቅት አውሮፓ በሁለት ወታደራዊ ጎራዎች ማለትም በትሪፕል አላያንስ እና በትሪፕል ኦንቶንት ተከፈለች።

8. የጀርመን ግዛት ‘ብዙ ሀብት’ ሊያገኝ የቻለው እንዴት ነው?

8 የጀርመን ግዛት ይከተለው የነበረው የወራሪነት ፖሊሲ የትሪፕል አላያንስ ዋነኛ ክፍል ለሆነችው ጀርመን ‘ብዙ ሀብት’ አስገኝቷል። ኦስትሪያ-ሃንጋሪና ኢጣሊያ የሮማ ካቶሊኮች ናቸው። በመሆኑም ትሪፕል አላያንስ የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱን ትኩረት ሲያገኝ የደቡብ ንጉሥ ግን አብዛኛው የትሪፕል ኦንቶንት ክፍል ካቶሊክ ባለመሆኑ ይህን ትኩረት ሳያገኝ ቀርቷል።

9. የሰሜን ንጉሥ ልቡን ‘በተቀደሰው ቃል ኪዳን’ ላይ ያደረገው እንዴት ነው?

9 ስለ ይሖዋ ሕዝቦችስ ምን ማለት ይቻላል? “የተቀጠረው የብሔራት ዘመን” በ1914 እንደሚያበቃ ከረጅም ጊዜ አንስቶ ሲያስታውቁ ነበር። * (ሉቃስ 21:24 NW) በዚያው ዓመት የዳዊት ወራሽ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ የሚተዳደረው የአምላክ መንግሥት በሰማይ ተቋቁሟል። (2 ሳሙኤል 7:12-16፤ ሉቃስ 22:28, 29) ከመጋቢት 1880 አንስቶ መጠበቂያ ግንብ መጽሔት የአምላክን መንግሥት ግዛት ‘ከተቀጠረው የብሔራት ዘመን’ ወይም “ከአሕዛብ ዘመናት” (እንደ 1954 ትርጉም) ፍጻሜ ጋር አያይዞ ሲገልጸው ቆይቷል። ይሁን እንጂ የጀርመኑ የሰሜን ንጉሥ ‘ልብ በተቀደሰው የመንግሥት ቃል ኪዳን ላይ ነበር።’ ቄሣር ቪልሄልም የአምላክን መንግሥት አገዛዝ አምኖ ከመቀበል ይልቅ በምድር ላይ የበላይ የመሆን ምኞቱን በማራመድ ‘እንደ ፈቃዱ አድርጓል።’ ይሁንና ይህን በማድረጉ የአንደኛው የዓለም ጦርነት ዘር እንዲዘራ አድርጓል።

ንጉሡ በጦርነት ‘አዝኖ ተመለሰ’

10, 11. አንደኛው የዓለም ጦርነት የተጀመረው እንዴት ነው? ይህስ ‘በተወሰነው ጊዜ’ የሆነው እንዴት ነበር?

10 መልአኩ እንዲህ ሲል ተንብዮአል:- “[የሰሜን ንጉሥ] በተወሰነውም ጊዜ ይመለሳል ወደ ደቡብም ይመጣል፤ ነገር ግን ኋለኛው እንደ ፊተኛው አይሆንም።” (ዳንኤል 11:29) አሕዛብ በምድር ላይ ያላቸውን የበላይነት ወደ ፍጻሜው ለማምጣት አምላክ ‘የወሰነው ጊዜ’ ያበቃው በ1914 ሰማያዊ መንግሥቱን በሰማይ ባቋቋመ ጊዜ ነው። በዚያው ዓመት ሰኔ 28 ቀን የኦስትሪያው አርክዱክ ፍራንሲስ ፈርዲናንድና ሚስቱ በሳራየቮ ቦስኒያ በሰርብ ሽብርተኞች እጅ ተገደሉ። የአንደኛውን የዓለም ጦርነት እሳት የጫረው ድርጊት ይህ ነበር።

