ሕዝቅኤል 23:1-49

  • ታማኝ ያልሆኑ ሁለት እህትማማቾች (1-49)

    • ኦሆላ ከአሦር ጋር አመነዘረች (5-10)

    • ኦሆሊባ ከባቢሎንና ከግብፅ ጋር አመነዘረች (11-35)

    • በሁለቱ እህትማማቾች ላይ የተላለፈ የቅጣት ፍርድ (36-49)

23  የይሖዋ ቃል ዳግመኛ እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣ፦  “የሰው ልጅ ሆይ፣ ከአንድ እናት የተወለዱ ሁለት ሴቶች ነበሩ።+  እነሱም በግብፅ ዝሙት አዳሪዎች ሆኑ፤+ ከወጣትነታቸው ጊዜ ጀምሮ አመነዘሩ። በዚያም ጡታቸው ተሻሸ፤ የድንግልናቸውም ጉያ ተዳበሰ።  የታላቂቱ ስም ኦሆላ፣* የእህቷም ስም ኦሆሊባ* ነበር። እነሱም የእኔ ሆኑ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆችም ወለዱ። ስማቸውን በተመለከተ፣ ኦሆላ ሰማርያ+ ስትሆን ኦሆሊባ ደግሞ ኢየሩሳሌም ናት።  “ኦሆላ የእኔ ሆና ሳለች ታመነዝር ጀመር።+ ጎረቤቶቿ የሆኑትን ፍቅረኞቿን+ አሦራውያንን በፍትወት ተመኘች።+  እነሱ ሰማያዊ ልብስ የለበሱ ገዢዎችና የበታች ገዢዎች ሲሆኑ ሁሉም መልከ ቀና ወጣቶች እንዲሁም ፈረሰኞች ነበሩ።  እሷ ምርጥ ከሆኑት የአሦር ልጆች ሁሉ ጋር ማመንዘሯን ቀጠለች፤ ደግሞም በፍትወት የምትመኛቸው ሰዎች በሚያመልኳቸው አስጸያፊ ጣዖቶች* ራሷን አረከሰች።+  በግብፅ ትፈጽመው የነበረውን ምንዝር አልተወችም፤ እነሱ በወጣትነቷ ከእሷ ጋር ተኝተዋልና፤ የድንግልናዋን ጉያ ዳብሰዋል እንዲሁም ፍትወታቸውን በእሷ ላይ አፍስሰዋል።*+  ስለዚህ በፍትወት ለተመኘቻቸው፣ ፍቅረኞቿ ለሆኑት አሦራውያን አሳልፌ ሰጠኋት።+ 10  እነሱ እርቃኗን ገለጡ፤+ ወንዶችና ሴቶች ልጆቿን ማረኩ፤+ እሷንም በሰይፍ ገደሏት። በሴቶች መካከል መጥፎ ስም አተረፈች፤ እነሱም የፍርድ እርምጃ ወሰዱባት። 11  “እህቷ ኦሆሊባ ይህን ስትመለከት ፍትወቷ እጅግ የከፋ ሆነ፤ አመንዝራነቷም ከእህቷ የባሰ ሆነ።+ 12  ጎረቤቶቿ የሆኑትን የአሦርን ልጆች በፍትወት ተመኘች፤+ እነሱ ያማረ ልብስ የለበሱ ገዢዎችና የበታች ገዢዎች እንዲሁም ፈረሰኞች ሲሆኑ ሁሉም መልከ ቀና ወጣቶች ነበሩ። 13  እሷ ራሷን ባረከሰች ጊዜ ሁለቱም በአንድ መንገድ እንደሄዱ ተገነዘብኩ።