ሕዝቅኤል 16:1-63

  • አምላክ ለኢየሩሳሌም ያለው ፍቅር (1-63)

    • ተጥላ የተገኘች ልጅ (1-7)

    • አምላክ አስዋባት፤ ከእሷም ጋር የጋብቻ ቃል ኪዳን ገባ (8-14)

    • ታማኝ ሳትሆን ቀረች (15-34)

    • በአመንዝራነቷ ተቀጣች (35-43)

    • ከሰማርያና ከሰዶም ጋር ተነጻጸረች (44-58)

    • አምላክ ቃል ኪዳኑን አስታወሰ (59-63)

16  የይሖዋ ቃል ዳግመኛ እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣ፦  “የሰው ልጅ ሆይ፣ ለኢየሩሳሌም አስጸያፊ ልማዶቿን አሳውቃት።+  እንዲህ በል፦ ‘ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ለኢየሩሳሌም እንዲህ ይላል፦ “መገኛሽና ትውልድሽ በከነአናውያን ምድር ነው። አባትሽ አሞራዊ፣+ እናትሽም ሂታዊት ነበሩ።+  አወላለድሽንም በተመለከተ፣ በተወለድሽበት ቀን እትብትሽ አልተቆረጠም፤ ንጹሕም እንድትሆኚ በውኃ አልታጠብሽም፤ በጨውም አልታሸሽም፤ ደግሞም በጨርቅ አልተጠቀለልሽም።  ለአንቺ አዝኖ ከእነዚህ ነገሮች አንዱንም እንኳ ያደረገልሽ የለም። የራራልሽም የለም። ይልቁንም በተወለድሽበት ቀን ስለተጠላሽ* አውላላ ሜዳ ላይ ተጣልሽ።  “‘“በአጠገብሽ ሳልፍ በደምሽ ላይ ስትንፈራገጪ አየሁሽ፤ ደግሞም በደምሽ ላይ ተኝተሽ ሳለ ‘በሕይወት ኑሪ!’ አልኩሽ። አዎ፣ በደምሽ ላይ ተኝተሽ ሳለ ‘በሕይወት ኑሪ!’ አልኩሽ።  በሜዳ ላይ እንደሚበቅሉ ዕፀዋት እጅግ እንድትበዢ አደረግኩ፤ አንቺም አደግሽ፤ ደግሞም ሙሉ ሰው ሆንሽ፤ እጅግ ያማረ ጌጥም አደረግሽ። ጡቶችሽ አጎጠጎጡ፤ ፀጉርሽም አደገ፤ ይሁንና በዚህ ጊዜም እርቃንሽንና ራቁትሽን ነበርሽ።”’  “‘በአጠገብሽ ሳልፍ አየሁሽ፤ የፍቅር ግንኙነት ለመጀመር ዕድሜሽ እንደደረሰ አስተዋልኩ። ስለዚህ ልብሴን* በአንቺ ላይ ዘርግቼ+ እርቃንሽን ሸፈንኩ፤ ደግሞም ማልኩልሽ፤ ከአንቺም ጋር ቃል ኪዳን አደረግኩ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ፤ ‘አንቺም የእኔ ሆንሽ።  በተጨማሪም በውኃ አጠብኩሽ፤ ከደምሽም አነጻሁሽ፤ ዘይትም ቀባሁሽ።+ 10  ከዚያም የተጠለፈ ሸማ አለበስኩሽ፤ ከጥሩ ቆዳ* የተሠራ ጫማም ሰጠሁሽ፤ በጥሩ በፍታም ጠቀለልኩሽ፤ እጅግ ውድ የሆነ ልብስም አለበስኩሽ። 11  በጌጣጌጥ አንቆጠቆጥኩሽ፤ በእጆችሽ አምባር፣ በአንገትሽም ሐብል አጠለቅኩልሽ። 12  በተጨማሪም በአፍንጫሽ ቀለበት፣ በጆሮዎችሽ ጉትቻ፣ በራስሽም ላይ የሚያምር አክሊል አደረግኩልሽ። 13  ራስሽን በወርቅና በብር አስጌጥሽ፤ ልብስሽም ጥሩ በፍታ፣ እጅግ ውድ በሆነ ጨርቅ የተሠራና የተጠለፈ ሸማ ነበር። ምግብሽም የላመ ዱቄት፣ ማርና ዘይት ነበር፤ እጅግ ውብ ሆንሽ፤+ ንግሥት ለመሆንም* በቃሽ።’” 14  “‘ከውበትሽ የተነሳ ዝናሽ* በብሔራት መካከል ገነነ፤+ ውበትሽ በአንቺ ላይ ካኖርኩት ግርማዬ የተነሳ ፍጹም ሆኖ ነበርና’+ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።” 15  “‘ሆኖም አንቺ በውበትሽ መመካት ጀመርሽ፤+ ዝናሽንም ለዝሙት አዳሪነት ተጠቀምሽበት።