ሕዝቅኤል 36:1-38

  • ስለ እስራኤል ተራሮች የተነገረ ትንቢት (1-15)

  • የእስራኤል ተመልሶ መቋቋም (16-38)

    • ‘ታላቅ ስሜን እቀድሰዋለሁ’ (23)

    • “እንደ ኤደን የአትክልት ስፍራ” (35)

36  “አንተም የሰው ልጅ ሆይ፣ ስለ እስራኤል ተራሮች ትንቢት ተናገር፤ እንዲህም በል፦ ‘የእስራኤል ተራሮች ሆይ፣ የይሖዋን ቃል ስሙ።  ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ጠላት ስለ እናንተ ‘እሰይ! የጥንቶቹ ከፍ ያሉ ቦታዎች ሳይቀሩ የእኛ ርስት ሆነዋል!’ ብሏል።”’+  “ስለዚህ ትንቢት ተናገር፤ እንዲህም በል፦ ‘ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ከብሔራት መካከል ለተረፉት* ርስት እንድትሆኑ ባድማ ስላደረጓችሁና ከየአቅጣጫው ጥቃት ስለሰነዘሩባችሁ እንዲሁም ሰው አፍ ውስጥ ስለገባችሁና ሰዎች ስማችሁን ስላጠፉ፣+  የእስራኤል ተራሮች ሆይ፣ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ የተናገረውን ቃል ስሙ! ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ለተራሮችና ለኮረብቶች፣ ለጅረቶችና ለሸለቆዎች፣ ፈራርሰው ባድማ ለሆኑት ቦታዎችና+ በዙሪያቸው ባሉት ከጥፋት የተረፉ ብሔራት ለተበዘበዙት እንዲሁም መሳለቂያ ለሆኑት የተተዉ ከተሞች ይህን ቃል ተናግሯል፤+  ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እነሱን በተመለከተ እንዲህ ይላል፦ ‘የግጦሽ ቦታዎቿን ለመውሰድና ምድሪቱን ለመበዝበዝ ሲሉ በታላቅ ደስታና በከፍተኛ ንቀት*+ ምድሬን የገዛ ርስታቸው እንደሆነ አድርገው በተናገሩት፣ ከጥፋት በተረፉት ብሔራትና በመላዋ ኤዶም ላይ በቅንዓቴ እሳት+ እናገራለሁ።’”’+  “ስለዚህ ስለ እስራኤል ምድር ትንቢት ተናገር፤ ለተራሮችና ለኮረብቶች፣ ለጅረቶችና ለሸለቆዎች እንዲህ በል፦ ‘ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “እነሆ፣ ብሔራት ያደረሱባችሁን ውርደት ስለተሸከማችሁ በቅንዓቴና በቁጣዬ እናገራለሁ።”’+  “ስለዚህ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘በዙሪያችሁ ያሉት ብሔራት የገዛ ራሳቸውን ኀፍረት ይሸከማሉ ብዬ እጄን አንስቼ ምያለሁ።+  የእስራኤል ተራሮች ሆይ፣ እናንተ ግን ለሕዝቤ ለእስራኤል ቅርንጫፍ ታወጣላችሁ፤ ፍሬም ታፈራላችሁ፤+ እነሱ በቅርቡ ይመለሳሉና።  እኔ ከእናንተ ጋር ነኝ፤ ፊቴንም ወደ እናንተ እመልሳለሁ፤ እናንተም ትታረሳላችሁ፤ ደግሞም ዘር ይዘራባችኋል። 10  ሕዝባችሁን ይኸውም መላውን የእስራኤል ቤት አበዛለሁ፤ ከተሞቹም የሰው መኖሪያ ይሆናሉ፤+ የፈራረሱትም ስፍራዎች ዳግመኛ ይገነባሉ።