ኢያሱ 17:1-18

  • በስተ ምዕራብ ያለው የምናሴ ርስት (1-13)

  • ለዮሴፍ ዘሮች የተሰጣቸው ተጨማሪ ርስት (14-18)

17  ከዚያም ዕጣው+ ለምናሴ+ ነገድ ወጣ፤ ምክንያቱም እሱ የዮሴፍ የበኩር ልጅ ነበር።+ የጊልያድ አባት የሆነው የምናሴ የበኩር ልጅ ማኪር+ ጦረኛ ሰው ስለነበር ጊልያድን እና ባሳንን+ ወሰደ።  ለቀሩት የምናሴ ዘሮችም በየቤተሰባቸው ይኸውም ለአቢዔዜር+ ልጆች፣ ለሄሌቅ ልጆች፣ ለአስሪዔል ልጆች፣ ለሴኬም ልጆች፣ ለሄፌር ልጆችና ለሸሚዳ ልጆች ዕጣ ወጣ። የዮሴፍ ልጅ የምናሴ ዘሮች ወንዶቹ በየቤተሰባቸው እነዚህ ነበሩ።+  ሆኖም የምናሴ ልጅ፣ የማኪር ልጅ፣ የጊልያድ ልጅ፣ የሄፌር ልጅ ሰለጰአድ+ ሴቶች እንጂ ወንዶች ልጆች አልነበሩትም፤ የሴቶች ልጆቹም ስም ማህላ፣ ኖኅ፣ ሆግላ፣ ሚልካ እና ቲርጻ ነበር።  እነሱም ወደ ካህኑ አልዓዛር፣+ ወደ ነዌ ልጅ ወደ ኢያሱና ወደ አለቆቹ ቀርበው “ይሖዋ በወንድሞቻችን መካከል ርስት እንዲሰጠን ሙሴን አዞት ነበር” አሏቸው።+ ስለዚህ ኢያሱ ይሖዋ በሰጠው ትእዛዝ መሠረት በአባታቸው ወንድሞች መካከል ርስት ሰጣቸው።+  ምናሴ በዮርዳኖስ ማዶ* ከነበሩት ከጊልያድና ከባሳን በተጨማሪ አሥር ድርሻዎች ወጡለት፤+  ምክንያቱም የምናሴ ሴቶች ልጆች በወንዶች ልጆቹ መካከል ርስት ተሰጥቷቸው ነበር፤ የጊልያድም ምድር የቀሩት የምናሴ ዘሮች ርስት ሆነ።  የምናሴ ወሰን ከአሴር አንስቶ ከሴኬም+ ፊት ለፊት እስከምትገኘው እስከ ሚክመታት+ ድረስ ነበር፤ ወሰኑ በስተ ደቡብ* በኩል የኤንታጱአ ነዋሪዎች እስከሚገኙበት ምድር ይዘልቃል።  የታጱአ+ ምድር የምናሴ ሆነች፤ በምናሴ ወሰን ላይ የምትገኘው የታጱአ ከተማ ግን የኤፍሬም ዘሮች ነበረች።  ወሰኑ ወደ ቃና ሸለቆ ይኸውም ከሸለቆው በስተ ደቡብ ቁልቁል ይወርዳል። በምናሴ ከተሞች መካከል የሚገኙ የኤፍሬም ከተሞች የነበሩ ሲሆን+ የምናሴ ወሰን በሸለቆው ሰሜናዊ ክፍል አድርጎ ባሕሩ ጋ ሲደርስ ያበቃል።+ 10  በስተ ደቡብ በኩል ያለው የኤፍሬም፣ በስተ ሰሜን በኩል ያለው ደግሞ የምናሴ ነበር፤ ባሕሩም የእሱ ወሰን ነበር፤+ እነሱም* በስተ ሰሜን እስከ አሴር፣ በስተ ምሥራቅ ደግሞ እስከ ይሳኮር ይደርሱ ነበር። 