በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሁሉን ቻይ ሆኖም አሳቢ

ሁሉን ቻይ ሆኖም አሳቢ

“[ይሖዋ] እንዴት እንደተሠራን በሚገባ ያውቃልና፤ አፈር መሆናችንን ያስታውሳል።”—መዝ. 103:14

መዝሙሮች፦ 30, 10

1, 2. (ሀ) ሥልጣን ካላቸው የሰው ልጆች በተቃራኒ ይሖዋ ሰዎችን የሚይዘው እንዴት ነው? (ለ) በዚህ ርዕስ ውስጥ ምን እንመለከታለን?

ሥልጣንና ተሰሚነት ያላቸው ሰዎች፣ አብዛኛውን ጊዜ ‘ሥልጣናቸውን የሚያሳይ’ ነገር ሲያደርጉ ብሎም ሌሎችን ሲጨቁኑ ይስተዋላል። (ማቴ. 20:25፤ መክ. 8:9) ይሖዋ ግን እንዲህ ካሉ ሰዎች በእጅጉ የተለየ ነው! ይሖዋ ሁሉን ቻይ አምላክ ቢሆንም ፍጽምና ለሌላቸው የሰው ልጆች የላቀ አሳቢነትና ደግነት ያሳያል። ስሜታችንን ከግምት ያስገባል፤ እንዲሁም ለሚያስፈልጉን ነገሮች ትኩረት ይሰጣል። በተጨማሪም ይሖዋ “አፈር መሆናችንን” ስለሚያስታውስ በፍጹም ከአቅማችን በላይ አይጠብቅብንም።—መዝ. 103:13, 14

2 ይሖዋ ለአገልጋዮቹ አሳቢነት ያሳየባቸውን በርካታ ምሳሌዎች መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ማግኘት እንችላለን። ከእነዚህ ምሳሌዎች መካከል ሦስቱን በዚህ ርዕስ ውስጥ እንመለከታለን። በመጀመሪያ፣ አምላክ ብላቴናውን ሳሙኤልን ለሊቀ ካህናቱ ለኤሊ የፍርድ መልእክት እንዲያስተላልፍ በአሳቢነት የረዳው እንዴት እንደሆነ እናያለን። ሁለተኛ፣ ሙሴ እስራኤላውያንን እንዲመራ በተነገረው ወቅት ኃላፊነቱን ለመቀበል ሲያመነታ ይሖዋ በትዕግሥት የያዘው እንዴት እንደሆነ እንመረምራለን። በሦስተኛ ደረጃ ደግሞ አምላክ እስራኤላውያንን ከግብፅ ሲያወጣቸው እንዴት አሳቢነት እንዳሳያቸው እንመለከታለን። እነዚህን ሦስት ምሳሌዎች ስንመረምር፣ ስለ ይሖዋ ምን ትምህርት እንደምናገኝ እንዲሁም ያገኘነውን ትምህርት ተግባራዊ ማድረግ የምንችልበትን መንገድ ለማስተዋል እንሞክር።

ይሖዋ ለአንድ ብላቴና ያሳየው አሳቢነት

3. ብላቴናው ሳሙኤል አንድ ምሽት ምን አጋጠመው? ይህስ ምን ጥያቄ ያስነሳል? (በመግቢያው ላይ ያለውን ሥዕል ተመልከት።)

3 ሳሙኤል በማደሪያው ድንኳን ውስጥ ‘ይሖዋን ማገልገል’ የጀመረው ገና ትንሽ ልጅ እያለ ነው። (1 ሳሙ. 3:1) አንድ ምሽት ሳሙኤል ተኝቶ እያለ አንድ ያልተለመደ ነገር ተከሰተ። * (1 ሳሙኤል 3:2-10ን አንብብ።) ሳሙኤል አንድ ድምፅ ስሙን ሲጠራው ሰማ። ሳሙኤል፣ አረጋዊው ሊቀ ካህናት ኤሊ የጠራው ስለመሰለው ወደ እሱ እየሮጠ ሄዶ “አቤት፣ ጠራኸኝ?” አለው። ኤሊ ግን “አይ፣ አልጠራሁህም” በማለት መለሰለት። ይህ ሁኔታ ሁለት ጊዜ ሲደገም ኤሊ ሳሙኤልን እየጠራው ያለው አምላክ መሆኑን አስተዋለ። ስለዚህ ምን ምላሽ መስጠት እንዳለበት ለሳሙኤል ነገረው፤ ሳሙኤልም እንደታዘዘው አደረገ። ይሁንና ይሖዋ ሳሙኤልን ሲጠራው፣ ገና ከመጀመሪያው ማንነቱን ያልገለጸለት ለምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ መልሱን በቀጥታ አይናገርም፤ ሆኖም ቀጥሎ የተከናወኑት ነገሮች ይሖዋ ይህን ያደረገው ለብላቴናው ሳሙኤል አስቦለት ሊሆን እንደሚችል ይጠቁማሉ። እንዲህ የምንለው ለምንድን ነው?