+ ከአላፊ አግዳሚው ጋር ያለገደብ አመነዘርሽ፤+ ውበትሽንም ለማንም አሳልፈሽ ሰጠሽ። 16  የተለያዩ ቀለማት ካሏቸው ልብሶችሽ አንዳንዶቹን ወስደሽ የምታመነዝሪባቸውን ከፍ ያሉ የማምለኪያ ቦታዎችሽን አስጌጥሽባቸው፤+ እነዚህ ነገሮች መሆን የለባቸውም፤ ጨርሶ ሊፈጸሙም አይገባም። 17  ደግሞም በሰጠሁሽ ወርቅና ብር የተሠሩትን ያማሩ ጌጣጌጦችሽን ወስደሽ ለራስሽ የወንድ ምስሎች ሠራሽ፤ ከእነሱም ጋር አመነዘርሽ።+ 18  የተጠለፉ ሸማዎችሽንም ወስደሽ አለበስሻቸው፤* ዘይቴንና ዕጣኔንም አቀረብሽላቸው።+ 19  ደግሞም እንድትበዪው የሰጠሁሽን ከላመ ዱቄት፣ ከዘይትና ከማር የተዘጋጀ ምግብ ደስ የሚያሰኝ* መዓዛ አድርገሽ አቀረብሽላቸው።+ የተፈጸመው ነገር ይኸው ነው’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።” 20  “‘ለእኔ የወለድሻቸውን ወንዶችና ሴቶች ልጆችሽን+ ወስደሽ መብል ይሆኑ ዘንድ ለጣዖቶቹ ሠዋሽላቸው፤+ የምትፈጽሚው ምንዝር እጅግ አልበዛም? 21  ወንዶች ልጆቼን አረድሽ፤ በእሳትም አሳልፈሽ መሥዋዕት አድርገሽ አቀረብሻቸው።+ 22  አስጸያፊ ልማዶችሽንና ምንዝርሽን ሁሉ ስትፈጽሚ እርቃንሽንና ራቁትሽን ሆነሽ በገዛ ደምሽ ላይ ስትንፈራገጪ የነበርሽበትን የልጅነትሽን ጊዜ አላስታወስሽም። 23  ይህን ሁሉ ክፋት ከፈጸምሽ በኋላ ወዮ፣ ወዮልሽ’+ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ። 24  ‘ለራስሽ ጉብታ አበጀሽ፤ በየአደባባዩም ከፍ ያለ ቦታ ሠራሽ። 25  በየመንገዱ ላይ በሚገኝ የታወቀ ስፍራ ሁሉ ከፍ ያለ ቦታ ሠራሽ፤ ለአላፊ አግዳሚው ሁሉ ራስሽን በመስጠት*+ ውበትሽን ወደ አስጸያፊ ነገር ለወጥሽ፤ የምትፈጽሚውንም ምንዝር አበዛሽ።+ 26  በፍትወት ከተቃጠሉ ጎረቤቶችሽ* ይኸውም ከግብፅ ወንዶች ልጆች ጋር አመነዘርሽ፤+ ገደብ በሌለው ምንዝርሽ አስቆጣሽኝ። 27  አሁን እጄን በአንቺ ላይ እዘረጋለሁ፤ ቀለብሽንም እቀንሳለሁ፤+ በጸያፍ ተግባርሽ የተነሳ የሚሸማቀቁትና የሚጠሉሽ ሴቶች ይኸውም የፍልስጤም ሴቶች ልጆች ያሻቸውን እንዲያደርጉብሽ አሳልፌ እሰጥሻለሁ።+ 28  “‘እርካታ ባለማግኘትሽ ከአሦር ወንዶች ልጆች ጋር ደግሞ አመነዘርሽ፤+ ሆኖም ከእነሱ ጋር ካመነዘርሽ በኋላም እንኳ አልረካሽም። 29  ስለዚህ ምንዝርሽን በነጋዴዎች* ምድርና በከለዳውያን ምድር አበዛሽ፤+ ያም ሆኖ እንኳ አልረካሽም። 30  ዓይን አውጣ እንደሆነች ዝሙት አዳሪ+ ይህን ሁሉ ነገር የፈጸምሽው ልብሽ ምንኛ ታማሚ* ቢሆን ነው!’* ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ። 31  ‘ይሁንና በየመንገዱ ላይ በሚገኝ የታወቀ ስፍራ ሁሉ ጉብታሽን ስታበጂና በየአደባባዩ ለራስሽ ከፍ ያለ ቦታ ስትሠሪ እንደ ዝሙት አዳሪ አልሆንሽም፤ ምክንያቱም ምንም ዓይነት ክፍያ አትቀበዪም። 32  አንቺ በባሏ ፋንታ እንግዳ የሆኑ ሰዎችን የምታስተናግድ አመንዝራ ሚስት ነሽ!+ 33  ሰዎች ለዝሙት አዳሪዎች ሁሉ ስጦታ ይሰጣሉ፤+ በፍትወት ለሚመኙሽ ሁሉ ስጦታ የሰጠሽው ግን አንቺ ነሽ፤+ ደግሞም ከየቦታው መጥተው ከአንቺ ጋር እንዲያመነዝሩ ጉቦ ትሰጫቸዋለሽ።