ኤርምያስ 42:1-22

  • ሕዝቡ ኤርምያስን እንዲጸልይላቸው ለመኑት (1-6)

  • ይሖዋ “ወደ ግብፅ አትሂዱ” አላቸው (7-22)

42  ከዚያም የሠራዊቱ አለቆች ሁሉ፣ የቃሬሃ ልጅ ዮሃናን፣+ የሆሻያህ ልጅ የዛንያህ* እና ሕዝቡ ሁሉ ከትንሹ እስከ ትልቁ ቀርበው  ነቢዩ ኤርምያስን እንዲህ አሉት፦ “ሞገስ ለማግኘት የምናቀርበውን ልመና እባክህ ስማ፤ ስለ እኛና ስለ እነዚህ ቀሪዎች ሁሉ ወደ አምላክህ ወደ ይሖዋ ጸልይ፤ ይኸው እንደምታየው ከብዙዎች መካከል የቀረነው ጥቂቶች ብቻ ነን።+  አምላክህ ይሖዋ በየት መሄድ እንደሚገባንና ምን ማድረግ እንዳለብን ይንገረን።”  ነቢዩ ኤርምያስ እንዲህ ሲል መለሰላቸው፦ “እሺ፣ ሰምቻችኋለሁ፤ በጠየቃችሁኝ መሠረት ወደ አምላካችሁ ወደ ይሖዋ እጸልያለሁ፤ ይሖዋ የሚመልስላችሁንም ቃል ሁሉ እነግራችኋለሁ። አንድም ቃል አላስቀርባችሁም።”  እነሱም ለኤርምያስ እንዲህ ብለው መለሱለት፦ “አምላክህ ይሖዋ በአንተ በኩል እንዳዘዘን ባናደርግ፣ ይሖዋ በእኛ ላይ እውነተኛና ታማኝ ምሥክር ይሁን።  የአምላካችንን የይሖዋን ቃል በመታዘዝ መልካም እንዲሆንልን፣ ነገሩ ቢስማማንም ባይስማማንም፣ ወደ እሱ የምንልክህ አምላካችን ይሖዋ የሚለውን ሁሉ እንፈጽማለን።”  ከአሥር ቀን በኋላ የይሖዋ ቃል ወደ ኤርምያስ መጣ።  ስለዚህ የቃሬሃን ልጅ ዮሃናንን፣ ከእሱ ጋር የነበሩትን የሠራዊቱን አለቆች ሁሉ እንዲሁም ሕዝቡን ሁሉ ከትንሹ እስከ ትልቁ ድረስ ጠራ።+  እንዲህም አላቸው፦ “ሞገስ ለማግኘት ያሰማችሁትን ልመና በፊቱ እንዳቀርብ ወደ እሱ የላካችሁኝ የእስራኤል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ 10  ‘በእርግጥ በዚህች ምድር ላይ የምትኖሩ ከሆነ፣ እገነባችኋለሁ እንጂ አላፈርሳችሁም፤ እተክላችኋለሁ እንጂ አልነቅላችሁም፤ በእናንተ ላይ ባመጣሁት ጥፋት እጸጸታለሁና።*+ 11  ከምትፈሩት ከባቢሎን ንጉሥ የተነሳ አትሸበሩ።’+ “‘ከእሱ የተነሳ አትፍሩ’ ይላል ይሖዋ፤ ‘አድናችሁና ከእጁ እታደጋችሁ ዘንድ እኔ ከእናንተ ጋር ነኝና። 12  ምሕረት አደርግላችኋለሁ፤+ እሱም ምሕረት ያደርግላችኋል፤ ወደ ገዛ ምድራችሁም ይመልሳችኋል። 13  “‘እናንተ ግን “አይሆንም፤ በዚህች ምድር ላይ አንኖርም!” ብትሉና የአምላካችሁን የይሖዋን ቃል ባትታዘዙ፣ 14  ደግሞም “አይሆንም፤ ጦርነት ወደማናይበት፣ የቀንደ መለከት ድምፅ ወደማንሰማበት ወይም ምግብ አጥተን ወደማንራብበት ወደ ግብፅ ምድር እንሄዳለን፤+ በዚያም እንኖራለን” ብትሉ፣ 15  እናንተ የይሁዳ ቀሪዎች ሆይ፣ እንግዲህ የይሖዋን ቃል ስሙ። የእስራኤል አምላክ፣ የሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ወደ ግብፅ ለመግባት ቆርጣችሁ ከተነሳችሁና በዚያ ለመኖር* ከሄዳችሁ፣ 16  የፈራችሁት ሰይፍ ራሱ በግብፅ ምድር ያገኛችኋል፤ የፈራችሁትም ረሃብ ወደ ግብፅ ተከትሏችሁ ይሄዳል፤ በዚያም ትሞታላችሁ።+ 17  በዚያ ለመኖር ሲሉ ወደ ግብፅ ለመሄድ ቆርጠው የተነሱ ሰዎች ሁሉ በሰይፍ፣ በረሃብና በቸነፈር* ይሞታሉ። በእነሱ ላይ ከማመጣው ጥፋት ከመካከላቸው የሚተርፍ ወይም የሚያመልጥ አይኖርም።”’ 18  “የእስራኤል አምላክ፣ የሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላልና፦ ‘ወደ ግብፅ ከሄዳችሁ፣ ቁጣዬና ንዴቴ በኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ላይ እንደወረደ ሁሉ+ በእናንተም ላይ ቁጣዬ ይወርዳል፤ እናንተም ለእርግማን፣ ለውርደትና ለነቀፋ ትዳረጋላችሁ፤ መቀጣጫም ትሆናላችሁ፤+ ይህን ቦታም ዳግመኛ አታዩትም።’ 19  “የይሁዳ ቀሪዎች ሆይ፣ ይሖዋ በእናንተ ላይ ተናግሯል። ወደ ግብፅ አትሂዱ። ዛሬ እንዳስጠነቀቅኳችሁ በእርግጥ እወቁ፤ 20  በደላችሁም ሕይወታችሁን* እንደሚያሳጣችሁ እወቁ። እንዲህ ስትሉ ወደ ይሖዋ አምላካችሁ ልካችሁኝ ነበርና፦ ‘ወደ አምላካችን ወደ ይሖዋ ስለ እኛ ጸልይ፤ አምላካችን ይሖዋም የሚለውን ነገር ሁሉ ንገረን፤ እኛም የተባልነውን እናደርጋለን።’+ 21  እኔም ዛሬ ነግሬአችኋለሁ፤ እናንተ ግን የአምላካችሁን የይሖዋን ቃልም ሆነ ወደ እናንተ ልኮኝ የነገርኳችሁን ሁሉ አትታዘዙም።+ 22  ስለዚህ ሄዳችሁ ልትኖሩበት በፈለጋችሁት ቦታ በሰይፍ፣ በረሃብና በቸነፈር እንደምትሞቱ በእርግጥ እወቁ።”+

የግርጌ ማስታወሻዎች

2ነገ 25:23 ላይ ያአዛንያህ፣ ኤር 43:2 ላይ ደግሞ አዛርያስ ተብሎ ተጠርቷል።
ወይም “አዝናለሁና።”
ወይም “ለተወሰነ ጊዜ በዚያ ለመኖር።”
ወይም “በበሽታ።”
ወይም “ነፍሳችሁን።”