ሁለተኛ ነገሥት 6:1-33

  • ኤልሳዕ የመጥረቢያው አናት እንዲንሳፈፍ አደረገ (1-7)

  • ኤልሳዕና የሶርያ ሠራዊት (8-23)

    • የኤልሳዕ አገልጋይ ዓይኖች ተከፈቱ (16, 17)

    • ኤልሳዕ የሶርያውያኑን አእምሮ አሳወረ (18, 19)

  • በተከበበችው ሰማርያ ውስጥ የተከሰተው ረሃብ (24-33)

6  የነቢያት ልጆች+ ኤልሳዕን እንዲህ አሉት፦ “ይኸው እንደምታየው አብረንህ የምንኖርበት ስፍራ በጣም ጠቦናል።  እባክህ ወደ ዮርዳኖስ እንሂድ። እያንዳንዳችን ከዚያ እንጨት እንቁረጥ፤ በዚያም የምንቀመጥበት መኖሪያ እንሥራ።” እሱም “እሺ ሂዱ” አላቸው።  ከመካከላቸው አንዱ “አንተስ ከአገልጋዮችህ ጋር ለመሄድ ፈቃደኛ ነህ?” አለው። እሱም “እሺ እሄዳለሁ” አለ።  ስለዚህ አብሯቸው ሄደ፤ ወደ ዮርዳኖስም መጥተው ዛፍ መቁረጥ ጀመሩ።  ከእነሱ አንዱ ዛፍ እየቆረጠ ሳለ የመጥረቢያው አናት ወልቆ ውኃው ውስጥ ወደቀ። ሰውየውም “ወየው ጌታዬ፣ ተውሼ ያመጣሁት መጥረቢያ እኮ ነው!” በማለት ጮኸ።  የእውነተኛው አምላክ ሰውም “የት ነው የወደቀው?” አለው። ሰውየውም ቦታውን አሳየው። እሱም እንጨት ቆርጦ ውኃው ውስጥ በመጣል የመጥረቢያው አናት እንዲንሳፈፍ አደረገ።  ከዚያም “በል አውጣው” አለው። ሰውየውም እጁን ዘርግቶ ወሰደው።  በዚህ ጊዜ የሶርያ ንጉሥ እስራኤልን ለመውጋት ዘምቶ ነበር።+ ከአገልጋዮቹ ጋር ከተማከረ በኋላ “እዚህ እዚህ ቦታ አብሬያችሁ እሰፍራለሁ” አለ።  ከዚያም የእውነተኛው አምላክ ሰው+ “ሶርያውያን በዚህ እየወረዱ ስለሆነ በዚህ በኩል እንዳታልፍ ተጠንቀቅ” በማለት ወደ እስራኤል ንጉሥ መልእክት ላከ። 10  የእስራኤልም ንጉሥ፣ የእውነተኛው አምላክ ሰው እንዳይሄድ ወዳስጠነቀቀው ስፍራ መልእክት ላከ። በዚህ መንገድ ኤልሳዕ ንጉሡን በተደጋጋሚ ጊዜ* ያስጠነቅቀው የነበረ ሲሆን ንጉሡም ከዚያ አካባቢ ይርቅ ነበር።+ 11  ይህ ጉዳይ የሶርያን ንጉሥ* እጅግ አበሳጨው፤ በመሆኑም አገልጋዮቹን ጠርቶ “ከመካከላችን ከእስራኤል ንጉሥ ጋር የወገነ ካለ ንገሩኝ!” አላቸው። 12  ከዚያም ከአገልጋዮቹ መካከል አንዱ “ንጉሡ ጌታዬ ሆይ፣ ኧረ ማንም የለም! አንተ መኝታ ቤትህ ውስጥ ሆነህ የምትናገረውን ነገር ለእስራኤል ንጉሥ የሚነግረው በእስራኤል ያለው ነቢዩ ኤልሳዕ ነው”+ አለው። 13  ንጉሡም “በሉ ሰዎች ልኬ እንዳስይዘው ሄዳችሁ የት እንደሚገኝ አጣሩ” አላቸው። በኋላም “ዶታን+ ነው ያለው” የሚል ወሬ ደረሰው። 14  እሱም ወዲያውኑ ፈረሶችን፣ የጦር ሠረገሎችንና ብዙ ሠራዊት ወደዚያ ላከ፤ እነሱም በሌሊት መጥተው ከተማዋን ከበቡ። 15  የእውነተኛው አምላክ ሰው አገልጋይ በማለዳ ተነስቶ ወደ ውጭ ሲወጣ በፈረሶችና በጦር ሠረገሎች የተጠናከረ ሠራዊት ከተማዋን መክበቡን አየ። አገልጋዩም ወዲያውኑ “ወየው ጌታዬ! ምን ብናደርግ ይሻላል?” አለ። 16  ኤልሳዕ ግን “አይዞህ፣ አትፍራ!+ ከእነሱ ጋር ካሉት ከእኛ ጋር ያሉት ይበልጣሉ”+ አለው። 17  ከዚያም ኤልሳዕ “ይሖዋ ሆይ፣ እባክህ ያይ ዘንድ ዓይኖቹን ክፈትለት”+ በማለት ጸለየ። ይሖዋም ወዲያውኑ የአገልጋዩን ዓይኖች ከፈተ፤ እሱም አየ፤ እነሆ የእሳት ፈረሶችና የጦር ሠረገሎች+ በኤልሳዕ ዙሪያ ተራራማውን አካባቢ ሞልተውት ነበር።