ሕዝቅኤል 41:1-26

  • በቤተ መቅደሱ ውስጥ የሚገኘው መቅደስ (1-4)

  • ግንቡና በጎን በኩል ያሉት ክፍሎች (5-11)

  • በምዕራብ በኩል ያለው ሕንፃ (12)

  • ሕንፃዎቹ ተለኩ (13-15ሀ)

  • ውስጠኛው መቅደስ (15ለ-26)

41  ከዚያም ወደ ውጨኛው መቅደስ* አስገባኝ፤ በጎንና በጎን ያሉትንም ዓምዶች ለካ፤ የዓምዶቹ ወርድ በአንደኛው ጎን ስድስት ክንድ፣* በሌላኛውም ጎን ስድስት ክንድ ሆነ።  የመግቢያው ወርድ አሥር ክንድ ነበር፤ በመግቢያው ግራና ቀኝ ያሉት ግንቦች* አምስት አምስት ክንድ ነበሩ። የውጨኛውን መቅደስ ርዝመት ሲለካ 40 ክንድ ሆነ፤ ወርዱ ደግሞ 20 ክንድ ሆነ።  ከዚያም ወደ ውስጥ* ገብቶ በመግቢያው ጎን ላይ ያለውን ዓምድ ውፍረት ሲለካ ሁለት ክንድ ሆነ፤ የመግቢያውም ወርድ ስድስት ክንድ ነበር። በመግቢያው ግራና ቀኝ ያሉት ግንቦች ሰባት ክንድ ነበሩ።*  ከዚያም ከውጨኛው መቅደስ ትይዩ ያለውን ክፍል ለካ፤ ርዝመቱም 20 ክንድ፣ ወርዱም 20 ክንድ ሆነ።+ እሱም “ይህ ቅድስተ ቅዱሳኑ+ ነው” አለኝ።  ከዚያም የቤተ መቅደሱን ግንብ ሲለካ ውፍረቱ ስድስት ክንድ ሆነ። በቤተ መቅደሱ ጎን ዙሪያውን ያሉት ክፍሎች ወርድ አራት ክንድ ነበር።+  በጎን በኩል ያሉት ክፍሎች ከበላያቸው ሁለት ፎቅ ነበራቸው፤ በእያንዳንዱ ፎቅ ላይ 30 ክፍሎች ነበሩ። በቤተ መቅደሱ ግንብ ዙሪያ፣ በጎን በኩል ያሉትን ክፍሎች ደግፈው የሚይዙ ተሸካሚዎች ነበሩ፤ በመሆኑም እነዚህ ተሸካሚዎች ወደ ቤተ መቅደሱ ግንብ ዘልቀው አልገቡም።+  በቤተ መቅደሱ ግራና ቀኝ ጠመዝማዛ መተላለፊያ* ነበር፤ ላይ ወደሚገኙት ክፍሎች ሲወጣ የመወጣጫዎቹ ወርድ ይጨምር ነበር።+ አንድ ሰው ከታች ተነስቶ በመካከለኛው ፎቅ በኩል ወደ መጨረሻው ፎቅ ሲወጣ ፎቁ እየሰፋ ይሄድ ነበር።  በቤተ መቅደሱ ዙሪያ ከፍ ያለ መሠረት መኖሩን አየሁ፤ በጎን በኩል ያሉት ክፍሎች መሠረትም እስከ ማዕዘኑ ድረስ ሙሉ ዘንግ ይኸውም ስድስት ክንድ ነበር።  በጎን በኩል ያሉት ክፍሎች የውጨኛው ግንብ ወርድ አምስት ክንድ ነበር። በጎን ካሉት ክፍሎች አጠገብ የቤተ መቅደሱ ክፍል የሆነ ክፍት ቦታ* ነበር። 10  በቤተ መቅደሱና በመመገቢያ ክፍሎቹ*+ መካከል በሁለቱም በኩል ወርዱ 20 ክንድ የሆነ ቦታ ነበር። 11  በሰሜን አቅጣጫ፣ በጎን በኩል ባሉት ክፍሎችና ክፍት በሆነው ቦታ መካከል መግቢያ ነበር፤ በደቡብ አቅጣጫም ሌላ መግቢያ ነበር። ክፍት የሆነው ቦታ በሁሉም አቅጣጫ ወርዱ አምስት ክንድ ነበር። 12  በምዕራብ በኩል ክፍት ከሆነው ስፍራ ትይዩ ያለው ሕንፃ ወርዱ 70 ክንድ፣ ርዝመቱ ደግሞ 90 ክንድ ነበር፤ የሕንፃው ግንብ ውፍረት ዙሪያውን አምስት ክንድ ነበር። 13  ቤተ መቅደሱን ሲለካ ርዝመቱ 100 ክንድ ሆነ። ክፍት የሆነው ስፍራ፣ ሕንፃውና* ግንቦቹ ርዝመታቸው 100 ክንድ ነበር። 14  ከምሥራቅ ትይዩ የሆነው የቤተ መቅደሱ የፊተኛው ክፍልና ክፍት የሆነው ስፍራ ወርድ 100 ክንድ ነበር። 15  በሁለቱም ጎን ያሉትን መተላለፊያዎቹን ጨምሮ በጀርባ በኩል ክፍት ከሆነው ስፍራ ጋር ትይዩ የሆነውን ሕንፃ ርዝመት ሲለካ 100 ክንድ ሆነ። እንዲሁም ውጨኛውን መቅደስ፣ ውስጠኛውን መቅደስና+ የግቢውን በረንዳዎች ለካ፤ 16  ደግሞም በሦስቱም ቦታዎች ያሉትን ደፎች፣ እየጠበቡ የሚሄዱ ክፈፎች ያሏቸው መስኮቶችና+ መተላለፊያዎች ለካ። ከደፉ አጠገብ ከወለሉ አንስቶ እስከ መስኮቶቹ ድረስ የእንጨት ማስጌጫዎች ነበሩ፤+ መስኮቶቹም ተሸፍነው ነበር። 17  ከመግቢያው በላይ ያለው፣ የቤተ መቅደሱ ውስጥና ውጭ እንዲሁም በዙሪያው ያለው ግንብ ሁሉ ተለካ። 18  ግንቡ ኪሩቤልና+ የዘንባባ ዛፍ ምስል ተቀርጸውበት ነበር፤+ በሁለት ኪሩቤል መካከል የዘንባባ ዛፍ ምስል ነበር፤ እያንዳንዱ ኪሩብ ሁለት ፊት ነበረው። 19  ሰው የሚመስለው ፊት በአንድ በኩል ወዳለው የዘንባባ ዛፍ ምስል የዞረ ሲሆን፣ አንበሳ* የሚመስለው ፊት ደግሞ በሌላ በኩል ወዳለው የዘንባባ ዛፍ ዞሮ ነበር።+ በዚህ መንገድ በቤተ መቅደሱ ዙሪያ ተቀርጸው ነበር። 20  በመቅደሱ ግድግዳ ላይ ከወለሉ አንስቶ ከመግቢያው በላይ እስካለው ስፍራ ድረስ ኪሩቤልና የዘንባባ ዛፍ ምስሎች ተቀርጸው ነበር። 21  የመቅደሱ መቃኖች አራት ማዕዘን ናቸው።*+ ከቅዱሱ ስፍራ* ፊት ለፊት 22  ቁመቱ ሦስት ክንድ፣ ርዝመቱ ደግሞ ሁለት ክንድ የሆነ ከእንጨት የተሠራ መሠዊያ+ የሚመስል ነገር ነበር። የማዕዘን ቋሚዎች ነበሩት፤ መሠረቱና* ጎኖቹ ከእንጨት የተሠሩ ነበሩ። እሱም “በይሖዋ ፊት ያለው ጠረጴዛ ይህ ነው”+ አለኝ። 23  የውጨኛው መቅደስና ቅዱሱ ስፍራ እያንዳንዳቸው ሁለት በሮች ነበሯቸው።+ 24  በሮቹ ታጣፊ የሆኑ ሁለት ሳንቃዎች ነበሯቸው፤ እያንዳንዱ በር ሁለት ሳንቃዎች ነበሩት። 25  በግድግዳው ላይ ያሉት ዓይነት ኪሩቦችና የዘንባባ ዛፍ ምስሎች በመቅደሱ በሮች ላይ ተቀርጸው ነበር።+ በተጨማሪም በውጭ በኩል ከፊት ለፊት በረንዳው ላይ ከእንጨት የተሠራ ወጣ ያለ ነገር* ነበር። 26  እንዲሁም በበረንዳው ግራና ቀኝ፣ ከቤተ መቅደሱ ጎን ባሉት ክፍሎች ላይና በታዛው አካባቢ እየጠበቡ የሚሄዱ ክፈፎች ያሏቸው መስኮቶችና+ የዘንባባ ዛፍ ምስሎች ነበሩ።