4, 5. (ሀ) ሳሙኤል ለኤሊ አንድ መልእክት እንዲያስተላልፍ ይሖዋ ሲነግረው ምን አደረገ? (ለ) ይህ ታሪክ ስለ ይሖዋ ምን ያስተምረናል?

4 1 ሳሙኤል 3:11-18ን አንብብ። የይሖዋ ሕግ፣ ልጆች በዕድሜ የገፉ ሰዎችን በተለይም የሕዝብ አለቃ የሆኑትን እንዲያከብሩ ያዝዝ ነበር። (ዘፀ. 22:28፤ ዘሌ. 19:32) በመሆኑም ብላቴናው ሳሙኤል በጠዋት ተነስቶ ወደ ኤሊ በመሄድ፣ ይሖዋ የነገረውን አስደንጋጭ የፍርድ መልእክት በድፍረት ለኤሊ ማስተላለፍ ምን ያህል ሊከብደው እንደሚችል መገመት አያዳግትም! እንዲያውም ዘገባው “ሳሙኤል ራእዩን ለኤሊ መንገር ፈርቶ ነበር” ይላል። ሆኖም አምላክ፣ ሳሙኤልን እያነጋገረው ያለው እሱ መሆኑን ኤሊ እንዲያውቅ አደረገ። በዚህም የተነሳ ኤሊ ራሱ ሳሙኤልን ጠርቶ የይሖዋን መልእክት እንዲነግረው አዘዘው። ኤሊ “እሱ ከነገረህ ነገር ውስጥ አንዲት ቃል እንኳ [እንዳትደብቀኝ]” አለው። ሳሙኤልም በታዘዘው መሠረት ይሖዋ ያለውን “በሙሉ ምንም ሳይደብቅ ነገረው።”

5 በእርግጥ ሳሙኤል የተናገረው መልእክት ለኤሊ አዲስ ነገር አልነበረም። ስሙ ያልተጠቀሰ አንድ “የአምላክ ሰው” ቀደም ሲል ተመሳሳይ መልእክት ለሊቀ ካህናቱ ለኤሊ ነግሮት ነበር። (1 ሳሙ. 2:27-36) ስለ ሳሙኤልና ኤሊ የሚናገረው ታሪክ፣ ይሖዋ ምን ያህል አሳቢና ጥበበኛ እንደሆነ ያሳያል።

6. አምላክ ብላቴናውን ሳሙኤልን የረዳበት መንገድ ምን ያስተምረናል?

6 አንተም ወጣት ከሆንክ፣ የሚያጋጥሙህን ተፈታታኝ ሁኔታዎችና ስሜትህን ይሖዋ እንደሚረዳልህ ስለ ሳሙኤል ከሚናገረው ዘገባ መማር ትችላለህ። ምናልባትም ዓይናፋር በመሆንህ ምክንያት ለትላልቅ ሰዎች የመንግሥቱን መልእክት ማካፈል ወይም ከእኩዮችህ ለየት ብለህ መታየት ይከብድህ ይሆናል። ያም ቢሆን ይሖዋ አንተን መርዳት እንደሚፈልግ እርግጠኛ ሁን። የልብህን አውጥተህ ለይሖዋ በጸሎት ንገረው። (መዝ. 62:8) እንደ ሳሙኤል ስላሉ ልጆች በሚናገሩ የመጽሐፍ ቅዱስ ዘገባዎች ላይ አሰላስል። በተጨማሪም አንተ የሚያጋጥሙህ ዓይነት ፈተናዎችን የተቋቋሙ ወጣትም ሆኑ አዋቂ ክርስቲያኖችን አማክር። እነዚህ ክርስቲያኖች ይሖዋ ባልጠበቁት መንገድ የረዳቸው እንዴት እንደሆነ ይነግሩህ ይሆናል።

ይሖዋ ለሙሴ ያሳየው አሳቢነት

7, 8. ይሖዋ ለሙሴ ለየት ያለ አሳቢነት ያሳየው እንዴት ነው?