+ 14  ይሁን እንጂ እሷ በአመንዝራነቷ ገፋችበት። በግድግዳው ላይ የተቀረጹትን የወንድ ምስሎች ይኸውም ቀይ ቀለም የተቀቡትን የከለዳውያን የተቀረጹ ምስሎች አየች፤ 15  እነሱ ወገባቸው ላይ ቀበቶ ታጥቀዋል፤ በራሳቸውም ላይ የተንዘረፈፈ ጥምጥም አድርገዋል፤ ደግሞም ተዋጊዎች ይመስላሉ፤ ሁሉም በከለዳውያን ምድር የተወለዱትን ባቢሎናውያን ያመለክታሉ። 16  እሷም እነሱን እንዳየቻቸው በፍትወት ትመኛቸው ጀመር፤ ወደ ከለዳውያንም ምድር መልእክተኞች ላከችባቸው።+ 17  በመሆኑም የባቢሎን ልጆች ከእሷ ጋር ለመተኛት ወደ እሷ መምጣታቸውን ቀጠሉ፤ በፍትወታቸውም* አረከሷት። በእነሱ ከረከሰች በኋላ ተጸይፋቸው* ከእነሱ ራቀች። 18  “በማንአለብኝነት ማመንዘሯንና እርቃኗን መግለጧን በቀጠለች ጊዜ+ እህቷን ተጸይፌ* እንደራቅኳት ሁሉ እሷንም ተጸይፌ ራቅኳት።+ 19  እሷ ግን በግብፅ ምድር ስታመነዝር+ የነበረበትን የወጣትነቷን ዘመን በማስታወስ በአመንዝራነቷ ይባስ ገፋችበት።+ 20  ብልታቸው እንደ አህያ ብልት፣ አባለዘራቸውም እንደ ፈረስ አባለዘር በሆኑ ወንዶች የተያዙ ቁባቶች እንደሚያደርጉት እሷም በፍትወት ተመኘቻቸው። 21  በግብፅ ምድር ጉያሽን በዳበሱበት፣ የወጣትነትሽንም ጡቶች ባሻሹበት ጊዜ በወጣትነትሽ ትፈጽሚው የነበረውን ጸያፍ ምግባር ተመኘሽ።+ 22  “ስለዚህ ኦሆሊባ ሆይ፣ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘ተጸይፈሽ* የራቅሻቸውን ፍቅረኞችሽን በአንቺ ላይ አስነሳለሁ፤+ እነሱንም ከየአቅጣጫው አመጣብሻለሁ፤+ 23  እነሱም የባቢሎን ልጆችና+ ከለዳውያን+ ሁሉ እንዲሁም የአሦርን ልጆች ሁሉ ጨምሮ የጰቆድ፣+ የሾአ እና የቆአ ሰዎች ናቸው። ሁሉም መልከ ቀና ወጣቶች፣ ገዢዎችና የበታች ገዢዎች፣ ተዋጊዎችና የተመረጡ አማካሪዎች እንዲሁም ፈረሰኞች ናቸው። 24  እነሱም የጦር ሠረገሎችንና መንኮራኩሮችን* ሁሉ እያንጋጉ፣ ትልቅና ትንሽ* ጋሻ የያዘ እንዲሁም የራስ ቁር የደፋ ብዙ ሠራዊት አስከትለው ጥቃት ይሰነዝሩብሻል። በዙሪያሽም ይሰለፋሉ፤ እኔም የመፍረድ ሥልጣን እሰጣቸዋለሁ፤ እነሱም ትክክል መስሎ በታያቸው መንገድ ይፈርዱብሻል።+ 25  እኔም ቁጣዬን በአንቺ ላይ እገልጣለሁ፤ እነሱም በታላቅ ቁጣ እርምጃ ይወስዱብሻል። አፍንጫሽንና ጆሮዎችሽን ይቆርጣሉ፤ ከአንቺም የቀሩት በሰይፍ ይወድቃሉ። ወንዶችና ሴቶች ልጆችሽን ይወስዳሉ፤ ከአንቺም የቀሩት በእሳት ይበላሉ።+ 26  ልብሶችሽን ይገፉሻል፤+ ያማሩ ጌጣጌጦችሽንም ይነጥቁሻል።+ 27  በግብፅ ምድር የጀመርሽው+ ጸያፍ ምግባርና አመንዝራነትሽ እንዲያበቃ አደርጋለሁ።