11 ቄሣር ቪልሄልም ኦስትሪያ-ሃንጋሪ በሰርቢያ ላይ የበቀል እርምጃ እንድትወስድ አጥብቆ አሳሰበ። ኦስትሪያ-ሃንጋሪም የጀርመን ድጋፍ እንደማይለያት በመተማመን ሐምሌ 28 ቀን 1914 በሰርቢያ ላይ ጦርነት አወጀች። ይሁን እንጂ ሩሲያ ሰርቢያን መርዳት ጀመረች። ጀርመን በሩሲያ ላይ ጦርነት ስታውጅ ደግሞ (በትሪፕል ኦንቶንት ውስጥ የታቀፈችው) ፈረንሳይ ሩሲያን ረዳቻት። ከዚያም ጀርመን በፈረንሳይ ላይ ጦርነት አወጀች። ጀርመን ፓሪስን በቀላሉ ለመቆጣጠር እንዲያመቻት ስትል ከገለልተኛ አቋሟ የተነሣ የብሪታንያ ዋስትና የነበራትን ቤልጂየምን ወረረች። በመሆኑም ብሪታንያ በጀርመን ላይ ጦርነት አወጀች። በጦርነቱ ሌሎች አገሮች የተካፈሉ ሲሆን ኢጣሊያ ደግሞ የተሰለፈችበትን ጎራ ቀይራለች። ብሪታንያ በጦርነቱ ወቅት የሰሜኑ ንጉሥ የጥንቱ የደቡብ ንጉሥ ግዛት የነበረችውን ግብጽን በመውረር የስዊዝ ቦይን እንዳይዘጋባት ለመጠበቅ ስትል ግብጽን በሞግዚትነት ማስተዳደር ጀመረች።

12. በአንደኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ‘ሁኔታዎቹ እንደ ፊተኛው’ ሳይሆኑ የቀሩት እንዴት ነው?

12 ዘ ወርልድ ቡክ ኢንሳይክለፒዲያ እንደሚለው “ጥምር ኃይሉ ምንም ያክል ግዙፍና ጠንካራ ቢሆንም ጀርመን ጦርነቱን ለማሸነፍ የተቃረበች ይመስል ነበር።” ከዚህ ቀደም የሰሜን ንጉሥ የነበረው የሮማ ግዛት በሁለቱ ነገሥታት መካከል በተደረጉት ግጭቶች በተደጋጋሚ ድል ሲቀናው ቆይቷል። በዚህ ጊዜ ግን ‘ሁኔታዎቹ እንደፊተኛው አልሆኑም።’ የሰሜኑ ንጉሥ በጦርነቱ ድል ተነሣ። መልአኩ የዚህን ምክንያት ሲጠቅስ “የኪቲም መርከቦች ይመጡበታልና ስለዚህ አዝኖ ይመለሳል” ብሏል። (ዳንኤል 11:30⁠ሀ) እነዚህ “የኪቲም መርከቦች” ምንድን ናቸው?

13, 14. (ሀ) በሰሜኑ ንጉሥ ላይ የዘመቱት ‘የኪቲም መርከቦች’ በዋነኝነት የሚያመለክቱት ማንን ነው? (ለ) አንደኛው የዓለም ጦርነት እየቀጠለ ሲሄድ ተጨማሪ የኪቲም መርከቦች የመጡት እንዴት ነው?

13 በዳንኤል ዘመን ኪቲም የምትባለው ቆጵሮስ ነበረች። በአንደኛው የዓለም ጦርነት መጀመሪያ አካባቢ ቆጵሮስ በብሪታንያ ተጠቅልላ ነበር። ከዚህም በተጨማሪ ዘ ዞንደርቫን ፒክቶሪያል ኢንሳይክለፒዲያ ኦቭ ዘ ባይብል እንደሚለው ከሆነ ኪቲም የሚለው ስም “በአጠቃላይ [ም]ዕራቡን በተለይ ደግሞ ባሕረተኛውን የ[ም]ዕራብ ክፍል የሚያካትት ሰፊ ትርጉም አለው።” ዘ ኒው ኢንተርናሽናል ቨርሽን “የኪቲም መርከቦች” የሚለውን አገላለጽ “የምዕራባዊው የባሕር ዳርቻ መርከቦች” ብሎ ይተረጉመዋል። በአንደኛው የዓለም ጦርነት ወቅት የኪቲም መርከቦች በአውሮፓ በስተ ምዕራብ የነበሩት የብሪታንያ መርከቦች መሆናቸው ታይቷል።

