አንደኛ ነገሥት 21:1-29

  • አክዓብ የናቡቴን የወይን እርሻ ለመውሰድ ፈለገ (1-4)

  • ኤልዛቤል ናቡቴን አስገደለችው (5-16)

  • ኤልያስ በአክዓብ ላይ የተናገረው የፍርድ መልእክት (17-26)

  • አክዓብ ራሱን አዋረደ (27-29)

21  እነዚህ ነገሮች ከተከናወኑ በኋላ ከኢይዝራኤላዊው ከናቡቴ የወይን እርሻ ጋር በተያያዘ አንድ ሁኔታ ተከሰተ፤ የወይን እርሻው የሚገኘው በኢይዝራኤል+ ውስጥ ከሰማርያው ንጉሥ ከአክዓብ ቤተ መንግሥት አጠገብ ነበር።  አክዓብ ናቡቴን እንዲህ አለው፦ “የወይን እርሻህ ከቤቴ አጠገብ ስለሚገኝ የአትክልት ቦታ እንዳደርገው ስጠኝ። እኔም በምትኩ ከዚህ የተሻለ የወይን እርሻ እሰጥሃለሁ። ከፈለግክ ደግሞ የቦታውን ዋጋ እሰጥሃለሁ።”  ናቡቴ ግን አክዓብን “የአባቶቼን ርስት ለአንተ መስጠት በይሖዋ ፊት ተገቢ ስላልሆነ ፈጽሞ የማላስበው ነገር ነው” አለው።+  በመሆኑም አክዓብ ኢይዝራኤላዊው ናቡቴ “የአባቶቼን ርስት አልሰጥህም” ስላለው ፊቱ ጠቁሮና አዝኖ ወደ ቤቱ ገባ። ከዚያም ፊቱን ወደ ግድግዳ አዙሮ ተኛ፤ ምግብ ለመብላትም ፈቃደኛ አልሆነም።  ሚስቱ ኤልዛቤልም+ ወደ እሱ ገብታ “ምግብ አልበላ እስኪልህ ድረስ እንዲህ ያዘንከው* ለምንድን ነው?” አለችው።  እሱም እንዲህ አላት፦ “ኢይዝራኤላዊውን ናቡቴን ‘የወይን እርሻህን በገንዘብ ሽጥልኝ። ከፈለግክ ደግሞ በምትኩ ሌላ የወይን እርሻ ልስጥህ’ ብዬው ነበር። እሱ ግን ‘የወይን እርሻዬን አልሰጥህም’ አለኝ።”  ሚስቱ ኤልዛቤልም “በእስራኤል ላይ ንጉሥ ሆነህ የምትገዛው አንተ አይደለህም? በል ተነስና እህል ቅመስ፤ ልብህም ደስ ይበለው። የኢይዝራኤላዊውን የናቡቴን የወይን እርሻ እኔ እሰጥሃለሁ” አለችው።+  ስለሆነም በአክዓብ ስም ደብዳቤዎች ጽፋ በእሱ ማኅተም አተመቻቸው፤+ ደብዳቤዎቹንም ናቡቴ በሚኖርበት ከተማ ወደሚገኙት ሽማግሌዎችና+ ታላላቅ ሰዎች ላከቻቸው።  በደብዳቤዎቹም ላይ እንዲህ ስትል ጻፈች፦ “ጾም አውጁ፤ ናቡቴንም በሕዝቡ ፊት በክብር ቦታ ላይ አስቀምጡት። 10  ሁለት የማይረቡ ሰዎችንም አምጥታችሁ ከፊት ለፊቱ አስቀምጡና ‘አምላክንና ንጉሡን ተራግመሃል!’+ በማለት እንዲመሠክሩበት አድርጉ።+ ከዚያም አውጥታችሁ በድንጋይ በመውገር ግደሉት።”+ 11  በመሆኑም የከተማዋ ሰዎች ማለትም እሱ በሚኖርበት ከተማ ያሉት ሽማግሌዎችና ታላላቅ ሰዎች ኤልዛቤል በላከችላቸው ደብዳቤዎች ላይ በተጻፈው መሠረት አደረጉ። 12  እነሱም ጾም አወጁ፤ ናቡቴም በሕዝቡ ፊት በክብር ቦታ ላይ እንዲቀመጥ አደረጉ። 13  ከዚያም ሁለት የማይረቡ ሰዎች መጥተው ፊት ለፊቱ ተቀመጡ፤ እነሱም በሕዝቡ ፊት ‘ናቡቴ አምላክንና ንጉሡን ተራግሟል!’ እያሉ በናቡቴ ላይ ይመሠክሩበት ጀመር።+ ከዚያም ወደ ከተማዋ ዳርቻ በመውሰድ በድንጋይ ወግረው ገደሉት።+ 14  እነሱም “ናቡቴ በድንጋይ ተወግሮ ሞቷል” በማለት ወደ ኤልዛቤል መልእክት ላኩባት።+ 15  ኤልዛቤልም ናቡቴ በድንጋይ ተወግሮ መሞቱን እንደሰማች አክዓብን “ኢይዝራኤላዊው ናቡቴ በገንዘብ ሊሸጥልህ ያልፈለገውን የወይን እርሻውን ተነስና ውረስ፤+ ምክንያቱም ናቡቴ በሕይወት የለም፤ ሞቷል” አለችው። 