+ ከእንግዲህ ዓይንሽን ወደ እነሱ አታነሺም፤ ግብፅንም አታስታውሺም።’ 28  “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላልና፦ ‘እነሆ፣ ለጠላሻቸው ሰዎች፣ ተጸይፈሽ* ለራቅሻቸው ሰዎች አሳልፌ ልሰጥሽ ነው።+ 29  እነሱ በጥላቻ እርምጃ ይወስዱብሻል፤ የደከምሽበትን ነገር ሁሉ ይወስዳሉ፤+ ራቁትሽንና እርቃንሽን ያስቀሩሻል። የፆታ ብልግና ስትፈጽሚ የተገለጠው አሳፋሪ የሆነው እርቃንሽ፣ ጸያፍ ምግባርሽና አመንዝራነትሽ ይፋ ይወጣል።+ 30  እንደ ዝሙት አዳሪ ብሔራትን ተከትለሽ ስለሄድሽና+ አስጸያፊ በሆኑት ጣዖቶቻቸው ራስሽን ስላረከስሽ+ እነዚህ ነገሮች ሁሉ ይፈጸሙብሻል። 31  የእህትሽን መንገድ ተከትለሻል፤+ ስለዚህ የእሷን ጽዋ አስጨብጥሻለሁ።’+ 32  “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘ጥልቅና ሰፊ የሆነውን የእህትሽን ጽዋ ትጠጫለሽ፤+ደግሞም መሳቂያና መሳለቂያ ትሆኛለሽ፤ ጽዋውም በዚህ የተሞላ ነው።+ 33  በስካርና በሐዘን፣በሽብርና በጥፋት ጽዋ ትዋጫለሽ፤*ይህም የእህትሽ የሰማርያ ጽዋ ነው። 34  ትጠጪዋለሽ፤ ትጨልጪዋለሽ፤+ የጽዋውንም ስብርባሪዎች ትቆረጣጥሚያለሽ፤ከዚያም ጡቶችሽን ትቆርጫለሽ። “እኔ ራሴ ተናግሬአለሁና” ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።’ 35  “ስለዚህ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘ስለረሳሽኝና ጨርሶ ቸል ስላልሽኝ*+ ጸያፍ ምግባርሽና አመንዝራነትሽ የሚያስከትለውን መዘዝ ትቀበያለሽ።’” 36  ከዚያም ይሖዋ እንዲህ አለኝ፦ “የሰው ልጅ ሆይ፣ በኦሆላና በኦሆሊባ+ ላይ ትፈርዳለህ? አስጸያፊ ተግባራቸውንስ ፊት ለፊት ትነግራቸዋለህ? 37  እነሱ አመንዝረዋል፤*+ እጃቸውም በደም ተበክሏል። አስጸያፊ ከሆኑት ጣዖቶቻቸው ጋር ከማመንዘራቸውም በተጨማሪ ለእኔ የወለዷቸውን ልጆች ለጣዖቶቻቸው መብል እንዲሆኑ ለእሳት አሳልፈው ሰጥተዋል።+ 38  በተጨማሪም በእኔ ላይ እንዲህ አድርገዋል፦ በዚያ ቀን መቅደሴን አርክሰዋል፤ ሰንበቶቼንም አቃለዋል። 39  ልጆቻቸውን አስጸያፊ ለሆኑት ጣዖቶቻቸው ከሠዉ+ በኋላ በዚያው ቀን ወደ መቅደሴ መጥተው አረከሱት።+ እንግዲህ በቤቴ ውስጥ ይህን አድርገዋል። 40  አልፎ ተርፎም ከሩቅ ቦታ ወንዶች እንዲመጡላቸው መልእክተኛ ላኩ።