ኤርምያስ 36:1-32

  • ኤርምያስ ባሮክን በቃሉ አስጻፈው (1-7)

  • ባሮክ ከጥቅልሉ ላይ ጮክ ብሎ አነበበ (8-19)

  • ኢዮዓቄም ጥቅልሉን አቃጠለው (20-26)

  • መልእክቱ በአዲስ ጥቅልል ላይ በድጋሚ ተጻፈ (27-32)

36  የኢዮስያስ ልጅ የሆነው የይሁዳ ንጉሥ ኢዮዓቄም+ በነገሠ በአራተኛው ዓመት የይሖዋ ቃል እንዲህ ሲል ወደ ኤርምያስ መጣ፦  “አንድ ጥቅልል* ውሰድና በኢዮስያስ ዘመን ለአንተ መናገር ከጀመርኩበት ቀን አንስቶ እስከ ዛሬ ድረስ+ በእስራኤል፣ በይሁዳና በብሔራት ሁሉ+ ላይ አመጣዋለሁ ብዬ የነገርኩህን ቃል በሙሉ ጻፍበት።+  ምናልባት የይሁዳ ቤት ሰዎች በእነሱ ላይ ላመጣ ያሰብኩትን ጥፋት ሁሉ ሲሰሙ ከክፉ መንገዳቸው ይመለሱ ይሆናል፤ እኔም በደላቸውንና ኃጢአታቸውን ይቅር እላለሁ።”+  ከዚያም ኤርምያስ የነሪያህን ልጅ ባሮክን+ ጠራው፤ ይሖዋ የነገረውንም ቃል ሁሉ በቃሉ አስጻፈው፤ ባሮክም በጥቅልሉ* ላይ ጻፈው።+  ኤርምያስም ባሮክን እንዲህ ሲል አዘዘው፦ “እኔ ታግጃለሁ፤ ወደ ይሖዋ ቤትም መግባት አልችልም።  ስለዚህ ገብተህ እኔ ያስጻፍኩህን የይሖዋን ቃል ከጥቅልሉ ላይ ጮክ ብለህ ማንበብ ያለብህ አንተ ነህ። በጾም ቀን በይሖዋ ቤት የተሰበሰቡ ሰዎች እየሰሙ አንብበው፤ በዚህ መንገድ፣ ከየከተሞቻቸው ለመጡት የይሁዳ ሰዎች ሁሉ ታነብላቸዋለህ።  ምናልባት ሞገስ ለማግኘት የሚያቀርቡት ልመና ወደ ይሖዋ ሊደርስና እያንዳንዳቸው ከክፉ መንገዳቸው ሊመለሱ ይችላሉ፤ ይሖዋ በዚህ ሕዝብ ላይ የተናገረው ቁጣና መዓት ታላቅ ነውና።”  በመሆኑም የነሪያህ ልጅ ባሮክ ነቢዩ ኤርምያስ ያዘዘውን ሁሉ አደረገ፤ በይሖዋ ቤት የይሖዋን ቃል ከጥቅልሉ* ላይ ጮክ ብሎ አነበበ።+  የኢዮስያስ ልጅ የሆነው የይሁዳ ንጉሥ ኢዮዓቄም+ በነገሠ በአምስተኛው ዓመት፣ በዘጠነኛው ወር በኢየሩሳሌም ያለው ሕዝብ ሁሉና ከይሁዳ ከተሞች ወደ ኢየሩሳሌም የመጣው ሕዝብ ሁሉ በይሖዋ ፊት ጾም አወጀ።+ 10  ከዚያም ባሮክ በይሖዋ ቤት በላይኛው ግቢ ይኸውም በይሖዋ ቤት በአዲሱ በር መግቢያ+ አጠገብ ባለው፣ የቅዱሳን መጻሕፍት ገልባጭ* በሆነው በሳፋን+ ልጅ በገማርያህ+ ክፍል* ሕዝቡ ሁሉ እየሰማ የኤርምያስን ቃል ከጥቅልሉ* ላይ አነበበ። 