+ 34  አንቺ ከሌሎች ዝሙት አዳሪ ሴቶች ፈጽሞ የተለየሽ ነሽ። አንቺ የፈጸምሽው ዓይነት ምንዝር የፈጸመ ሰው ታይቶ አይታወቅም! አንቺ ትከፍያቸዋለሽ እንጂ እነሱ አይከፍሉሽም። የአንቺ አድራጎት ተቃራኒ ነው።’ 35  “በመሆኑም አንቺ ዝሙት አዳሪ፣+ የይሖዋን ቃል ስሚ። 36  ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘ከፍቅረኞችሽና የወንዶች ልጆችሽን ደም መሥዋዕት አድርገሽ ካቀረብሽላቸው+ አስጸያፊና ቀፋፊ ጣዖቶችሽ*+ ሁሉ ጋር ባመነዘርሽ ጊዜ ከልክ በላይ በፍትወት ስለተቃጠልሽና እርቃንሽ ስለተገለጠ፣ 37  እኔ ደስ ያሰኘሻቸውን ፍቅረኞችሽን ሁሉ፣ የወደድሻቸውንም ሆነ የጠላሻቸውን ሁሉ አንድ ላይ እሰበስባለሁ። እነሱን ከየቦታው በአንቺ ላይ እሰበስባቸዋለሁ፤ እርቃንሽን ለእነሱ እገልጣለሁ፤ እነሱም ሙሉ በሙሉ እርቃንሽን ሆነሽ ያዩሻል።+ 38  “‘አመንዝሮችና ደም የሚያፈሱ ሴቶች+ ሊፈረድባቸው በሚገባው ፍርድ እቀጣሻለሁ፤+ ደግሞም በቁጣና በቅናት ደምሽ ይፈስሳል።+ 39  በእጃቸው አሳልፌ እሰጥሻለሁ፤ እነሱም ጉብታዎችሽን ያፈርሳሉ፤ ከፍ ያሉ ቦታዎችሽንም ያወድማሉ፤+ ልብሶችሽንም ይገፉሻል፤+ ያማሩ ጌጣጌጦችሽንም ይወስዳሉ፤+ እርቃንሽንና ራቁትሽንም ያስቀሩሻል። 40  ብዙ ሰዎችን ያነሳሱብሻል፤+ በድንጋይም ይወግሩሻል፤+ በሰይፋቸውም ያርዱሻል።+ 41  ቤቶችሽን በእሳት ያቃጥላሉ፤+ በብዙ ሴቶችም ፊት በአንቺ ላይ ፍርዴን ይፈጽማሉ፤ ምንዝርሽንም አስተውሻለሁ፤+ ከእንግዲህም ወዲህ ዋጋ አትከፍዪም። 42  በአንቺ ላይ የነበረው ቁጣዬ ይበርዳል፤+ ንዴቴም ከአንቺ ይርቃል።+ እኔም እረጋጋለሁ፤ ከእንግዲህም አልቆጣም።’ 43  “‘የልጅነት ጊዜሽን ስላላስታወስሽና+ እነዚህን ነገሮች ሁሉ በማድረግ ስላስቆጣሽኝ እኔም የተከተልሽው መንገድ የሚያስከትለውን መዘዝ በራስሽ ላይ አመጣብሻለሁ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ፤ ‘አንቺም ከእንግዲህ ወዲህ አስነዋሪ ምግባርሽንና አስጸያፊ የሆኑ ልማዶችሽን ሁሉ አትፈጽሚም። 44  “‘እነሆ፣ ምሳሌያዊ አባባል የሚጠቀም ሁሉ “ልጅቷም በእናቷ ወጣች!”+ እያለ ይተርትብሻል። 45  አንቺ የእናትሽ ልጅ ነሽ፤ እሷ ባሏንና ልጆቿን ትንቃለች። ደግሞም ባሎቻቸውንና ልጆቻቸውን የናቁት የእህቶችሽ እህት ነሽ። እናታችሁ ሂታዊት፣ አባታችሁ ደግሞ አሞራዊ ነበሩ።’”+ 46  “‘ታላቅ እህትሽ ከሴቶች ልጆቿ*+ ጋር ከአንቺ በስተ ሰሜን* የምትኖረው ሰማርያ ናት፤+ ታናሽ እህትሽም ከሴቶች ልጆቿ ጋር ከአንቺ በስተ ደቡብ* የምትኖረው ሰዶም ናት።+ 47  በእነሱ መንገድ መሄድና የእነሱን አስጸያፊ ልማዶች መከተል ብቻ ሳይሆን በጥቂት ጊዜ ውስጥ በምግባርሽ ሁሉ ከእነሱ ይበልጥ ብልሹ ሆንሽ።+ 48  በሕያውነቴ እምላለሁ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ፣ ‘አንቺና ሴቶች ልጆችሽ ያደረጋችሁትን እህትሽ ሰዶምና ሴቶች ልጆቿ አላደረጉትም። 