16  አክዓብም ናቡቴ መሞቱን እንደሰማ ተነስቶ የኢይዝራኤላዊውን የናቡቴን የወይን እርሻ ለመውረስ ወደዚያ ወረደ። 17  ሆኖም የይሖዋ ቃል ወደ ቲሽባዊው ወደ ኤልያስ+ እንዲህ ሲል መጣ፦ 18  “በሰማርያ+ የሚገኘውን የእስራኤልን ንጉሥ አክዓብን ለማግኘት ተነስተህ ወደዚያ ውረድ። እሱም የናቡቴን የወይን እርሻ ለመውረስ ሄዶ እዚያ ይገኛል። 19  እንዲህም በለው፦ ‘ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ሰው ገድለህ+ ንብረቱን ወሰድክ+ አይደል?”’ ከዚያም እንዲህ በለው፦ ‘ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ውሾች የናቡቴን ደም በላሱበት ቦታ የአንተንም ደም ይልሱታል።”’”+ 20  አክዓብም ኤልያስን “ጠላቴ ሆይ፣ አገኘኸኝ?” አለው፤+ እሱም እንዲህ አለው፦ “አዎ፣ አግኝቼሃለሁ። ‘እንግዲህ አንተ በይሖዋ ፊት መጥፎ የሆነውን ነገር ለማድረግ ቆርጠህ ስለተነሳህ*+ 21  ጥፋት አመጣብሃለሁ፤ እየተከታተልኩም ሙልጭ አድርጌ እጠርግሃለሁ፤ እንዲሁም በእስራኤል ውስጥ የሚገኘውን ምስኪኑንና ደካማውን+ ጨምሮ የአክዓብ የሆነውን ወንድ* ሁሉ አጠፋለሁ።+ 22  ቁጣዬን ስላነሳሳህና እስራኤላውያን ኃጢአት እንዲፈጽሙ ስላደረግክ ቤትህን እንደ ናባጥ ልጅ እንደ ኢዮርብዓም+ ቤትና እንደ አኪያህ ልጅ እንደ ባኦስ+ ቤት አደርገዋለሁ።’ 23  ኤልዛቤልን በተመለከተም ይሖዋ እንዲህ ብሏል፦ ‘ውሾች በኢይዝራኤል በሚገኘው ቁራሽ መሬት ላይ ኤልዛቤልን ይበሏታል።+ 24  ከአክዓብ ወገን የሆነውን፣ በከተማ ውስጥ የሚሞተውን ውሾች ይበሉታል፤ በሜዳ ላይ የሚሞተውን ደግሞ የሰማይ አሞሮች ይበሉታል።+ 25  በእርግጥም በሚስቱ በኤልዛቤል ተነድቶ+ በይሖዋ ፊት መጥፎ የሆነውን ነገር ለማድረግ ቆርጦ የተነሳ* እንደ አክዓብ ያለ አንድም ሰው የለም።+ 26  ይሖዋ ከእስራኤላውያን ፊት ያሳደዳቸው አሞራውያን እንዳደረጉት ሁሉ እሱም አስጸያፊ የሆኑ ጣዖቶችን* በመከተል እጅግ አስነዋሪ ነገር አደረገ።’”+ 27  አክዓብም ይህን እንደሰማ ልብሱን ቀደደ፤ ማቅም ለበሰ፤ ጾመ፤ እንዲሁም ማቅ ላይ ይተኛና በሐዘን ተኮራምቶ ይሄድ ነበር። 28  ከዚያም የይሖዋ ቃል ወደ ቲሽባዊው ወደ ኤልያስ እንዲህ ሲል መጣ፦ 29  “አክዓብ ስለ እሱ በተናገርኩት ነገር የተነሳ ራሱን እንዴት እንዳዋረደ ተመለከትክ?+ ራሱን በፊቴ ስላዋረደ ላመጣበት የነበረውን ጥፋት በእሱ ዘመን አላመጣም። ከዚህ ይልቅ በእሱ ቤት ላይ ጥፋት የማመጣው በልጁ ዘመን ነው።”+

የግርጌ ማስታወሻዎች

ቃል በቃል “መንፈስህ ያዘነው።”
ቃል በቃል “ራስህን ስለሸጥክ።”
ቃል በቃል “ግንብ ላይ የሚሸናውን።” ወንዶችን የሚያናንቅ የዕብራይስጥ አገላለጽ ነው።
ቃል በቃል “ራሱን የሸጠ።”
እዚህ ላይ የገባው የዕብራይስጥ ቃል “ፋንድያ” ከሚለው ቃል ጋር ዝምድና ሊኖረው የሚችል ሲሆን ንቀትን ለማመልከት ተሠርቶበታል።