11  የሳፋን ልጅ፣ የገማርያህ ልጅ ሚካያህ ከጥቅልሉ* ላይ የተነበበውን የይሖዋን ቃል ሁሉ በሰማ ጊዜ 12  ወደ ንጉሡ ቤት፣* ወደ ጸሐፊው ክፍል ወረደ። መኳንንቱ* ሁሉ ይኸውም ጸሐፊው ኤሊሻማ፣+ የሸማያህ ልጅ ደላያህ፣ የአክቦር+ ልጅ ኤልናታን፣+ የሳፋን ልጅ ገማርያህ፣ የሃናንያህ ልጅ ሴዴቅያስና ሌሎቹ መኳንንት ሁሉ በዚያ ተቀምጠው ነበር። 13  ሚካያህ፣ ባሮክ ሕዝቡ እየሰማ ከጥቅልሉ* ላይ ሲያነብ ያዳመጠውን ቃል ሁሉ ነገራቸው። 14  በዚህ ጊዜ መኳንንቱ ሁሉ የኩሺ ልጅ፣ የሸሌምያህ ልጅ፣ የነታንያህ ልጅ የሆነውን የሁዲን “ሕዝቡ እየሰማህ ያነበብከውን ጥቅልል ይዘህ ና” ብሎ እንዲነግረው ወደ ባሮክ ላኩት። የነሪያህ ልጅ ባሮክም ጥቅልሉን ይዞ ወደ እነሱ ሄደ። 15  እነሱም “እባክህ ተቀመጥና ጥቅልሉን ጮክ ብለህ አንብብልን” አሉት። ባሮክም አነበበላቸው። 16  እነሱም ቃሉን ሁሉ እንደሰሙ በፍርሃት ተውጠው እርስ በርስ ተያዩ፤ ከዚያም ባሮክን “ይህን ቃል ሁሉ ለንጉሡ ልንነግረው ይገባል” አሉት። 17  ደግሞም ባሮክን “ይህን ሁሉ ቃል የጻፍከው እንዴት እንደሆነ እስቲ ንገረን። በቃሉ ነው ያስጻፈህ?” ብለው ጠየቁት። 18  ባሮክም “ይህን ሁሉ በቃሉ አስጻፈኝ፤ እኔም በጥቅልሉ* ላይ በቀለም ጻፍኩት” ብሎ መለሰላቸው። 19  መኳንንቱ ባሮክን “ሂድ፣ አንተና ኤርምያስ ተደበቁ፤ ያላችሁበትንም ማንም ሰው አይወቅ” አሉት።+ 20  ከዚያም ንጉሡ ወደሚገኝበት ግቢ ሄዱ፤ ጥቅልሉንም በጸሐፊው በኤሊሻማ ክፍል አስቀመጡት፤ የሰሙትንም ነገር ሁሉ ለንጉሡ ነገሩት። 21  ንጉሡም ጥቅልሉን እንዲያመጣ የሁዲን+ ላከው፤ እሱም ጥቅልሉን ከጸሐፊው ከኤሊሻማ ክፍል ይዞት መጣ። የሁዲም ንጉሡና በንጉሡ አጠገብ ቆመው የነበሩት መኳንንት ሁሉ እየሰሙ ያነበው ጀመር። 22  ንጉሡ በዘጠነኛው ወር* የክረምቱን ወቅት በሚያሳልፍበት ቤት ተቀምጦ ነበር፤ በፊቱም በምድጃ የሚነድ እሳት ነበር። 23  የሁዲ ሦስት ወይም አራት ዓምድ ካነበበ በኋላ ንጉሡ የተነበበውን ክፍል በጸሐፊ ቢላ እየቀደደ በምድጃ ውስጥ ወዳለው እሳት ይወረውረው ነበር፤ ጥቅልሉ ሙሉ በሙሉ ተቃጥሎ እስኪያልቅ ድረስ እንዲሁ አደረገ። 24  ይህን ሁሉ ቃል ሲሰሙ የነበሩት ንጉሡም ሆነ አገልጋዮቹ በሙሉ ምንም ፍርሃት አልተሰማቸውም፤ ልብሳቸውንም አልቀደዱም። 25  ኤልናታን፣+ ደላያህና+ ገማርያህ+ ንጉሡ ጥቅልሉን እንዳያቃጥለው ቢለምኑትም እንኳ አልሰማቸውም። 