49  እነሆ፣ የእህትሽ የሰዶም በደል ይህ ነበር፦ እሷና ሴቶች ልጆቿ+ ኩራተኞች ነበሩ፤+ የተትረፈረፈ ምግብ የነበራቸው+ ሲሆን ያለጭንቀት ተረጋግተው ይኖሩ ነበር፤+ ይሁንና ጎስቋላውንና ድሃውን አልደገፉም።+ 50  እነሱም ትዕቢታቸውን አላስወገዱም፤+ በፊቴም አስጸያፊ የሆኑ ልማዶችን መፈጸማቸውን ቀጠሉ፤+ በመሆኑም እነሱን ማስወገድ ተገቢ ሆኖ አገኘሁት።+ 51  “‘ሰማርያም+ ብትሆን አንቺ የሠራሽውን ኃጢአት ግማሹን እንኳ አልሠራችም። አንቺ ከምትፈጽሚያቸው አስጸያፊ ልማዶች ሁሉ የተነሳ እህቶችሽ ጻድቃን መስለው እስኪታዩ ድረስ ከእነሱ ይበልጥ ብዙ አስጸያፊ ልማዶች መፈጸምሽን ቀጠልሽ።+ 52  የእህቶችሽ ምግባር ተገቢ መስሎ እንዲታይ ስላደረግሽ* አሁን ኀፍረትሽን ተከናነቢ። ከእነሱ ይበልጥ አስጸያፊ በሆነ መንገድ ከፈጸምሽው ኃጢአት የተነሳ እነሱ ከአንቺ ይልቅ ጻድቃን ሆነዋል። እንግዲህ እህቶችሽን ጻድቃን ስላስመሰልሻቸው ኀፍረት ተከናነቢ፤ ውርደትሽንም ተሸከሚ።’ 53   “‘በምርኮ የተወሰዱባቸውን ይኸውም ከሰዶምና ከሴቶች ልጆቿ የተማረኩትን እንዲሁም ከሰማርያና ከሴቶች ልጆቿ የተማረኩትን እሰበስባለሁ፤ በተጨማሪም ከአንቺ የተማረኩትን ከእነሱ ጋር እሰበስባለሁ፤+ 54  ይህም የሚሆነው ውርደትሽን እንድትሸከሚ ነው፤ ደግሞም እነሱን በማጽናናት ባደረግሽው ነገር የተነሳ ውርደት ትከናነቢያለሽ። 55  የገዛ እህቶችሽ፣ ሰዶምና ሴቶች ልጆቿ ወደ ቀድሞ ሁኔታቸው ይመለሳሉ፤ እንዲሁም ሰማርያና ሴቶች ልጆቿ ወደ ቀድሞ ሁኔታቸው ይመለሳሉ፤ አንቺና ሴቶች ልጆችሽም ቀድሞ ወደነበራችሁበት ሁኔታ ትመለሳላችሁ።+ 56  ኩሩ በነበርሽበት ቀን እህትሽ ሰዶም በአንደበትሽ ለመጠራት እንኳ የምትበቃ አልነበረችም፤ 57   ይህም የሆነው ክፋትሽ ከመጋለጡ በፊት ነበር።+ አሁን ግን የሶርያ ሴቶች ልጆችና ጎረቤቶቿ በአንቺ ላይ ነቀፋ ይሰነዝራሉ፤ እንዲሁም የፍልስጤማውያን+ ሴቶች ልጆች፣ በዙሪያሽም ያሉ ሁሉ በንቀት ያዩሻል። 58  አስነዋሪ ምግባርሽና አስጸያፊ ልማዶችሽ የሚያስከትሉብሽን መዘዝ ትቀበያለሽ’ ይላል ይሖዋ።” 59  “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላልና፦ ‘እንግዲህ ቃል ኪዳኔን በማፍረስ መሐላውን ስለናቅሽ+ እኔም እንዳደረግሽው አደርግብሻለሁ።+ 60  ይሁንና እኔ ራሴ በልጅነትሽ ጊዜ ከአንቺ ጋር የገባሁትን ቃል ኪዳን አስታውሳለሁ፤ ደግሞም ከአንቺ ጋር ዘላቂ ቃል ኪዳን አደርጋለሁ።+ 61  ታላላቆችሽና ታናናሾችሽ የሆኑትን እህቶችሽን ስትቀበዪ ምግባርሽን ታስታውሻለሽ፤ ደግሞም ታፍሪያለሽ፤+ እኔም እነሱን ሴቶች ልጆች አድርጌ እሰጥሻለሁ፤ ይህን የማደርገው ግን ከአንቺ ጋር በገባሁት ቃል ኪዳን የተነሳ አይደለም።’ 62  “‘እኔ ራሴም ከአንቺ ጋር የገባሁትን ቃል ኪዳን አጸናለሁ፤ አንቺም እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ታውቂያለሽ። 63  ከዚያም፣ ያን ሁሉ ነገር ብታደርጊም እንኳ ለአንቺ ባስተሰረይኩልሽ ጊዜ ሥራሽን ታስታውሻለሽ፤+ ከደረሰብሽም ውርደት የተነሳ አፍሽን ለመክፈት እጅግ ታፍሪያለሽ’+ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።”