+ 18  ሶርያውያኑ ወደ ኤልሳዕ መውረድ ሲጀምሩ ኤልሳዕ “እባክህ፣ ይህን ሕዝብ አሳውረው”+ በማለት ወደ ይሖዋ ጸለየ። እሱም ኤልሳዕ በጠየቀው መሠረት አሳወራቸው። 19  ኤልሳዕም “መንገዱ ይሄ አይደለም፤ ከተማዋም ይህች አይደለችም። ወደምትፈልጉት ሰው መርቼ እንዳደርሳችሁ እኔን ተከተሉኝ” አላቸው። ይሁን እንጂ ኤልሳዕ የወሰዳቸው ወደ ሰማርያ+ ነበር። 20  እነሱም ሰማርያ ሲደርሱ ኤልሳዕ “ይሖዋ ሆይ፣ እንዲያዩ ዓይኖቻቸውን ክፈት” አለ። ስለዚህ ይሖዋ ዓይኖቻቸውን ከፈተላቸው፤ እነሱም ሰማርያ ውስጥ መሆናቸውን አዩ። 21  የእስራኤል ንጉሥ ባያቸው ጊዜ ኤልሳዕን “አባቴ ሆይ፣ ልግደላቸው? ልፍጃቸው?” አለው። 22  እሱ ግን እንዲህ አለው፦ “አትግደላቸው። ለመሆኑ በሰይፍህ ወይም በቀስትህ ማርከህ የወሰድካቸውን ሰዎች ትገድላለህ? በል አሁን እንዲበሉና እንዲጠጡ ምግብና ውኃ ስጣቸው፤+ ከዚያም ወደ ጌታቸው ይመለሱ።” 23  በመሆኑም ታላቅ ግብዣ አደረገላቸው፤ እነሱም በሉ፣ ጠጡም፤ ከዚያም ወደ ጌታቸው እንዲመለሱ አሰናበታቸው። ከዚያ በኋላ የሶርያውያን+ ወራሪ ቡድን ወደ እስራኤል ምድር ተመልሶ አልመጣም። 24  ከጊዜ በኋላ የሶርያ ንጉሥ ቤንሃዳድ ሠራዊቱን ሁሉ ሰብስቦ በመውጣት ሰማርያን ከበበ።+ 25  በመሆኑም በሰማርያ ታላቅ ረሃብ ተከሰተ፤+ ከተማዋን ከበው በነበረበት ጊዜም አንድ የአህያ ጭንቅላት+ 80 የብር ሰቅል እንዲሁም አንድ አራተኛ የቃብ መስፈሪያ* የርግብ ኩስ 5 የብር ሰቅል እስኪያወጣ ድረስ ረሃቡ ጸንቶ ነበር። 26  የእስራኤል ንጉሥ በቅጥሩ ላይ ሲያልፍ አንዲት ሴት “ጌታዬ ንጉሥ ሆይ፣ እርዳን!” በማለት ወደ እሱ ጮኸች። 27  ንጉሡም “ይሖዋ ካልረዳሽ እኔ ከየት አምጥቼ ልረዳሽ እችላለሁ? ከአውድማው ነው ወይስ ከወይኑ ወይስ ከዘይት መጭመቂያው?” አላት። 28  ከዚያም “ለመሆኑ ችግርሽ ምንድን ነው?” ሲል ጠየቃት። እሷም እንዲህ ስትል መለሰች፦ “ይህች ሴት ‘ዛሬ የአንቺን ልጅ እንድንበላው አምጪው፤ ነገ ደግሞ የእኔን ልጅ እንበላለን’ አለችኝ።+ 29  በመሆኑም ልጄን ቀቅለን በላነው።+ በማግስቱ ‘የአንቺን ልጅ እንድንበላው አምጪው’ አልኳት። እሷ ግን ልጇን ደበቀችው።” 30  ንጉሡ ሴትየዋ ያለችውን ሲሰማ ልብሱን ቀደደ።+ በቅጥሩም ላይ በሚያልፍበት ጊዜ ሕዝቡ ንጉሡ ከልብሶቹ ሥር ማቅ መልበሱን አየ። 31  ከዚያም “የሻፋጥ ልጅ የኤልሳዕ ጭንቅላት ዛሬ አንገቱ ላይ ካደረ አምላክ እንዲህ ያድርግብኝ፤ ከዚህ የባሰም ያምጣብኝ!” አለ።+ 32  ኤልሳዕ ቤቱ ውስጥ ተቀምጦ ነበር፤ ሽማግሌዎቹም አብረውት ተቀምጠው ነበር። ንጉሡ አንድ ሰው ከፊቱ አስቀድሞ ላከ፤ ሆኖም መልእክተኛው ከመድረሱ በፊት ኤልሳዕ ሽማግሌዎቹን እንዲህ አላቸው፦ “ይህ የነፍሰ ገዳይ ልጅ+ ጭንቅላቴን ሊያስቆርጥ ሰው እንደላከ ታያላችሁ? በሉ መልእክተኛው ሲመጣ በሩን ዝጉት፤ ደግሞም እንዳይገባ በሩን ዘግታችሁ ያዙት። የጌታው ኮቴ ድምፅ ከኋላው ይሰማ የለም?” 33  እሱም ገና ከእነሱ ጋር እየተነጋገረ ሳለ መልእክተኛው ወደ እሱ ደረሰ፤ ንጉሡም “ይህ ከይሖዋ የመጣ ጥፋት ነው። ታዲያ ከዚህ በላይ ይሖዋን ለምን እጠብቃለሁ?” አለ።

የግርጌ ማስታወሻዎች

ወይም “ከአንድ ወይም ከሁለት ጊዜ በላይ።”
ቃል በቃል “የሶርያን ንጉሥ ልብ።”
አንድ ቃብ 1.22 ሊትር ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ለ14ን ተመልከት።