+ 11  አዎ፣ ሕዝባችሁንና ከብቶቻችሁን አበዛለሁ፤+ እነሱም ይበዛሉ፤ ፍሬያማም ይሆናሉ። እንደቀድሞው ዘመን ሰዎች እንዲኖሩባችሁ አደርጋለሁ፤+ ደግሞም ከበፊቱ የበለጠ አበለጽጋችኋለሁ፤+ እናንተም እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ታውቃላችሁ።+ 12  በእናንተ ላይ ሰዎች ይኸውም ሕዝቤ እስራኤል እንዲመላለሱ አደርጋለሁ፤ እነሱም ይወርሷችኋል።+ የእነሱ ርስት ትሆናላችሁ፤ ከእንግዲህ ልጅ አልባ አታደርጓቸውም።’”+ 13  “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘“ሰዎችን የምትበላና በላይዋ ያሉትን ብሔራት የወላድ መሃን የምታደርግ ምድር ናችሁ” ስለሚሏችሁ፣’ 14  ‘ከእንግዲህ ሰው አትበሉም ወይም በምድሪቱ ላይ ያሉትን ብሔራት ልጅ አልባ አታደርጉም’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ። 15  ‘ከእንግዲህ ብሔራት እናንተን እንዲሰድቡ ወይም ሰዎች የሚሰነዝሩባችሁን ዘለፋ እንድትሸከሙ አልፈቅድም፤+ ደግሞም በምድሪቱ ላይ ላሉት ብሔራት መሰናክል አትሆኑም’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።” 16  የይሖዋም ቃል ዳግመኛ እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣ፦ 17  “የሰው ልጅ ሆይ፣ የእስራኤል ቤት ሰዎች በምድራቸው ላይ ይኖሩ በነበረበት ጊዜ በመንገዳቸውና በሥራቸው ምድሪቱን አረከሷት።+ መንገዳቸው በፊቴ እንደ ወር አበባ ርኩሰት ነበር።+ 18  በምድሪቱ ላይ ደም ስላፈሰሱና ምድሪቱን አስጸያፊ በሆኑ ጣዖቶቻቸው* ስላረከሱ+ ቁጣዬን አፈሰስኩባቸው።+ 19  ደግሞም በብሔራት መካከል በተንኳቸው፤ በየአገሩም ዘራኋቸው።+ እንደ መንገዳቸውና እንደ ሥራቸው ፈረድኩባቸው። 20  ሆኖም ወደ እነዚህ ብሔራት በመጡ ጊዜ ሰዎች ስለ እነሱ ‘እነዚህ የይሖዋ ሕዝብ ናቸው፤ ይሁን እንጂ ከእሱ ምድር ለመፈናቀል ተገደዱ’ እያሉ ቅዱስ ስሜን አረከሱ።+ 21  በመሆኑም የእስራኤል ቤት በሄዱባቸው ብሔራት መካከል ያረከሱት ቅዱስ ስሜ ያሳስበኛል።”+ 22  “ስለዚህ ለእስራኤል ቤት ሰዎች እንዲህ በል፦ ‘ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “የእስራኤል ቤት ሰዎች ሆይ፣ እርምጃ የምወስደው ለእናንተ ብዬ ሳይሆን በሄዳችሁባቸው ብሔራት መካከል ላረከሳችሁት ቅዱስ ስሜ ስል ነው።”’+ 23  ‘በብሔራት መካከል የረከሰውን፣ ይኸውም በእነሱ መካከል ያረከሳችሁትን ታላቅ ስሜን በእርግጥ እቀድሰዋለሁ፤+ ዓይኖቻቸው እያዩ በመካከላችሁ በምቀደስበት ጊዜ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ፣ ‘ብሔራት እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ያውቃሉ።+ 24  ከብሔራት መካከል አወጣችኋለሁ፤ ከየአገሩም ሁሉ ሰብስቤ ወደ ምድራችሁ አመጣችኋለሁ።+ 25  ንጹሕ ውኃ እረጫችኋለሁ፤ እናንተም ንጹሕ ትሆናላችሁ፤+ ከርኩሰታችሁ ሁሉና አስጸያፊ ከሆኑት ጣዖቶቻችሁ ሁሉ+ አነጻችኋለሁ።