የግርጌ ማስታወሻዎች

ወይም “ነፍስሽ ስለተጠላች።”
ወይም “ቀሚሴን።”
ወይም “የአቆስጣ ቆዳ።”
ወይም “ንጉሣዊ ሥልጣን ለመቀበልም።”
ቃል በቃል “ስምሽ።”
የወንድ ጣዖቶቹን ያመለክታል።
ወይም “የሚያረጋጋ፤ የሚያበርድ።” ቃል በቃል “እረፍት የሚሰጥ።”
ቃል በቃል “እግሮችሽን በመክፈት።”
ቃል በቃል “ትልቅ ሥጋ ካላቸው ጎረቤቶችሽ።”
ቃል በቃል “በከነአን።”
ወይም “ደካማ።”
“ይህን ሁሉ ነገር ስትፈጽሚ በአንቺ ላይ ምንኛ እቆጣ!” ማለትም ሊሆን ይችላል።
እዚህ ላይ የገባው የዕብራይስጥ ቃል “ፋንድያ” ከሚለው ቃል ጋር ዝምድና ሊኖረው የሚችል ሲሆን ንቀትን ለማመልከት ተሠርቶበታል።
ቃል በቃል “በስተ ቀኝሽ።”
ቃል በቃል “በስተ ግራሽ።”
በዙሪያዋ ያሉትን ከተሞች ሊያመለክት ይችላል።
ወይም “ለእነሱ ስለተከራከርሽ።”