በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“የአምላካችን ቃል . . . ለዘላለም ጸንቶ ይኖራል”

“የአምላካችን ቃል . . . ለዘላለም ጸንቶ ይኖራል”

“ለምለሙ ሣር ይደርቃል፤ አበባው ይጠወልጋል፤ የአምላካችን ቃል ግን ለዘላለም ጸንቶ ይኖራል።”—ኢሳ. 40:8

መዝሙሮች፦ 95, 97

1, 2. (ሀ) መጽሐፍ ቅዱስ ባይኖር ሕይወት ምን ይመስል ነበር? (ለ) ከአምላክ ቃል ይበልጥ ጥቅም ማግኘት እንድንችል የሚረዳን ምንድን ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ ባይኖር ሕይወትህ ምን ሊመስል እንደሚችል አስበህ ታውቃለህ? የዕለት ተዕለት ሕይወትህን የምትመራበት አስተማማኝ መመሪያ ልታገኝ አትችልም። አምላክን፣ ሕይወትንና የወደፊቱን ጊዜ በተመለከተ ለሚፈጠሩብህ ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ የምታገኝበት ምንም መንገድ አይኖርም። እንዲሁም ይሖዋ በጥንት ጊዜ ከሰው ልጆች ጋር ስለነበረው ግንኙነት ልታውቅ አትችልም።

2 ደስ የሚለው ነገር እንዲህ ያለ አሳዛኝ ሁኔታ አላጋጠመንም። ምክንያቱም ይሖዋ ቃሉን መጽሐፍ ቅዱስን ሰጥቶናል። በውስጡ ያለው መልእክት ለዘላለም ጸንቶ እንደሚኖርም ዋስትና ሰጥቶናል። ሐዋርያው ጴጥሮስ በአንድ ወቅት ኢሳይያስ 40:8⁠ን ጠቅሶ ተናግሮ ነበር። በዚህ ጥቅስ ላይ የሚገኘው “የይሖዋ ቃል” የሚለው አገላለጽ በቀጥታ መጽሐፍ ቅዱስን የሚያመለክት ባይሆንም በመንፈስ መሪነት የተጻፈው ይህ ሐሳብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘውን መልእክት ለማመልከት ሊሠራበት ይችላል። (1 ጴጥሮስ 1:24, 25ን አንብብ።) እርግጥ ነው፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ ይበልጥ ጥቅም ማግኘት የምንችለው በአፍ መፍቻ ቋንቋችን የሚገኝ ከሆነ ነው። የአምላክን ቃል የሚወዱ ሰዎች ይህን እውነታ የተገነዘቡት ከረጅም ጊዜ በፊት ነው። ባለፉት መቶ ዘመናት የኖሩ ቅን ልብ ያላቸው ግለሰቦች ብዙ መሥዋዕት ቢያስከፍላቸውም ቅዱሳን መጻሕፍት እንዲተረጎሙና እንዲሰራጩ አድርገዋል። የእነዚህ ሰዎች ፍላጎት ከአምላክ ፈቃድ ጋር የሚስማማ ነው፤ የአምላክ ፈቃድ “ሁሉም ዓይነት ሰዎች እንዲድኑና የእውነትን ትክክለኛ እውቀት እንዲያገኙ ነው።”—1 ጢሞ. 2:3, 4

3. በዚህ ርዕስ ውስጥ ምን እንመረምራለን? (በመግቢያው ላይ ያለውን ሥዕል ተመልከት።)

3 በዚህ ርዕስ ውስጥ የአምላክ ቃል (1) የቋንቋ ለውጦችን፣ (2) ፖለቲካዊ ለውጦች በስፋት በሚነገረው ቋንቋ ላይ የፈጠሩትን ተጽዕኖ፣ (3) እንዳይተረጎም የተደረገውን ጥረት ተቋቁሞ የጸናው እንዴት እንደሆነ የሚያሳዩ አንዳንድ ምሳሌዎችን እንመለከታለን። እንዲህ ማድረጋችን ምን ጥቅም ያስገኝልናል? ለአምላክ ቃል ያለን አድናቆት እንዲጨምር ይረዳናል። በተጨማሪም ለእኛ ጥቅም ሲል ይህ መጽሐፍ እንዲጻፍ ላደረገውና የዚህ መጽሐፍ ባለቤት ለሆነው አካል ያለን ፍቅር እንዲያድግ ያደርጋል።—ሚክ. 4:2፤ ሮም 15:4