7 ሙሴ 80 ዓመት ሲሆነው ይሖዋ አንድ ከባድ ኃላፊነት ሰጠው። ሙሴ እስራኤላውያንን ከግብፅ ባርነት ነፃ እንዲያወጣቸው ታዘዘ። (ዘፀ. 3:10) ለ40 ዓመት ያህል በምድያም ምድር እረኛ ሆኖ የኖረው ሙሴ እንዲህ ዓይነት ተልእኮ ሲሰጠው በጣም ደንግጦ መሆን አለበት። “ወደ ፈርዖን የምሄደውና እስራኤላውያንን ከግብፅ የማወጣው ለመሆኑ እኔ ማን ነኝ?” በማለት ጠየቀ። አምላክ ግን “እኔ ከአንተ ጋር እሆናለሁ” በማለት አበረታታው። (ዘፀ. 3:11, 12) አክሎም “[የእስራኤል ሽማግሌዎች] በእርግጥ ቃልህን ይሰማሉ” በማለት ቃል ገባለት። ያም ቢሆን ሙሴ “ቃሌንስ ባይሰሙ?” ብሎ ጠየቀው። (ዘፀ. 3:18፤ 4:1) ሙሴ አምላክን ‘ተሳስተህ ቢሆንስ?’ ያለው ያህል ነበር! ይሁን እንጂ ይሖዋ በሙሴ ላይ አልተቆጣም። እንዲያውም ተአምራት መፈጸም እንዲችል ለሙሴ ኃይል ሰጠው፤ ተአምር እንደፈጸመ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተገለጸ የመጀመሪያው ሰው ሙሴ ነው።—ዘፀ. 4:2-9, 21

8 ሙሴ ግን አንደበተ ርቱዕ እንዳልሆነ በመናገር የተሰጠውን ተልእኮ መቀበል እንደማይችል ገለጸ። ይሖዋም “በምትናገርበት ጊዜ እኔ ከአንተ ጋር እሆናለሁ፤ የምትናገረውንም ነገር አስተምርሃለሁ” አለው። ሙሴ በዚህ ጊዜስ አመለካከቱን ለማስተካከል ፈቃደኛ ሆኖ ይሆን? አልሆነም፤ ከዚህ ይልቅ ሌላ ሰው እንዲልክ አምላክን በትሕትና ጠየቀው። በዚህ ጊዜ ይሖዋ ተቆጣ። ያም ቢሆን ለሙሴ ቃለ አቀባይ እንዲሆንለት አሮንን በመሾም አሁንም ለሙሴ አሳቢነት አሳይቶታል።—ዘፀ. 4:10-16

9. ይሖዋ ለሙሴ ትዕግሥትና አሳቢነት ማሳየቱ ሙሴ ኃላፊነቱን ሲወጣ የጠቀመው እንዴት ነው?

9 ይህ ዘገባ ስለ ይሖዋ ምን ያስተምረናል? ይሖዋ ሁሉን ቻይ አምላክ እንደመሆኑ መጠን ሙሴ ፈርቶት ወዲያውኑ እንዲታዘዘው ማድረግ ይችል ነበር። ሆኖም ትሑት የሆነውን አገልጋዩን በማበረታታት ትዕግሥትና ደግነት አሳይቶታል። እንዲህ ያለ አሳቢነት ማሳየቱ ያስገኘው ጥቅም ይኖር ይሆን? በሚገባ! ሙሴ ታላቅ መሪ መሆን ችሏል፤ በተጨማሪም ሌሎችን በገርነትና በአሳቢነት በመያዝ የይሖዋን ምሳሌ ተከትሏል።—ዘኁ. 12:3

ከሌሎች ጋር ባለህ ግንኙነት የይሖዋን ምሳሌ ትከተላለህ? (አንቀጽ 10⁠ን ተመልከት)

10. እንደ ይሖዋ አሳቢነት ማሳየታችን ምን ጥቅም አለው?