14 ጦርነቱ በቀጠለ መጠን የብሪታንያ የባሕር ኃይል በተጨማሪ የኪቲም መርከቦች ተጠናክሮ ነበር። ግንቦት 7 ቀን 1915 U-20 የተባለው የጀርመን ሰርጓጅ መርከብ በአየርላንድ ደቡባዊ ዳርቻ የነበረችውን ሉሲቴኒየ የተባለች የሲቪል መርከብ አሰጠመ። ከሞቱት ሰዎች መካከል 128ቱ አሜሪካውያን ነበሩ። ቆየት ብሎም ጀርመን የሰርጓጅ መርከቦች ውጊያዋን ወደ አትላንቲክ አሰፋች። ከዚህ የተነሣ ሚያዝያ 6 ቀን 1917 የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ዉድሮው ዊልሰን በጀርመን ላይ ጦርነት አወጁ። በዩናይትድ ስቴትስ የጦር መርከቦች ይበልጥ የተጠናከረው የደቡብ ንጉሥ ማለትም የአንግሎ አሜሪካ የዓለም ኃይል ከተቀናቃኙ ጋር ወደሚደረገው ጦርነት ሙሉ በሙሉ ገባ።

15. የሰሜኑ ንጉሥ ‘አዝኖ የተመለሰው’ መቼ ነው?

15 የሰሜን ንጉሥ ከአንግሎ አሜሪካ የዓለም ኃይል በደረሰበት ጥቃት ‘አዝኖ’ ኅዳር 1918 ሽንፈቱን አምኖ ለመቀበል ተገድዷል። ዳግማዊ ቪልሄልም በስደት ወደ ኔዘርላንድስ ሲሸሽ ጀርመን ሪፑብሊካዊ መስተዳድር ሆነች። ይሁን እንጂ የሰሜን ንጉሥ አብቅቶለታል ማለት አልነበረም።

ንጉሡ ‘እንደ ፈቃዱ ያደርጋል’

16. በትንቢቱ መሠረት የሰሜን ንጉሥ ሽንፈት ሲገጥመው ምን ያደርጋል?

16 “[የሰሜኑ ንጉሥ] በቅዱሱም ቃል ኪዳን ላይ ይቆጣል፣ ፈቃዱንም ያደርጋል፤ ተመልሶም ቅዱሱን ቃል ኪዳን የተዉትን ሰዎች ይመለከታል።” (ዳንኤል 11:30⁠ለ) መልአኩ የተናገረው ይህ ትንቢት በትክክል ፍጻሜውን አግኝቷል።

17. አዶልፍ ሂትለር ወደ ሥልጣን እንዲወጣ ያበቁት ሁኔታዎች ምን ነበሩ?

17 ጦርነቱ በ1918 ካበቃ በኋላ የድል አድራጊዎቹ ኅብረት ጀርመንን ቅጣት አዘል የሰላም ስምምነት እንድትፈርም አስገድዷታል። የጀርመን ሕዝብ የስምምነቱን ነጥብ ከባድ ሆኖ አግኝቶት የነበረ ሲሆን አዲሱ ሪፑብሊካዊ መንግሥትም ገና ከጅምሩ አንስቶ ደካማ ነበር። ጀርመን ለተወሰኑ ዓመታት በከባድ ችግር ስትውተረተር ቆይታ የኋላ ኋላ 6 ሚልዮን ዜጎቿን ሥራ አጥ ባደረገው ታላቅ ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ተመትታለች። በ1930ዎቹ መጀመሪያ ላይ አዶልፍ ሂትለር ወደ ሥልጣን እንዲወጣ ሁኔታዎቹ ተመቻችተውለት ነበር ለማለት ይቻላል። በጥር 1933 ቻንስለር ሆኖ በቀጣዩ ዓመት ናዚዎቹ ሦስተኛው ራይክ ብለው የሰየሙት ግዛት ፕሬዚዳንት ሆነ። *