የቋንቋ ለውጦች

4. (ሀ) ቋንቋ በጊዜ ሂደት የሚለወጠው እንዴት ነው? (ለ) አምላካችን ለየትኛውም ቋንቋ እንደማያዳላ የሚያሳየው ምንድን ነው? ይህስ ምን እንዲሰማህ ያደርጋል?

4 ቋንቋ በጊዜ ሂደት ይለወጣል። በመሆኑም በአንድ ቋንቋ ውስጥ ያሉ ቃላትና አገላለጾች ቀደም ሲል ከነበራቸው ፈጽሞ የተለየ ትርጉም ሊኖራቸው ይችላል። አንተ የምትናገረው ቋንቋ እንኳ ምን ያህል እንደተለወጠ የሚያሳዩ ምሳሌዎችን ታስታውስ ይሆናል። አብዛኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ከተጻፈባቸው ከዕብራይስጥና ከግሪክኛ ጋር በተያያዘም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን ይነገር የነበረው ዕብራይስጥና ግሪክኛ በዛሬው ጊዜ ከሚነገረው ፈጽሞ የተለየ ነው። ስለዚህ በዛሬው ጊዜ የሚነገረውን ዕብራይስጥና ግሪክኛ የሚያውቁትን ጨምሮ ማንኛውም ሰው የአምላክን ቃል መረዳት ከፈለገ በዘመናዊ ቋንቋ የተዘጋጀውን መጽሐፍ ቅዱስ ሊያነብ ይገባል። አንዳንዶች መጽሐፍ ቅዱስን መጀመሪያ በተጻፈበት ቋንቋ ለማንበብ የጥንቱን ዕብራይስጥና ግሪክኛ መማር እንዳለባቸው ይሰማቸዋል። ሆኖም ይህ የሚያስቡትን ያህል ውጤታማ ላይሆን ይችላል። * ደስ የሚለው ነገር፣ መጽሐፍ ቅዱስ ሙሉ በሙሉም ሆነ በከፊል ከ3,200 በሚበልጡ ቋንቋዎች ተተርጉሟል። ከዚህ በግልጽ ማየት እንደሚቻለው ይሖዋ “በምድር ላይ [የሚኖር] ብሔር፣ ነገድ፣ ቋንቋና ሕዝብ ሁሉ” ከቃሉ ተጠቃሚ እንዲሆን ይፈልጋል። (ራእይ 14:6ን አንብብ።) ይህን ማወቅህ የማያዳላና አፍቃሪ አምላክ ወደሆነው ወደ ይሖዋ ይበልጥ እንድትቀርብ አያደርግህም?—ሥራ 10:34

5. ኪንግ ጄምስ ቨርዥን ከቋንቋና ከአምላክ ስም ጋር በተያያዘ ምን አስተዋጽኦ አበርክቷል?

5 ቋንቋ በጊዜ ሂደት ስለሚለወጥ መጽሐፍ ቅዱስ የተተረጎመባቸው ቋንቋዎችም መለወጣቸው አይቀርም። መጀመሪያ ሲዘጋጅ ለመረዳት ቀላል የነበረ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም እንኳ ከጊዜ በኋላ ለመረዳት አስቸጋሪ ሊሆን ይችላል። ወደ እንግሊዝኛ የተተረጎመን አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም እንደ ምሳሌ እንመልከት። ኪንግ ጄምስ ቨርዥን ለመጀመሪያ ጊዜ የተዘጋጀው በ1611 ነው። ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም በስፋት ከተሰራጩት የእንግሊዝኛ መጽሐፍ ቅዱሶች መካከል አንዱ ሲሆን በእንግሊዝኛ ቋንቋ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ አሳድሯል። * ይሁንና ኪንግ ጄምስ ቨርዥን “ጀሆቫ” የሚለውን የአምላክ ስም ያስገባው በጥቂት ቦታዎች ላይ ብቻ ነው። የአምላክ ስም በሚገኝባቸው ሌሎች የዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍት ጥቅሶች ላይ “ጌታ” የሚለውን ቃል ለየት ባለ የፊደል አጣጣል አስገብቷል። በቀጣይ እትሞቹም ላይ በክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ በሚገኙ አንዳንድ ጥቅሶች ላይ “ጌታ” የሚለውን ቃል ለየት ባለ የፊደል አጣጣል አስገብቷል። በዚህ መንገድ፣ ኪንግ ጄምስ ቨርዥን የአምላክ ስም በተለምዶ አዲስ ኪዳን ተብሎ በሚጠራው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ውስጥ እንደሚገኝ አረጋግጧል።

