በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሰዎች ስለ ጸሎት ምን ይላሉ?

ሰዎች ስለ ጸሎት ምን ይላሉ?

“ግራ በሚገባኝ ጊዜ ወደ አምላክ ስጸልይ እሱ ከጎኔ እንደሆነና እጄን ይዞ እየመራኝ እንዳለ ይሰማኛል።”​—ማሪያ

“ባለቤቴ ለ13 ዓመት ያህል ከካንሰር ጋር ስትታገል ቆይታ ሕይወቷ አለፈ። በወቅቱ በየዕለቱ ወደ አምላክ እጸልይ እንደነበር አስታውሳለሁ፤ ሥቃይ ውስጥ ሆኜ ስጮኽ እንደሚሰማኝ እርግጠኛ ነበርኩ። ይህን ማወቄ የመረጋጋት ስሜት እንዲሰማኝ አድርጓል።”​—ራውል

“ጸሎት አምላክ ለሰው ልጆች የሰጠው ግሩም ስጦታ ነው።”​—አርነ

ማሪያን፣ ራውልን እና አርነን ጨምሮ ብዙ ሰዎች ጸሎትን እንደ ልዩ ስጦታ አድርገው ይመለከቱታል። በጸሎት አማካኝነት አምላክን ማነጋገር፣ ማመስገንና እርዳታውን መጠየቅ እንደሚችሉ ይሰማቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ ወደ አምላክ መጸለይን አስመልክቶ በሚናገረው በሚከተለው ሐሳብ ላይ ሙሉ እምነት አላቸው፦ “በእሱ ላይ ያለን ትምክህት ይህ ነው፤ የምንጠይቀው ነገር ምንም ይሁን ምን ከፈቃዱ ጋር በሚስማማ ሁኔታ እስከለመንን ድረስ ይሰማናል።”—1 ዮሐንስ 5:14

በሌላ በኩል ደግሞ በርካታ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ጸሎት የሚናገረውን ሐሳብ መቀበል ይከብዳቸዋል። ስቲቭ የተባለ ሰው የተናገረውን እንደ ምሳሌ መጥቀስ እንችላለን። እንዲህ ብሏል፦ “17 ዓመት ሲሞላኝ ሦስት ጓደኞቼ በሁለት የተለያዩ አደጋዎች ሕይወታቸው አለፈ። አንዱ በመኪና አደጋ ሁለቱ ደግሞ ባሕር ውስጥ ሰጥመው ሞቱ።” በዚህ ጊዜ ስቲቭ ምን አደረገ? እንዲህ ብሏል፦ “ይህ ሁሉ የሆነበትን ምክንያት እንዲያሳውቀኝ ወደ አምላክ ጸለይኩ፤ ሆኖም ምንም ምላሽ አላገኘሁም። ስለዚህ ‘መጸለዬ ምን ዋጋ አለው?’ ብዬ ራሴን ጠየቅኩ።” ብዙ ሰዎች ጸሎታቸው መልስ እንዳላገኘ ስለሚሰማቸው መጸለያቸው ምንም ዋጋ እንደሌለው ያስባሉ።

ሰዎች የጸሎትን አስፈላጊነት የሚጠራጠሩባቸው ሌሎች ምክንያቶችም አሉ። አንዳንዶች አምላክ የሚያስፈልጉንን ወይም የሚያስጨንቁንን ነገሮች ጨምሮ ሁሉንም ነገሮች ስለሚያውቅ ለእሱ መንገር ምንም ጥቅም እንደሌለው ይሰማቸዋል።

ሌሎች ደግሞ ቀደም ሲል በሠሩት ኃጢአት ምክንያት አምላክ ጸሎታቸውን መስማት እንደማይፈልግ አድርገው ያስባሉ። ጄኒ የተባለች ሴት እንዲህ ብላለች፦ “ትልቁ ችግሬ ዋጋ ቢስ እንደሆንኩ የሚሰማኝ መሆኑ ነው። የምጸጸትባቸውን ነገሮች ስላደረግኩ አምላክ ጸሎቴን ይሰማል ብዬ መጠበቅ እንደሌለብኝ ራሴን አሳምነዋለሁ።”

አንተስ ስለ ጸሎት ምን ይሰማሃል? ጸሎትን በተመለከተ ቀደም ሲል የጠቀስናቸውን ሰዎች ዓይነት አመለካከት ወይም ጥርጣሬ ካለህ መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው አጥጋቢ መልስ ሊያጽናናህ ይችላል። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ጸሎት የሚናገረው ሐሳብ እምነት የሚጣልበት ነው፤ * እንደሚከተሉት ላሉ ጥያቄዎች መልስ እንድታገኝ ይረዳሃል፦

  • አምላክ በእርግጥ ጸሎታችንን ይሰማል?

  • አንዳንድ ጸሎቶች መልስ የማያገኙት ለምንድን ነው?

  • አምላክ ጸሎታችንን እንዲሰማ እንዴት መጸለይ ይኖርብናል?

  • መጸለያችን ምን ጥቅም ያስገኝልናል?

^ አን.9 መጽሐፍ ቅዱስ፣ ኢየሱስ ክርስቶስን ጨምሮ በርካታ የአምላክ አገልጋዮች ያቀረቡትን ጸሎት ይዟል። በተለምዶ ብሉይ ኪዳን ተብለው በሚጠሩት የዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ከ150 የሚበልጡ ጸሎቶች ይገኛሉ።