ሁለተኛ ነገሥት 2:1-25

  • ኤልያስ በአውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ተወሰደ (1-18)

    • ኤልሳዕ የኤልያስን የነቢይነት ልብስ ለበሰ (13, 14)

  • ኤልሳዕ የኢያሪኮን ውኃ ፈወሰ (19-22)

  • ድቦች ከቤቴል የወጡትን ልጆች ቦጫጨቁ (23-25)

2  ይሖዋ ኤልያስን+ በአውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ የሚወስድበት ጊዜ ሲደርስ+ ኤልያስና ኤልሳዕ+ ከጊልጋል+ ተነስተው ጉዞ ጀመሩ።  ኤልያስም ኤልሳዕን “ይሖዋ ወደ ቤቴል እንድሄድ ስለላከኝ እባክህ አንተ እዚህ ቆይ” አለው። ኤልሳዕ ግን “ሕያው በሆነው በይሖዋና በሕያውነትህ* እምላለሁ፣ ከአንተ አልለይም” አለው። በመሆኑም አብረው ወደ ቤቴል+ ወረዱ።  ከዚያም በቤቴል የነበሩት የነቢያት ልጆች* ወጥተው ኤልሳዕን “ይሖዋ በአንተ ላይ ራስ የነበረውን ጌታህን ዛሬ ሊወስደው እንደሆነ አውቀሃል?”+ አሉት። እሱም “አዎ፣ አውቄአለሁ። ዝም በሉ” አለ።  ኤልያስም “ኤልሳዕ፣ ይሖዋ ወደ ኢያሪኮ+ እንድሄድ ስለላከኝ እባክህ አንተ እዚህ ቆይ” አለው። ኤልሳዕ ግን “ሕያው በሆነው በይሖዋና በሕያውነትህ* እምላለሁ፣ ከአንተ አልለይም” አለው። በመሆኑም አብረው ወደ ኢያሪኮ መጡ።  ከዚያም በኢያሪኮ የነበሩት የነቢያት ልጆች ወደ ኤልሳዕ ቀርበው “ይሖዋ በአንተ ላይ ራስ የነበረውን ጌታህን ዛሬ ሊወስደው እንደሆነ አውቀሃል?” አሉት። እሱም “አዎ፣ አውቄአለሁ። ዝም በሉ” አለ።  ኤልያስም ኤልሳዕን “ይሖዋ ወደ ዮርዳኖስ እንድሄድ ስለላከኝ እባክህ አንተ እዚህ ቆይ” አለው። ኤልሳዕ ግን “ሕያው በሆነው በይሖዋና በሕያውነትህ* እምላለሁ፣ ከአንተ አልለይም” አለው። በመሆኑም አብረው ሄዱ።  ከነቢያት ልጆች መካከል 50ዎቹ ተከትለዋቸው በመሄድ ራቅ ብለው ቆመው ያዩአቸው ነበር፤ በዚህ ጊዜ ሁለቱ ዮርዳኖስ አጠገብ ቆመው ነበር።  ከዚያም ኤልያስ የነቢይ ልብሱን+ አውልቆ በመጠቅለል ውኃውን መታው፤ ውኃውም ግራና ቀኝ ተከፈለ፤ ሁለቱም በደረቅ መሬት ተሻገሩ።+  ዮርዳኖስን እንደተሻገሩ ኤልያስ ኤልሳዕን “ከአንተ ከመወሰዴ በፊት እንዳደርግልህ የምትፈልገውን ጠይቀኝ” አለው። ኤልሳዕም “እባክህ፣ መንፈስህ+ በእጥፍ* ይሰጠኝ”+ አለው። 10  ኤልያስም “የጠየቅከው አስቸጋሪ ነገር ነው። ከአንተ ስወሰድ ካየኸኝ እንዳልከው ይሆንልሃል፤ አለዚያ ግን አይሆንልህም” አለው። 11  ሁለቱ እየተጨዋወቱ በመሄድ ላይ ሳሉ የእሳት ሠረገላና የእሳት ፈረሶች+ ድንገት መጥተው ለያዩአቸው፤ ኤልያስም በአውሎ ነፋስ ውስጥ ሆኖ ወደ ሰማይ ወጣ።+ 12  ኤልሳዕ ይህን ሲመለከት “አባቴ፣ አባቴ፣ እነሆ የእስራኤል ሠረገላና ፈረሰኞቹ!”