6. አዲስ ዓለም ትርጉምን በማግኘታችን አመስጋኝ የሆንነው ለምንድን ነው?

6 ሆኖም ዘመናት እያለፉ ሲሄዱ ኪንግ ጄምስ ቨርዥን ላይ የሚገኙ አንዳንድ አገላለጾች ጊዜ ያለፈባቸው ሆኑ። ከረጅም ጊዜ በፊት ከተዘጋጁ በሌላ ቋንቋ የሚገኙ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞችም ጋር በተያያዘ ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። በመሆኑም በዘመናዊ ቋንቋ የተዘጋጀውን አዲስ ዓለም ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ ማግኘታችን የሚያስደስት አይደለም? ይህ ትርጉም ሙሉ በሙሉ ወይም በከፊል ከ150 በሚበልጡ ቋንቋዎች ይገኛል፤ በመሆኑም በርካታ ሰዎች ይህን የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም የማንበብ አጋጣሚ አላቸው። ይህ ትርጉም ቀለል ያሉ ቃላትን ስለሚጠቀም የአምላክ ቃል ወደ ልባችን ዘልቆ እንዲገባ ያደርጋል። (መዝ. 119:97) አዲስ ዓለም ትርጉምን ልዩ የሚያደርገው ዋነኛው ምክንያት ግን የአምላክ ስም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ቀድሞ በነበረበት ቦታ ላይ ተመልሶ እንዲገባ ማድረጉ ነው።

ፖለቲካዊ ለውጦች

7, 8. (ሀ) በሦስተኛው መቶ ዘመን ዓ.ዓ. የነበሩ በርካታ አይሁዳውያን የዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍትን መረዳት የከበዳቸው ለምንድን ነው? (ለ) የግሪክ ሰብዓ ሊቃናት ምንድን ነው?

7 ፖለቲካዊ ለውጦች፣ በአንድ ወቅት ላይ በስፋት የሚነገረው ቋንቋ እንዲለወጥ ሊያደርጉ ይችላሉ። ታዲያ አምላክ እንዲህ ባሉ ለውጦች ምክንያት ሰዎች ቃሉን መረዳት ከባድ እንዳይሆንባቸው ያደረገው እንዴት ነው? ከዚህ በፊት የተፈጸመን አንድ ታሪክ መመልከታችን የዚህን ጥያቄ መልስ ለማግኘት ይረዳናል። የመጀመሪያዎቹን 39 የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት የጻፉት፣ እስራኤላውያን ወይም አይሁዳውያን ናቸው። “የአምላክ ቅዱስ ቃል” መጀመሪያ ላይ “በአደራ” የተሰጠው ለእነሱ ነበር። (ሮም 3:1, 2) ሆኖም በሦስተኛው መቶ ዘመን ዓ.ዓ. በርካታ አይሁዳውያን ዕብራይስጥ አይችሉም ነበር። ለምን? ታላቁ እስክንድር በርካታ አካባቢዎችን በቁጥጥሩ ሥር በማዋል የግሪክ ግዛት እንዲስፋፋ አድርጎ ነበር። (ዳን. 8:5-7, 20, 21) ግዛቱ እየተስፋፋ ሲሄድ በተለያዩ ቦታዎች ተበታትነው ይኖሩ የነበሩትን አይሁዳውያን ጨምሮ አብዛኞቹ ተገዢዎች የሚግባቡበት የጋራ ቋንቋ ግሪክኛ ሆነ። በመሆኑም በርካታ አይሁዳውያን የሚናገሩት ግሪክኛ ነበር፤ ይህም የዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍትን መረዳት አስቸጋሪ እንዲሆንባቸው አድርጓል። ታዲያ መፍትሔው ምን ይሆን?