18. ሂትለር ‘እንደ ፈቃዱ ያደረገው’ እንዴት ነው?

18 ሂትለር ወደ ሥልጣን ከወጣ በኋላ ብዙም ሳይቆይ በኢየሱስ ክርስቶስ ቅቡዓን ወንድሞች በሚወከለው ‘ቅዱስ ቃል ኪዳን ላይ’ ጠንካራ ጥቃት ሠነዘረ። (ማቴዎስ 25:40) በዚህ መልኩ ብዙዎቹን ጭካኔ በሞላበት መንገድ በማንገላታት በእነዚህ ታማኝ ክርስቲያኖች ላይ ‘እንደ ፈቃዱ አድርጓል።’ ሂትለር በኢኮኖሚያዊና ዲፕሎማሲያዊ መስክ ስኬት በማግኘቱ በዚህ ረገድም ‘እንደ ፈቃዱ አድርጓል’ ለማለት ይቻላል። በጥቂት ዓመታት ውስጥ ጀርመን በዓለም መድረክ ጉልህ ሥፍራ የሚሰጣት ኃይል እንድትሆን አድርጓል።

19. ሂትለር እርዳታ ፍለጋ ወደ ማን ዞር ብሏል?

19 ሂትለር ‘ቅዱሱን ቃል ኪዳኑን የተዉትንም ሰዎች ተመልክቷል።’ እነዚህ እነማን ነበሩ? ከማስረጃዎቹ ለመገንዘብ እንደሚቻለው እነዚህ ከአምላክ ጋር የቃል ኪዳን ዝምድና አለን የሚሉትና የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርት መሆናቸውን የተዉት የሕዝበ ክርስትና መሪዎች ናቸው። ሂትለር ‘ቃል ኪዳኑን የተዉት ሰዎች’ እንዲረዱት ያቀረበው ጥሪ ተቀባይነት አግኝቷል። ለምሳሌ ያህል ከሮማው ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ጋር ስምምነት አድርጓል። ሂትለር በ1935 የአብያተ ክርስቲያናት ጉዳይ ሚንስቴር አቋቁሟል። ዋነኛው ግቡ የወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናትን በመንግሥት ቁጥጥር ሥር ማድረግ ነበር።

ከንጉሡ የሚወጡት ‘ክንዶች’

20. የሰሜኑ ንጉሥ የተጠቀመባቸው ‘ክንዶች’ ምንድን ናቸው? በማንስ ላይ?

20 መልአኩ “ከእርሱም ጋር ሠራዊቶች ይቆማሉ [“ከእርሱ ወጥተው የሚቆሙ ክንዶች ይኖራሉ፣” NW]” በማለት በትክክል እንደተነበየው ሂትለር ብዙም ሳይቆይ ወደ ጦርነት ገብቷል። (ዳንኤል 11:31ሀ) እነዚህ ‘ክንዶች’ የሰሜኑ ንጉሥ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት የደቡቡን ንጉሥ ለመውጋት ያሰለፋቸው ወታደራዊ ኃይሎች ናቸው። መስከረም 1, 1939 የናዚ ‘ክንዶች’ ፖላንድን ወረሩ። ከሁለት ቀናት በኋላ ብሪታንያና ፈረንሳይ ፖላንድን ለመርዳት ሲሉ በጀርመን ላይ ጦርነት አወጁ። በዚህ መንገድ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ተጀመረ። ፖላንድ ወዲያውኑ ፈራረሰች፤ የጀርመን ኃይሎችም ዴንማርክን፣ ኖርዌይን፣ ኔዘርላንድስን፣ ቤልጂየምን፣ ሉክሰምበርግንና ፈረንሳይን ተቆጣጠሩ። ዘ ዎርልድ ቡክ ኢንሳይክለፒዲያ እንደሚለው “በ1941 ማብቂያ ላይ ናዚ ጀርመን አህጉሯን ተቆጣጥሯት ነበር።”

21. በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ሂትለር ከጠበቀው የተገላቢጦሽ የሆነ ነገር የገጠመው እንዴት ነበር? ውጤቱስ ምን ሆነ?

21 ጀርመንና ሶቪየት ኅብረት የወዳጅነት፣ የትብብርና የግዛት አከላለል ስምምነት ተፈራርመው የነበረ ቢሆንም ሂትለር ሰኔ 22, 1941 ቀን የሶቪየትን ክልል ወረረ። ይህም ድርጊት ሶቪየት ኅብረት ከእንግሊዝ ጎን እንድትሰለፍ አድርጓታል። የጀርመን ኃይሎች አስቀድመው ወደፊት ገፍተው የነበረ ቢሆንም የሶቭየት ሠራዊት በሚያስገርም ሁኔታ ተቋቋማቸው። ታኅሣሥ 6 ቀን 1941 የጀርመን ሠራዊት በሞስኮ ሽንፈት ደረሰበት። በቀጣዩ ቀን የጀርመን አጋር የሆነችው ጃፓን የሃዋዩን ፐርል ሃርበር በቦንብ ደበደበች። ይህንን የሰማው ሂትለር ለአጋሮቹ “ከእንግዲህ በምንም ዓይነት ድሉ ከእኛ እጅ አይወጣም” ብሏቸው ነበር። ታኅሣሥ 11 ቀን ተቻኩሎ በዩናይትድ ስቴትስ ላይ ጦርነት አወጀ። ይሁንና የሶቪየት ኅብረትንም ሆነ የዩናይትድ ስቴትስን ኃይል አቃልሎ ተመልክቶት ነበር። የሶቪየት ሠራዊት ከምሥራቅ ሲያጣድፈው የብሪታንያና የአሜሪካ ኃይሎች ደግሞ ከምዕራብ እየገፉ ስለነበር ውጤቱ ሂትለር እንደጠበቀው አልነበረም። የጀርመን ኃይሎች አንድ በአንድ የያዙትን ግዛት እየለቀቁ መጡ። ሂትለር የራሱን ሕይወት ካጠፋ በኋላ ጀርመን ግንቦት 7 ቀን 1945 ለጥምረቱ እጅዋን ሰጠች።

22. የሰሜኑ ንጉሥ ‘ቅድስተ ቅዱሳኑን ያረከሰውና የዘወትሩን መሥዋዕት ያስቀረው’ እንዴት ነው?