26  በተጨማሪም ንጉሡ ጸሐፊውን ባሮክንና ነቢዩን ኤርምያስን እንዲይዟቸው የንጉሡን ልጅ የራህምኤልን፣ የአዝርዔልን ልጅ ሰራያህንና የአብድዔልን ልጅ ሸሌምያህን አዘዘ፤ ይሖዋ ግን ሰውሯቸው ነበር።+ 27  ንጉሡ፣ ባሮክ ከኤርምያስ አፍ እየሰማ የጻፈውን ቃል የያዘውን ጥቅልል+ ካቃጠለው በኋላ የይሖዋ ቃል እንደገና እንዲህ ሲል ወደ ኤርምያስ መጣ፦ 28  “ሌላ ጥቅልል ውሰድና የይሁዳ ንጉሥ ኢዮዓቄም ባቃጠለው በመጀመሪያው ጥቅልል+ ላይ የነበረውን ያንኑ ቃል ሁሉ ጻፍበት። 29  የይሁዳን ንጉሥ ኢዮዓቄምንም እንዲህ በለው፦ ‘ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ይህን ጥቅልል አቃጥለሃል፤ ደግሞም ‘“የባቢሎን ንጉሥ ያላንዳች ጥርጥር መጥቶ ይህችን ምድር ያወድማል፤ ሰውንና እንስሳንም ከምድሪቱ ላይ ያጠፋል” ብለህ በጥቅልሉ ላይ የጻፍከው ለምንድን ነው?’ ብለሃል።+ 30  ስለዚህ ይሖዋ በይሁዳ ንጉሥ በኢዮዓቄም ላይ እንዲህ ይላል፦ ‘በዳዊት ዙፋን ላይ የሚቀመጥ ሰው አይኖረውም፤+ ሬሳውም የቀን ሐሩርና የሌሊት ቁር ይፈራረቅበታል።+ 31  እሱን፣ ልጆቹንና* አገልጋዮቹን ለፈጸሙት በደል ተጠያቂ አደርጋቸዋለሁ፤ ደግሞም በእነሱ፣ በኢየሩሳሌም ነዋሪዎችና በይሁዳ ሰዎች ላይ አመጣባቸዋለሁ ብዬ የተናገርኩትን ጥፋት ሁሉ አወርድባቸዋለሁ፤+ እነሱ ግን አልሰሙም።’”’”+ 32  ከዚያም ኤርምያስ ሌላ ጥቅልል ወስዶ ለነሪያህ ልጅ ለጸሐፊው ለባሮክ ሰጠው፤+ እሱም ኤርምያስ በቃል እያስጻፈው የይሁዳ ንጉሥ ኢዮዓቄም በእሳት ባቃጠለው ጥቅልል*+ ላይ የነበረውን ቃል ሁሉ ጻፈበት። ደግሞም ከዚያ ጋር የሚመሳሰል ብዙ ቃል ተጨመረበት።

የግርጌ ማስታወሻዎች

ቃል በቃል “የመጽሐፍ ጥቅልል።”
ቃል በቃል “በመጽሐፍ ጥቅልሉ።”
ወይም “ከመጽሐፉ።”
ወይም “ጸሐፊ።”
ወይም “የመመገቢያ ክፍል።”
ወይም “ከመጽሐፉ።”
ወይም “ከመጽሐፉ።”
ወይም “የቤተ መንግሥት ባለሥልጣናቱ።”
ወይም “ቤተ መንግሥት።”
ወይም “ከመጽሐፉ።”
ወይም “በመጽሐፉ።”
ከኅዳር አጋማሽ እስከ ታኅሣሥ አጋማሽ ያለውን ጊዜ ያመለክታል። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ15ን ተመልከት።
ቃል በቃል “ዘሩንና።”
ወይም “መጽሐፍ።”