የግርጌ ማስታወሻዎች

ቃል በቃል “ቤተ መቅደስ።” በሕዝቅኤል ምዕራፍ 41 እና 42 ላይ ይህ ቃል የውጨኛውን መቅደስ (ቅድስት) ወይም መላውን መቅደስ (ቅድስቱንና ቅድስተ ቅዱሳኑን ጨምሮ ቤተ መቅደሱን) ያመለክታል።
ይህ ረጅም ክንድ የሚባለውን መለኪያ ያመለክታል። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።
ቃል በቃል “ጎኖች።”
ውስጠኛውን መቅደስ ወይም ቅድስተ ቅዱሳኑን ያመለክታል።
ቃል በቃል “የመግቢያው ወርድ ሰባት ክንድ ነበር።”
ክብ የሆኑ ደረጃዎችን የሚያመለክት ይመስላል።
በቤተ መቅደሱ ዙሪያ ያለ ጠባብ መመላለሻ ሳይሆን አይቀርም።
ወይም “በቤተ መቅደሱና በክፍሎቹ።”
ከመቅደሱ በስተ ምዕራብ የሚገኘውን ሕንፃ ያመለክታል።
ወይም “ደቦል አንበሳ።”
ቃል በቃል “መቃን አራት ማዕዘን ነው።” ወደ ቅድስት የሚያስገባውን በር የሚያመለክት ሳይሆን አይቀርም።
ቅድስተ ቅዱሳኑን የሚያመለክት ሳይሆን አይቀርም።
ቃል በቃል “ርዝመቱና።”
ወይም “ታዛ።”