22 መልአኩ “[የናዚ ክንዶችም] መቅደሱንም [“ቅድስተ ቅዱሳኑን፣” NW] ግንቡንም ያረክሳሉ፣ የዘወትሩንም መሥዋዕት ያስቀራሉ” ብሏል። በጥንቷ ይሁዳ ቅድስተ ቅዱሳኑ በኢየሩሳሌም የሚገኘው ቤተ መቅደስ ክፍል ነበር። ይሁን እንጂ አይሁዳውያኑ ኢየሱስን ለመቀበል አሻፈረን ባሉ ጊዜ ይሖዋ እነርሱንም ሆነ ቤተ መቅደሳቸውን ትቷቸዋል። (ማቴዎስ 23:37–24:2) እርግጥ ከመጀመሪያው መቶ ዘመን አንስቶ የይሖዋ ቤተ መቅደስ መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ ሆኗል። የዚህ ቤተ መቅደስ ቅድስተ ቅዱሳን በሰማይ ያለ ሲሆን የሊቀ ካህናቱ የኢየሱስ ወንድሞች የሚያገለግሉበት መንፈሳዊ አደባባዩ ደግሞ የሚገኘው በምድር ነው። ከ1930ዎቹ ወዲህ ‘እጅግ ብዙ ሰዎችም’ ከቅቡዓን ቀሪዎቹ ጋር ሆነው እያመለኩ በመሆናቸው ‘በአምላክ ቤተ መቅደስ’ ውስጥ እንደሚያገለግሉ ተደርገው ተገልጸዋል። (ራእይ 7:9, 15፤ 11:1, 2፤ ዕብራውያን 9:11, 12, 24) የሰሜኑ ንጉሥ በእርሱ ቁጥጥር ሥር ባሉት አገሮች በሚገኙት ቅቡዓን ቀሪዎችና ጓደኞቻቸው ላይ ምህረት የለሽ ስደት በማድረስ የቤተ መቅደሱን ምድራዊ አደባባይ አርክሷል። ስደቱ እጅግ ከባድ ከመሆኑ የተነሣ ‘የዘወትሩ መሥዋዕት’ ማለትም ስለ ይሖዋ ስም ለሕዝብ የሚቀርበው የምስጋና መሥዋዕት ተገትቶ ነበር። (ዕብራውያን 13:15) ይሁን እንጂ የታመኑት ቅቡዓን ክርስቲያኖችና ‘ሌሎች በጎች’ ከባድ መከራ ቢደርስባቸውም በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅትም መስበካቸውን ቀጥለዋል።—ዮሐንስ 10:16

‘የጥፋት ርኵሰቱ ብቅ ብሏል’

23. በመጀመሪያው መቶ ዘመን የተነሳው “ርኵሰት” ምንድን ነው?

23 የሁለተኛው የዓለም ጦርነት ማብቂያ ሲቃረብ የአምላክ መልአክ አስቀድሞ እንደተናገረው ሌላ ክስተት ብቅ አለ። “የጥፋትንም ርኵሰት ያቆማሉ።” (ዳንኤል 11:31ለ) ኢየሱስም ስለ ‘ጥፋት ርኵሰት’ ተናግሯል። በመጀመሪያው መቶ ዘመን ይህ የጥፋት ርኵሰት በ66 እዘአ የአይሁዳውያኑን ዓመፅ ለማዳፈን ወደ ኢየሩሳሌም የመጣው የሮማ ሠራዊት ነበር። *ማቴዎስ 24:15፤ ዳንኤል 9:27

24, 25. (ሀ) የዘመናችን ‘የጥፋት ርኵሰት’ ምንድን ነው? (ለ) ‘የጥፋት ርኩሰቱስ ብቅ ያለው’ መቼና እንዴት ነበር?

24 በዚህ ዘመን ‘ብቅ ያለው የጥፋት ርኵሰት’ ምንድን ነው? በአምላክ መንግሥት ቦታ ራሱን ያስቀመጠ አስመሳይ “ርኵሰት” እንደሆነ ግልጽ ነው። ይህ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ሲፈነዳ ወደ ጥልቁ የወረደው ወይም የዓለም የሰላም ድርጅት መሆኑ ያከተመለት የመንግሥታቱ ቃል ኪዳን ማኅበር ነው። (ራእይ 17:8) ይሁን እንጂ ይህ “አውሬ” “ከጥልቁ ይወጣ ዘንድ አለው” ተብሎለታል። ሶቪየት ኅብረትን ጨምሮ 50 አባል መንግሥታት ጥቅምት 24, 1945 የተባበሩት መንግሥታትን ሲያቋቁሙ ይህ ነገር ፍጻሜውን አግኝቷል። በመሆኑም መልአኩ አስቀድሞ የተናገረለት “ርኵሰት” ማለትም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ብቅ ብሏል።

25 ጀርመን በሁለቱም የዓለም ጦርነቶች ወቅት የደቡቡ ንጉሥ ግንባር ቀደም ጠላት የነበረች ሲሆን የሰሜን ንጉሥ ሆና ነበር። ቀጥሎ ይህንን ቦታ የሚይዘው ማን ይሆን?