+ በማለት ጮኸ። ኤልያስ ከዓይኑ ሲሰወርበትም የራሱን ልብስ ይዞ ለሁለት ቀደደው።+ 13  ከዚያም ከኤልያስ ላይ የወደቀውን የነቢይ ልብስ+ አነሳ፤ ተመልሶም በዮርዳኖስ ዳርቻ ቆመ። 14  እሱም ከኤልያስ ላይ በወደቀው የነቢይ ልብስ ውኃውን መታና እንዲህ አለ፦ “የኤልያስ አምላክ ይሖዋ የት አለ?” ውኃውንም ሲመታው ግራና ቀኝ ተከፈለ፤ ኤልሳዕም ተሻገረ።+ 15  በኢያሪኮ የሚኖሩ የነቢያት ልጆች ኤልሳዕን ከሩቅ ሲመለከቱት “የኤልያስ መንፈስ በኤልሳዕ ላይ አርፏል”+ አሉ። በመሆኑም እሱን ለማግኘት ሄዱ፤ በፊቱም መሬት ላይ ተደፍተው እጅ ነሱት። 16  እነሱም እንዲህ አሉት፦ “እነሆ፣ ከአገልጋዮችህ ጋር ብቁ የሆኑ 50 ሰዎች አሉ። እባክህ ይሂዱና ጌታህን ይፈልጉት። ምናልባት የይሖዋ መንፈስ* ወደ ላይ አንስቶት ከተራሮቹ በአንዱ ላይ ወይም ከሸለቆዎቹ በአንዱ ውስጥ ጥሎት ይሆናል።”+ እሱ ግን “አትላኳቸው” አላቸው። 17  ሆኖም እነሱ እስኪያፍር ድረስ ወተወቱት፤ እሱም “እሺ፣ ላኳቸው” አለ። እነሱም 50ዎቹን ሰዎች ላኩ፤ ሰዎቹም ለሦስት ቀን ያህል ፈለጉት፤ ሆኖም ሊያገኙት አልቻሉም። 18  ወደ ኤልሳዕ በተመለሱም ጊዜ ኤልሳዕ በኢያሪኮ+ ነበር። እሱም “‘አትሂዱ’ ብያችሁ አልነበረም?” አላቸው። 19  ከጊዜ በኋላም የከተማዋ ሰዎች ኤልሳዕን “ጌታዬ፣ ይኸው እንደምታየው ከተማዋ የምትገኘው ጥሩ ቦታ ላይ ነው፤+ ሆኖም ውኃው መጥፎ ነው፤ ምድሪቱም ፍሬ አትሰጥም”* አሉት። 20  እሱም “አነስ ባለ አዲስ ጎድጓዳ ሳህን ጨው ጨምራችሁ አምጡልኝ” አለ። እነሱም አመጡለት። 21  ከዚያም ውኃው ወደሚመነጭበት ቦታ ሄዶ ጨው ረጨበትና+ “ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘ይህን ውኃ ፈውሼዋለሁ። ከእንግዲህ ለሞት ምክንያት አይሆንም፤ ምድሪቱንም ፍሬ እንዳትሰጥ* አያደርጋትም’” አለ። 22  ኤልሳዕ በተናገረውም ቃል መሠረት ውኃው እስከ ዛሬ ድረስ እንደተፈወሰ ነው። 23  እሱም ከዚያ ተነስቶ ወደ ቤቴል ወጣ። በዚህ ጊዜ ከከተማዋ የወጡ ልጆች “አንተ መላጣ፣ ውጣ! አንተ መላጣ፣ ውጣ!” እያሉ ያፌዙበት ጀመር።+ 24  በመጨረሻም ዞር ብሎ ተመለከታቸውና በይሖዋ ስም ረገማቸው። ከዚያም ሁለት እንስት ድቦች+ ከጫካው ወጥተው 42 ልጆችን ቦጫጨቁ።+ 25  እሱም ጉዞውን በመቀጠል ወደ ቀርሜሎስ ተራራ+ ሄደ፤ ከዚያ ደግሞ ወደ ሰማርያ ተመለሰ።

የግርጌ ማስታወሻዎች

ወይም “በሕያው ነፍስህ።”
“የነቢያት ልጆች” የሚለው አገላለጽ ነቢያት ትምህርት የሚቀስሙበትን ትምህርት ቤት ወይም የነቢያትን ማኅበር የሚያመለክት ሳይሆን አይቀርም።
ወይም “በሕያው ነፍስህ።”
ወይም “በሕያው ነፍስህ።”
ወይም “ሁለት እጅ።”
ወይም “ነፋስ።”
“ውርጃ እያስከተለች ነው” ማለትም ሊሆን ይችላል።
“ውርጃ እንድታስከትል” ማለትም ሊሆን ይችላል።