10 ከዚህ ዘገባ የምናገኘውን ትምህርት ተግባራዊ ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው? ባሎች፣ ወላጆች ወይም የጉባኤ ሽማግሌዎች በሌሎች ላይ በተወሰነ መጠን ሥልጣን አላቸው። ከዚህ አንጻር ባሎች ለሚስቶቻቸው፣ ወላጆች ለልጆቻቸው እንዲሁም ሽማግሌዎች ለጉባኤው አባላት አሳቢነት፣ ደግነትና ትዕግሥት በማሳየት የይሖዋን ምሳሌ መከተላቸው ምንኛ አስፈላጊ ነው! (ቆላ. 3:19-21፤ 1 ጴጥ. 5:1-3) እነዚህ ክርስቲያኖች ይሖዋንና ታላቁን ሙሴ ኢየሱስን ለመምሰል ጥረት የሚያደርጉ ከሆነ በቀላሉ የሚቀረቡ ይሆናሉ፤ አልፎ ተርፎም ለሌሎች የእረፍት ምንጭ መሆን ይችላሉ። (ማቴ. 11:28, 29) በተጨማሪም ግሩም ምሳሌ ይሆናሉ።—ዕብ. 13:7

ኃያል ሆኖም አሳቢ የሆነ አዳኝ

11, 12. ይሖዋ እስራኤላውያንን ያለአንዳች ስጋት ከግብፅ ወጥተው እንዲጓዙ የረዳቸው እንዴት ነው?

11 እስራኤላውያን በ1513 ዓ.ዓ. ግብፅን ለቀው ሲወጡ ቁጥራቸው ከሦስት ሚሊዮን በላይ ሳይሆን አይቀርም። በሕዝቡ መካከል ልጆች፣ አረጋውያን፣ አቅመ ደካሞች እንዲሁም የአካል ጉዳተኞች እንደሚኖሩ መገመት ይቻላል። እንዲህ ያለውን እጅግ ብዙ ሕዝብ ከግብፅ እየመሩ ለማውጣት አስተዋይና አሳቢ የሆነ መሪ እንደሚያስፈልግ ጥያቄ የለውም። ይሖዋም በሙሴ አማካኝነት ሕዝቡን በመምራት እንዲህ ዓይነት መሪ መሆኑን አሳይቷል። በመሆኑም እስራኤላውያን ዕድሜ ልካቸውን ከኖሩበት አገር ሲወጡ አንዳች ፍርሃት አልተሰማቸውም።—መዝ. 78:52, 53

12 ይሖዋ፣ ሕዝቡን ያለአንዳች ስጋት እንዲጓዙ የረዳቸው እንዴት ነው? በመጀመሪያ ደረጃ፣ ከግብፅ ሲወጡ “የጦርነት አሰላለፍ ተከትለው” በተደራጀ መንገድ እንዲጓዙ አድርጎ ነበር። (ዘፀ. 13:18) ይህም ሕዝቡ በእርግጥም እየመራቸው ያለው አምላካቸው መሆኑን እንዲተማመኑ አድርጓቸው መሆን አለበት። በተጨማሪም ይሖዋ “ቀን በደመና፣ ሌሊቱን ሙሉ ደግሞ በእሳት ብርሃን” ሕዝቡን በመምራት አብሯቸው መሆኑን የሚያረጋግጥ የሚታይ ማስረጃ ሰጥቷቸዋል። (መዝ. 78:14) ይሖዋ “አትፍሩ። አብሬያችሁ ሆኜ እመራችኋለሁ እንዲሁም እጠብቃችኋለሁ” ያላቸው ያህል ነበር። ደግሞም እንዲህ ያለ ማበረታቻ ማግኘታቸው ቀጥሎ ላጋጠማቸው ነገር አዘጋጅቷቸዋል።

እስራኤላውያን ቀይ ባሕርን ሲሻገሩ ይሖዋ በአሳቢነት ምን አድርጎላቸዋል? (አንቀጽ 13⁠ን ተመልከት)

13, 14. (ሀ) እስራኤላውያን ቀይ ባሕር ጋ ሲደርሱ ይሖዋ አሳቢነት ያሳያቸው እንዴት ነው? (ለ) ይሖዋ ከግብፃውያን የላቀ ኃይል እንዳለው ያሳየው እንዴት ነው?