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

^ አን.9 የዚህን መጽሐፍ 6ኛ ምዕራፍ ተመልከት።

^ አን.17 የመጀመሪያው ራይክ የቅድስቲቷ ሮማ ግዛት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የጀርመን ግዛት ነበር።

^ አን.23 የዚህን መጽሐፍ 11ኛ ምዕራፍ ተመልከት።

ምን አስተውለሃል?

• በ19ኛው መቶ ዘመን መጨረሻ ላይ የሰሜን ንጉሥና የደቡብ ንጉሥ የነበሩት ኃይሎች የትኞቹ ናቸው?

• በአንደኛው የዓለም ጦርነት ወቅት የተነሳው ግጭት ውጤት ለሰሜኑ ንጉሥ ‘እንደ ፊተኛው ሳይሆንለት የቀረው’ እንዴት ነው?

• ሂትለር ከአንደኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ጀርመንን በዓለም መድረክ ላይ ጉልህ ሥፍራ የሚሰጣት ኃይል እንድትሆን ያደረጋት እንዴት ነው?

• በሰሜኑ ንጉሥና በደቡቡ ንጉሥ መካከል በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት የነበረው ቅራኔ መጨረሻው ምን ነበር?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 268 ላይ የሚገኝ ሰንጠረዥ/ሥዕል]

በ⁠ዳንኤል 11:27-31 ላይ የተጠቀሱት ነገሥታት

የሰሜን ንጉሥ የደቡብ ንጉሥ

ዳንኤል 11:27-30⁠ሀ የጀርመን ግዛት የአንግሎ አሜሪካን

(አንደኛው የዓለም ጦርነት) የዓለም ኃይል አስከትላ

ብቅ ያለችው ብሪታንያ

ዳንኤል 11:30⁠ለ, 31 የሂትለር ሦስተኛ ራይክ የአንግሎ አሜሪካ

(ሁለተኛው የዓለም ጦርነት) የዓለም ኃይል

[ሥዕል]

ፕሬዚዳንት ዉድሮው ዊልሰን ከንጉሥ ጆርጅ አምስተኛ ጋር

[ሥዕል]

ብዙ ክርስቲያኖች በማጎሪያ ካምፖች ውስጥ ተንገላትተዋል

[ሥዕል]

በሕዝበ ክርስትና ውስጥ ያሉ መሪዎች ሂትለርን ደግፈዋል

[ሥዕል]

አርክዱክ ፈርዲናንድ ሲገደል ተሳፍሮባት የነበረችው አውቶሞቢል

[ሥዕል]

የጀርመን ወታደሮች በአንደኛው የዓለም ጦርነት

[በገጽ 257 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በ1945 በያልታ የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚንስትር ዊንስተን ቸርችል፣ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ፍራንክሊን ዲ ሩዝቨልት እንዲሁም የሶቪየቱ መሪ ጆሴፍ ስታሊን ተገናኝተው ጀርመንን መያዝን፣ በፖላንድ አዲስ መንግሥት ማቋቋምንና የተባበሩት መንግሥታትን ማቋቋሚያ ኮንፈረንስ ማካሄድን በተመለከተ ተነጋግረዋል

[በገጽ 258 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

1. አርክዱክ ፈርዲናንድ 2. የጀርመን ባሕር ኃይል 3. የብሪታንያ ባሕር ኃይል 4. ሉሲቴኒየ 5. ዩናይትድ ስቴትስ ጦርነት ማወጅዋን የሚገልጸው መግለጫ

[በገጽ 263 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የጀርመን የጦርነት አጋር የሆነችው ጃፓን ፐርል ሃርበርን ከደበደበች በኋላ አዶልፍ ሂትለር ድል እንደሚቀዳጅ እርግጠኛ ሆኖ ነበር