+ እነሱ በመጡ ጊዜ ገላሽን ታጠብሽ፤ ዓይንሽን ተኳልሽ፤ በጌጣጌጥም ተዋብሽ።+ 41  እጅግ ባማረ ድንክ አልጋ ላይ ተቀመጥሽ፤+ በፊቱም በተሰናዳ ማዕድ+ ላይ ዕጣኔንና+ ዘይቴን አኖርሽ።+ 42  በዚያም በፈንጠዝያ ላይ ያሉ ብዙ ወንዶች ሁካታ ይሰማ ነበር፤ በመካከላቸውም ከምድረ በዳ የመጡ ሰካራሞች ነበሩ። እነሱም በሴቶቹ እጆች ላይ አምባር አጠለቁ፤ በራሳቸውም ላይ የተዋበ አክሊል አደረጉላቸው። 43  “ከዚያም እኔ ሰውነቷ በምንዝር ስላለቀው ሴት፣ ‘አሁንም ማመንዘሯን ትቀጥላለች’ አልኩ። 44  ሰው ወደ ዝሙት አዳሪ እንደሚሄድ ሁሉ እነሱም ወደ እሷ መሄዳቸውን ቀጠሉ። በዚህ መንገድ፣ ባለጌ ወደሆኑት ወደ ኦሆላና ወደ ኦሆሊባ ገቡ። 45  ጻድቃን ግን ለምንዝርና ለደም አፍሳሽነት የሚገባውን ፍርድ ይፈርዱባታል፤+ እነሱ አመንዝሮች ናቸውና፤ እጃቸውም በደም ተበክሏል።+ 46  “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላልና፦ ‘መቀጣጫ ያደርጋቸውና ለብዝበዛ ይዳርጋቸው ዘንድ በእነሱ ላይ ብዙ ሠራዊት ይሰበሰባል።+ 47  ሠራዊቱ ድንጋይ ይወረውርባቸዋል፤+ በሰይፉም ይቆራርጣቸዋል። ወንዶችና ሴቶች ልጆቻቸውን ይገድላል፤+ ቤቶቻቸውንም በእሳት ያቃጥላል።+ 48  በምድሪቱ ላይ የሚፈጸመው ጸያፍ ምግባር እንዲወገድ አደርጋለሁ፤ ሴቶቹም ሁሉ ከዚህ ይማራሉ፤ የእናንተንም ጸያፍ ምግባር ከመከተል ይርቃሉ።+ 49  የፈጸማችሁት ጸያፍ ምግባር እንዲሁም አስጸያፊ በሆኑት ጣዖቶቻችሁ የሠራችሁት ኃጢአት የሚያስከትለውን መዘዝ እንድትቀበሉ ያደርጋሉ፤ እኔም ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንደሆንኩ ታውቃላችሁ።’”+

የግርጌ ማስታወሻዎች

“ድንኳኔ በእሷ ውስጥ ነው” የሚል ትርጉም አለው።
“የእሷ ድንኳን” የሚል ትርጉም አለው።
እዚህ ላይ የገባው የዕብራይስጥ ቃል “ፋንድያ” ከሚለው ቃል ጋር ዝምድና ሊኖረው የሚችል ሲሆን ንቀትን ለማመልከት ተሠርቶበታል።
ወይም “ከእሷ ጋር የፆታ ብልግና ፈጽመዋል።”
ወይም “የፆታ ብልግና በመፈጸምም።”
ወይም “ነፍሷ ተጸይፋቸው።”
ወይም “ነፍሴ ተጸይፋት።”
ወይም “ነፍስሽ ተጸይፋ።”
የሠረገላ ተሽከርካሪ እግር።
አብዛኛውን ጊዜ ቀስተኞች የሚይዙት ትንሽ ጋሻ።
ወይም “ነፍስሽ ተጸይፋ።”
ቃል በቃል “ትሞያለሽ።”
ቃል በቃል “ወደ ኋላሽ ስለጣልሽኝ።”
መንፈሳዊ ምንዝርን ያመለክታል።