13 ዘፀአት 14:19-22ን አንብብ። እስቲ ከእስራኤላውያን ጋር እንዳለህ አድርገህ አስብ፤ ከኋላህ የግብፃውያን ሠራዊት፣ ከፊትህ ደግሞ ቀይ ባሕር ስላለ ወዴት እንደምትሄድ ግራ ተጋብተሃል። በዚህ ጊዜ አምላክ እርምጃ ወሰደ። የደመናው ዓምድ ወደ ኋላ ሄዶ ከሕዝቡ በስተ ጀርባ ቆመ። የደመናው ዓምድ ግብፃውያንን ወደ እስራኤላውያን እንዳይደርሱ ያገዳቸው ከመሆኑም ሌላ አካባቢውን አጨለመባቸው። አንተ ያለህበት የእስራኤላውያን ሰፈር ግን በአስደናቂ ብርሃን ተሞልቷል! ከዚያም ሙሴ እጁን በባሕሩ ላይ ሲሰነዝር አየህ፤ በዚህ ጊዜ ከምሥራቅ የመጣ ኃይለኛ ነፋስ ውኃውን ለሁለት በመክፈል ባሕሩን ለመሻገር የሚያስችል ሰፊ መንገድ ከፈተ። አንተና ቤተሰብህ እንዲሁም የቤት እንስሶቻችሁ ከመላው ሕዝብ ጋር ሥርዓት ባለው መንገድ ቀይ ባሕርን መሻገር ጀመራችሁ። በድንገት ግን አንድ አስገራሚ ነገር አስተዋልክ። የባሕሩን ወለል ስትረግጠው ስምጥ ስምጥ የሚል ወይም የሚያንሸራትት ሳይሆን ደረቅ ነው፤ በመሆኑም እያዘገሙ የሚጓዙትን ጨምሮ ሁላችሁም ያለምንም ችግር ቀይ ባሕርን ተሻገራችሁ።

14 ዘፀአት 14:23, 26-30ን አንብብ። በዚህ መሃል፣ ትዕቢተኛውና ሞኙ ፈርዖን እየተንደረደረ ተከተላችሁ። ከዚያም ሙሴ በድጋሚ እጁን በባሕሩ ላይ ሰነዘረ። በዚህ ጊዜ፣ እንደ ግድግዳ ቆሞ የነበረው ውኃ በፈርዖንና በሠራዊቱ ላይ ተከለበሰ። ባሕሩ ወደ ቀድሞ ሁኔታው ሲመለስ ግብፃውያኑ በሙሉ አለቁ።—ዘፀ. 15:8-10

15. ይህ ታሪክ ስለ ይሖዋ ምን ያስተምረናል?

15 ይሖዋ የሥርዓት አምላክ መሆኑን ከዚህ ዘገባ መገንዘብ እንችላለን፤ ይህ ደግሞ ያለስጋት ለመኖር ይረዳናል። (1 ቆሮ. 14:33) ከዚህም ሌላ ይሖዋ ሕዝቡን በተለያዩ መንገዶች የሚንከባከብ አፍቃሪ እረኛ መሆኑን እንማራለን። ሕዝቡን ከጠላቶቻቸው ጥቃት ይከልላቸዋል እንዲሁም ይጠብቃቸዋል። ይህን ማወቃችን፣ ወደዚህ ሥርዓት ፍጻሜ ይበልጥ እየተቃረብን በሄድን መጠን በእጅጉ ያበረታታናል!—ምሳሌ 1:33

16. ይሖዋ እስራኤላውያንን ነፃ ስላወጣበት መንገድ መመርመራችን የሚጠቅመን እንዴት ነው?