8 በሦስተኛው መቶ ዘመን ዓ.ዓ. አጋማሽ አካባቢ የመጀመሪያዎቹ አምስት የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት ከዕብራይስጥ ወደ ግሪክኛ ተተረጎሙ። የተቀሩት የዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍት የትርጉም ሥራ ደግሞ በሁለተኛው መቶ ዘመን ዓ.ዓ. ተጠናቀቀ። የእነዚህ ቅዱሳን መጻሕፍት ስብስብ የግሪክ ሰብዓ ሊቃናት ተብሎ መጠራት ጀመረ። እስካሁን ባለው መረጃ መሠረት የሰብዓ ሊቃናት ትርጉም ሙሉውን የዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍት የያዘ የመጀመሪያው የትርጉም ሥራ ነው።

9. (ሀ) የሰብዓ ሊቃናት ትርጉምና ሌሎች ጥንታዊ ትርጉሞች የአምላክን ቃል ለሚያነቡ ሰዎች ምን ጥቅም አስገኝተዋል? (ለ) ከዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ይበልጥ የምትወደው የትኛውን ነው?

9 የሰብዓ ሊቃናት ትርጉም ግሪክኛ ተናጋሪ የነበሩ አይሁዳውያንና ሌሎች ሰዎች የዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍትን እንዲያነቡ ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክቷል። የአምላክን ቃል በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው መስማት ወይም ማንበብ መቻላቸው እነዚህን ሰዎች ምን ያህል አስደስቷቸው ሊሆን እንደሚችል እስቲ አስበው! ከጊዜ በኋላ ደግሞ የተለያዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ወደ ሲሪያክ፣ ጎቲክ፣ ላቲንና ብዙ ሰዎች ወደሚጠቀሙባቸው ሌሎች ቋንቋዎች ተተረጎሙ። በርካታ ሰዎች መረዳት በሚችሉት ቋንቋ መጽሐፍ ቅዱስን ማንበባቸው፣ ቃሉን እንዲወዱት አድርጓቸዋል፤ እኛ የምንወዳቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች እንዳሉን ሁሉ እነሱም የሚወዷቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ማግኘት እንደቻሉ ምንም ጥርጥር የለውም። (መዝሙር 119:162-165ን አንብብ።) በእርግጥም መጽሐፍ ቅዱስ ፖለቲካዊ ለውጦች በስፋት በሚነገረው ቋንቋ ላይ የፈጠሩትን ተጽዕኖ ተቋቁሞ ጸንቷል።

የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ሥራ ያጋጠመው ተቃውሞ

10. ጆን ዊክሊፍ በኖረበት ዘመን በርካታ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን የማግኘት አጋጣሚ ያልነበራቸው ለምንድን ነው?

10 ከፍተኛ ሥልጣን ያላቸው አካላት መጽሐፍ ቅዱስ ለተራው ሕዝብ እንዳይደርስ ጥረት ያደረጉባቸው ጊዜያት ነበሩ። ይሁንና ቅን ልብ ያላቸው ግለሰቦች እንዲህ ያለውን ተቃውሞ በድፍረት ተጋፍጠዋል። በ14ኛው መቶ ዘመን የኖረውን ጆን ዊክሊፍ የተባለ የሃይማኖት ምሁር እንደ ምሳሌ እንመልከት። ጆን ዊክሊፍ ሁሉም ሰው የአምላክን ቃል ማንበብ አለበት የሚል ጠንካራ እምነት ነበረው። ሆኖም በእሱ ዘመን፣ እንግሊዝ ውስጥ የሚኖሩ አብዛኞቹ ተራ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን ማግኘት አይችሉም ነበር። ለምን? አንደኛ፣ መጽሐፍ ቅዱስ የሚባዛው በእጅ በመገልበጥ ስለነበርና ይህም ከፍተኛ ወጪ ስለሚጠይቅ ብዙ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን ለመግዛት አቅማቸው አይፈቅድም። በተጨማሪም አብዛኞቹ ሰዎች ማንበብና መጻፍ አይችሉም ነበር። እርግጥ ነው፣ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መጽሐፍ ቅዱስ ሲነበብ ይሰሙ ይሆናል። ሆኖም በዚያ የሚሰሙት ነገር ላይገባቸው ይችላል። ምክንያቱም ቤተ ክርስቲያኗ የምትጠቀምበት መጽሐፍ ቅዱስ (ቩልጌት) የተጻፈው በላቲን ነበር። በመካከለኛው መቶ ዘመን ደግሞ ላቲን ተራው ሕዝብ የማይጠቀምበት የሞተ ቋንቋ ሆኖ ነበር ማለት ይቻላል! ታዲያ ተራው ሕዝብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘውን ውድ እውነት ማግኘት የሚችለው እንዴት ነው?—ምሳሌ 2:1-5