11  በይሳኮርና በአሴር ግዛቶች ውስጥ ለምናሴ የተሰጡት የሚከተሉት ናቸው፦ ቤትሼንና በሥሯ* ያሉት ከተሞች፣ ይብለአምና+ በሥሯ ያሉት ከተሞች፣ የዶር+ ነዋሪዎችና በሥሯ ያሉት ከተሞች እንዲሁም የኤንዶር+ ነዋሪዎችና በሥሯ ያሉት ከተሞች፣ የታአናክ+ ነዋሪዎችና በሥሯ ያሉት ከተሞች፣ የመጊዶ ነዋሪዎችና በሥሯ ያሉት ከተሞች፣ ሦስቱ ኮረብታማ አካባቢዎች። 12  ሆኖም የምናሴ ዘሮች እነዚህን ከተሞች መውረስ አልቻሉም፤ ከነአናውያን ይህን ምድር ላለመልቀቅ ቆርጠው ነበር።+ 13  እስራኤላውያን እያየሉ በሄዱ ጊዜ ከነአናውያንን የግዳጅ ሥራ እንዲሠሩ አስገደዷቸው፤+ ይሁን እንጂ ሙሉ በሙሉ አላባረሯቸውም።*+ 14  የዮሴፍ ዘሮችም ኢያሱን “አንድ ዕጣና+ አንድ ድርሻ ብቻ ርስት አድርገህ የሰጠኸን ለምንድን ነው?* ይሖዋ እስካሁን ድረስ ስለባረከን የሕዝባችን ቁጥር በዝቷል”+ አሉት። 15  ኢያሱም “ቁጥራችሁ ይህን ያህል ብዙ ከሆነ የኤፍሬም ተራራማ አካባቢ+ በጣም ስለሚጠብባችሁ ወደ ጫካው በመውጣት በፈሪዛውያንና+ በረፋይም+ ምድር የሚገኘውን አካባቢ ለራሳችሁ መንጥሩ” አላቸው። 16  ከዚያም የዮሴፍ ዘሮች እንዲህ አሉት፦ “ተራራማው አካባቢ አይበቃንም፤ ደግሞም በሸለቆው* ምድር ማለትም በቤትሼን+ እና በሥሯ* በሚገኙት ከተሞች እንዲሁም በኢይዝራኤል ሸለቆ+ ውስጥ* የሚኖሩት ከነአናውያን በሙሉ የብረት ማጭድ የተገጠመላቸው የጦር ሠረገሎች* አሏቸው።”+ 17  በመሆኑም ኢያሱ ለዮሴፍ ቤት ይኸውም ለኤፍሬምና ለምናሴ እንዲህ አለ፦ “እናንተ ብዙ ሕዝብ ናችሁ፤ ታላቅ ኃይልም አላችሁ። ድርሻችሁ አንድ ዕጣ ብቻ አይሆንም፤+ 18  ከዚህ ይልቅ ተራራማው አካባቢ የእናንተ ይሆናል።+ አካባቢው ጫካ ቢሆንም ትመነጥሩታላችሁ፤ የግዛታችሁም ወሰን ይሆናል። ምክንያቱም ከነአናውያን የብረት ማጭድ የተገጠመላቸው የጦር ሠረገሎች* ያሏቸውና ብርቱዎች ቢሆኑም እንኳ ከምድሩ ታባርሯቸዋላችሁ።”+

የግርጌ ማስታወሻዎች

በስተ ምሥራቅ ያለውን ያመለክታል።
ቃል በቃል “በስተ ቀኝ።”
የምናሴን ሰዎች ወይም የምናሴን ክልል ያመለክታል።
ወይም “በዙሪያዋ።”
ወይም “አላስለቀቋቸውም።”
ቃል በቃል “የሰጠኸኝ ለምንድን ነው?”
ወይም “በረባዳማው ሜዳ።”
ወይም “በዙሪያዋ።”
ወይም “ረባዳማ ሜዳ ላይ።”
ቃል በቃል “የብረት ሠረገሎች።”
ቃል በቃል “የብረት ሠረገሎች።”