16 በዛሬው ጊዜም ይሖዋ ለሕዝቡ በቡድን ደረጃ መንፈሳዊም ሆነ አካላዊ ጥበቃ ያደርግላቸዋል። በቅርቡ በሚመጣው ታላቅ መከራ ወቅትም እንዲህ ዓይነት ጥበቃ ማድረጉን ይቀጥላል። (ራእይ 7:9, 10) በመሆኑም ወጣቶችም ሆኑ አረጋውያን እንዲሁም ጤነኞችም ሆኑ የአካል ጉዳት ያለባቸው የአምላክ አገልጋዮች በታላቁ መከራ ወቅት በፍርሃት የሚርበደበዱበት ምክንያት የለም። * እንዲያውም ኢየሱስ ክርስቶስ “መዳናችሁ እየቀረበ ስለሆነ ቀጥ ብላችሁ ቁሙ፤ ራሳችሁንም ቀና አድርጉ” በማለት የሰጠውን መመሪያ ተግባራዊ ያደርጋሉ። (ሉቃስ 21:28) ከጥንቱ ፈርዖን ይበልጥ ኃያል የሆነው ጎግ ማለትም ግንባር የፈጠሩ ብሔራት፣ ጥቃት በሚሰነዝሩባቸው ጊዜም እንኳ የአምላክ ሕዝቦች ይሖዋ ጥበቃ እንደሚያደርግላቸው ሙሉ በሙሉ ይተማመናሉ። (ሕዝ. 38:2, 14-16) የአምላክ አገልጋዮች በዚያ ወቅት በልበ ሙሉነት የሚቆሙት ለምንድን ነው? ይሖዋ እንደማይለወጥ ስለሚያውቁ ነው። በታላቁ መከራ ወቅትም ይሖዋ አሳቢ አዳኝ መሆኑን ያረጋግጣል።—ኢሳ. 26:3, 20

17. (ሀ) ይሖዋ ለሕዝቡ አሳቢነት ስላሳየበት መንገድ ከሚያወሱ የመጽሐፍ ቅዱስ ዘገባዎች ምን ጥቅም ማግኘት እንችላለን? (ለ) በሚቀጥለው ርዕስ ላይ ምን እንመረምራለን?

17 ይሖዋ ሕዝቡን በደግነትና በአሳቢነት እንደሚንከባከብ፣ እንደሚመራና እንደሚያድን ከሚያሳዩ በርካታ ምሳሌዎች መካከል በዚህ ርዕስ ውስጥ የተመለከትነው ጥቂቶቹን ብቻ ነው። በእነዚህ ዘገባዎች ላይ ስታሰላስል፣ የይሖዋን ባሕርያት የሚያሳዩ ነጥቦችን ለማስተዋል ሞክር። ይህን ማድረግህ ግሩም የሆኑት የይሖዋ ባሕርያት ይበልጥ ግልጽ እንዲሆኑልህ ስለሚረዳህ ለእሱ ያለህ ፍቅርና በእሱ ላይ ያለህ እምነት ይጠናከራል። በሚቀጥለው ርዕስ ላይ በቤተሰብና በጉባኤ ውስጥ እንዲሁም በአገልግሎት ላይ ለሌሎች አሳቢነት በማሳየት የይሖዋን ምሳሌ መከተል የምንችለው እንዴት እንደሆነ እንመለከታለን።

^ አን.3 አይሁዳዊው የታሪክ ምሁር ጆሴፈስ ሳሙኤል በዚህ ወቅት የ12 ዓመት ልጅ እንደነበረ ተናግሯል።

^ አን.16 አርማጌዶንን በሕይወት ከሚያልፉ ሰዎች መካከል የአካል ጉዳት ያለባቸው ሰዎች እንደሚኖሩ መጠበቁ ምክንያታዊ ነው። ኢየሱስ ምድር ላይ በነበረበት ወቅት “ማንኛውንም ዓይነት ሕመም” ፈውሷል፤ ይህም አርማጌዶንን በሕይወት ለሚያልፉ ሰዎች ምን እንደሚያደርግ የሚያሳይ ናሙና ነው። (ማቴ. 9:35) ትንሣኤ የሚያገኙ ሰዎች ጤናማና የተሟላ አካል ይዘው እንደሚነሱ ምንም ጥርጥር የለውም።