ጆን ዊክሊፍና ተከታዮቹ ሁሉም ሰው የአምላክን ቃል እንዲያገኝ የመርዳት ፍላጎት ነበራቸው። አንተስ እንዲህ የማድረግ ፍላጎት አለህ? (አንቀጽ 11⁠ን ተመልከት)

11. የዊክሊፍ መጽሐፍ ቅዱስ ምን ተጽዕኖ አሳድሯል?

11 በ1382 የዊክሊፍ መጽሐፍ ቅዱስ ተብሎ የሚጠራው የእንግሊዝኛ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ተዘጋጀ። ይህ ትርጉም በአጭር ጊዜ ውስጥ በዊክሊፍ ተከታዮች ዘንድ ተወዳጅነት አተረፈ። ተራው ሕዝብ የአምላክን ቃል እንዲረዳ የማገዝ ፍላጎት የነበራቸው ሎላርድ ተብለው የሚታወቁት ተጓዥ ሰባኪዎች፣ በመላው እንግሊዝ ከአንዱ መንደር ወደ ሌላው በእግር እየተዘዋወሩ ሰብከዋል። ሎላርዶች አብዛኛውን ጊዜ፣ ለሚያገኟቸው ሰዎች ከዊክሊፍ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ አንዳንድ ጥቅሶችን የሚያነቡላቸው ከመሆኑም ሌላ የዚህን መጽሐፍ ቅዱስ በእጅ የተገለበጡ ቅጂዎች ይሰጧቸው ነበር። ሎላርዶች ያደረጉት ጥረት በርካታ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብ የነበራቸው ፍላጎት እንደ አዲስ እንዲቀጣጠል አድርጓል።

12. ቀሳውስቱ ዊክሊፍንና ሥራውን በመቃወም ምን እርምጃ ወሰዱ?

12 ታዲያ ቀሳውስቱ ምን ተሰማቸው? ለዊክሊፍ፣ እሱ ላዘጋጀው መጽሐፍ ቅዱስና ለተከታዮቹ ከፍተኛ ጥላቻ እንዳላቸው አሳይተዋል። የሃይማኖት መሪዎቹ በሎላርዶች ላይ ከባድ ስደት አደረሱባቸው። እነዚህ የሃይማኖት መሪዎች የዊክሊፍን የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጂዎች የቻሉትን ያህል በመሰብሰብ አቃጠሉ። በተጨማሪም ዊክሊፍ ቢሞትም መናፍቅ ነው ተብሎ እንዲፈረድበት አደረጉ። ሆኖም በሕይወት የሌለን ሰው መቅጣት ስለማይቻል ቀሳውስቱ የዊክሊፍ አፅም ተቆፍሮ እንዲወጣና እንዲቃጠል ከዚያም አመዱ በስዊፍት ወንዝ ላይ እንዲበተን አደረጉ። ቤተ ክርስቲያኗ ይህን ሁሉ ጥረት ብታደርግም ሕዝቡ የነበረውን የአምላክን ቃል የማንበብና የመረዳት ከፍተኛ ፍላጎት ልትገታ አልቻለችም። ከዚያ በኋላ ባሉት መቶ ዓመታት በአውሮፓም ሆነ በሌሎች የዓለም ክፍሎች የሚኖሩ በርካታ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ ተራው ሕዝብ በሚናገረው ቋንቋ እንዲተረጎምና እንዲሰራጭ ማድረግ ጀመሩ።

ይሖዋ ‘የሚጠቅመንን ነገር ያስተምረናል’

13. የትኛውን ሐቅ እንገነዘባለን? ይህስ እምነታችንን የሚያጠናክረው እንዴት ነው?