+ 26  አዲስ ልብ እሰጣችኋለሁ፤+ በውስጣችሁም አዲስ መንፈስ አሳድራለሁ።+ የድንጋይ ልባችሁን+ ከሰውነታችሁ አስወግጄ የሥጋ ልብ* እሰጣችኋለሁ። 27  መንፈሴን በውስጣችሁ አኖራለሁ፤ በሥርዓቴም እንድትመላለሱ አደርጋለሁ፤+ ድንጋጌዎቼንም ትጠብቃላችሁ፣ በተግባርም ታውሏቸዋላችሁ። 28  በዚያን ጊዜ ለአባቶቻችሁ በሰጠኋት ምድር ላይ ትኖራላችሁ፤ ሕዝቤም ትሆናላችሁ፤ እኔም አምላካችሁ እሆናለሁ።’+ 29  “‘ከርኩሰታችሁ ሁሉ አድናችኋለሁ፤ እህሉን እጠራዋለሁ፤ ደግሞም አበዛዋለሁ፤ ረሃብም አላመጣባችሁም።+ 30  በረሃብ የተነሳ በብሔራት መካከል ዳግመኛ ውርደት እንዳይደርስባችሁ፣ የዛፉን ፍሬና የእርሻውን ምርት አበዛለሁ።+ 31  በዚያን ጊዜ ክፉ መንገዳችሁንና መጥፎ ሥራችሁን ታስታውሳላችሁ፤ በበደላችሁና በምትፈጽሟቸው አስጸያፊ ልማዶች የተነሳ ራሳችሁን ትጸየፋላችሁ።+ 32  ይሁንና ይህን እወቁ፦ ይህን የማደርገው ለእናንተ ብዬ አይደለም’+ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ። ‘ይልቁንም የእስራኤል ቤት ሰዎች ሆይ፣ ከመንገዳችሁ የተነሳ እፈሩ፤ ደግሞም ተሸማቀቁ።’ 33  “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘ከበደላችሁ ሁሉ በማነጻችሁ ቀን ከተሞቹ የሰው መኖሪያ እንዲሆኑ፣ የፈራረሱትም ቦታዎች እንደገና እንዲገነቡ አደርጋለሁ።+ 34  አላፊ አግዳሚው ሁሉ ጠፍ ሆኖ ሲያየው የነበረው ባድማ መሬት ይታረሳል። 35  ሰዎችም እንዲህ ይላሉ፦ “ባድማ የነበረው ምድር እንደ ኤደን የአትክልት ስፍራ+ ሆነ፤ ፈራርሰው ባድማና ወና ሆነው የነበሩት ከተሞችም አሁን የተመሸጉ ከተሞችና የሰው መኖሪያ ሆነዋል።”+ 36  ደግሞም ከጥፋት የተረፉት በዙሪያችሁ ያሉት ብሔራት፣ የፈረሰውን የገነባሁትና ባድማ የሆነውን ምድር ያለማሁት እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ያውቃሉ። እኔ ይሖዋ ተናግሬአለሁ፤ ደግሞም አድርጌዋለሁ።’+ 37  “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘የእስራኤል ቤት ሰዎችም ይህን እንዳደርግላቸው እንዲጠይቁኝ እፈቅድላቸዋለሁ፦ ሕዝባቸውን እንደ መንጋ አበዛዋለሁ። 38  እንደ ቅዱሳን መንጋና በበዓል ወቅት+ በኢየሩሳሌም ውስጥ እንደሚገኘው መንጋ፣* ፈራርሰው የነበሩት ከተሞችም በሰው መንጋ ይሞላሉ፤+ እነሱም እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ያውቃሉ።’”

የግርጌ ማስታወሻዎች

ቃል በቃል “ለቀሩት።”
ወይም “በነፍሳቸው ንቀት።”
እዚህ ላይ የገባው የዕብራይስጥ ቃል “ፋንድያ” ከሚለው ቃል ጋር ዝምድና ሊኖረው የሚችል ሲሆን ንቀትን ለማመልከት ተሠርቶበታል።
ለአምላክ አመራር ፈጣን ምላሽ የሚሰጥን ልብ ያመለክታል።
“በኢየሩሳሌም ለመሥዋዕት እንደሚቀርቡ የበግ መንጋዎች” ማለትም ሊሆን ይችላል።