13 በዘመናችን ያሉ ክርስቲያኖች የሰብዓ ሊቃናት ትርጉምን፣ የዊክሊፍ መጽሐፍ ቅዱስንና ኪንግ ጄምስ ቨርዥንን ጨምሮ የትኛውም የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም በቀጥታ በአምላክ መንፈስ መሪነት የተዘጋጀ እንዳልሆነ ይገነዘባሉ። ይሁንና የእነዚህን ትርጉሞች ጨምሮ ለሕትመት የበቁ በርካታ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞችን ታሪክ ስንመለከት አንድ ሐቅ እንገነዘባለን፦ ይሖዋ አስቀድሞ በተናገረው መሠረት ቃሉ ለዘላለም ጸንቶ ይኖራል። ታዲያ ይህን ማወቅህ ይሖዋ ቃል የገባቸው ሌሎች ተስፋዎችም አንድም ሳይቀር እንደሚፈጸሙ ያለህን እምነት አያጠናክረውም?—ኢያሱ 23:14

14. የመጽሐፍ ቅዱስን ታሪክ መመርመራችን ለአምላክ ያለን ፍቅር እንዲያድግ የሚያደርገው እንዴት ነው?

14 መጽሐፍ ቅዱስ ለዘመናት ጸንቶ የኖረው እንዴት እንደሆነ መመርመራችን እምነታችን እንዲጠናከርና ለይሖዋ ያለን ፍቅር እንዲያድግ ያደርጋል። * አምላክ መጀመሪያውኑም ቢሆን ቃሉን የሰጠን ለምንድን ነው? ቃሉ ጸንቶ እንደሚኖር ማረጋገጫ የሰጠንስ ለምንድን ነው? ይህን ያደረገው ስለሚወደንና የሚጠቅመንን ነገር ሊያስተምረን ስለሚፈልግ ነው። (ኢሳይያስ 48:17, 18ን አንብብ።) ይሖዋ ያሳየን ፍቅር እኛም እሱን እንድንወደውና ትእዛዛቱን እንድንፈጽም ሊያነሳሳን ይገባል።—1 ዮሐ. 4:19፤ 5:3

15. በቀጣዩ ርዕስ ላይ የትኞቹን ጥያቄዎች እንመለከታለን?

15 ለአምላክ ቃል ያለን አድናቆት ከቃሉ ሙሉ ጥቅም ለማግኘት ጥረት እንድናደርግ ሊያነሳሳን ይገባል። ታዲያ ከግል የመጽሐፍ ቅዱስ ንባባችን ይበልጥ ጥቅም ማግኘት የምንችለው እንዴት ነው? በአገልግሎት ላይ የምናገኛቸው ሰዎች በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ መርዳት የምንችለው እንዴት ነው? በስብሰባዎች ላይ የሚያስተምሩ ወንድሞች ትምህርታቸው ሙሉ በሙሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ እንዲሆን ማድረግ የሚችሉት እንዴት ነው? የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ በቀጣዩ ርዕስ ላይ እንመለከታለን።

^ አን.4 በኅዳር 1, 2009 መጠበቂያ ግንብ ላይ የወጣውን “ዕብራይስጥ እና ግሪክኛ መማር ያስፈልግሃል?” የሚለውን ርዕስ ተመልከት።

^ አን.5 በርካታ የእንግሊዝኛ ፈሊጣዊ አነጋገሮች የመጡት ከኪንግ ጄምስ ቨርዥን ነው።

^ አን.14 መጥተህ እንድትጎበኝ እንጋብዝሃለን!” የሚለውን ሣጥን ተመልከት።