በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የጥናት ርዕስ 35

ይሖዋ ትሑት አገልጋዮቹን ከፍ አድርጎ ይመለከታል

ይሖዋ ትሑት አገልጋዮቹን ከፍ አድርጎ ይመለከታል

“ይሖዋ . . . ትሑት የሆነውን ሰው ይመለከታል።”—መዝ. 138:6

መዝሙር 48 በየዕለቱ ከይሖዋ ጋር መሄድ

ማስተዋወቂያ *

1. ይሖዋ ትሑት ለሆኑ ሰዎች ምን አመለካከት አለው? አብራራ።

ይሖዋ ትሑት የሆኑ ሰዎችን ይወዳል። ከእሱ ጋር የጠበቀ ወዳጅነት መመሥረት የሚችሉት እውነተኛ ትሕትና የሚያንጸባርቁ ሰዎች ብቻ ናቸው። በሌላ በኩል ግን ይሖዋ ‘ትዕቢተኛ የሆኑ ሰዎች ወደ እሱ እንዲቀርቡ አይፈቅድም።’ (መዝ. 138:6) ሁላችንም ይሖዋን ማስደሰትና ከእሱ ጋር የጠበቀ ወዳጅነት መመሥረት እንፈልጋለን፤ በመሆኑም ትሕትናን እንድናዳብር የሚያነሳሳ በቂ ምክንያት አለን።

2. በዚህ ርዕስ ውስጥ ምን እንመረምራለን?

2 በዚህ ርዕስ ውስጥ የሚከተሉትን ሦስት ጥያቄዎች እንመረምራለን፦ (1) ትሕትና ምንድን ነው? (2) ትሕትናን ማዳበር ያለብን ለምንድን ነው? (3) ትሕትናችንን ሊፈትኑ የሚችሉ አንዳንድ ሁኔታዎች የትኞቹ ናቸው? ቀጥለን እንደምንመለከተው ትሕትናን በማዳበር የይሖዋን ልብ ደስ ማሰኘትና ራሳችንን መጥቀም እንችላለን።—ምሳሌ 27:11፤ ኢሳ. 48:17

ትሕትና ምንድን ነው?

3. ትሕትና ምንድን ነው?

3 ትሕትና የሚለው ቃል ለራስ የተጋነነ አመለካከት አለመያዝን እንዲሁም ከኩራት ወይም ከእብሪት ነፃ መሆንን ያመለክታል። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚገልጸው፣ ትሑት የሆነ ሰው ከይሖዋ አምላክና ከሌሎች ሰዎች አንጻር ስላለው ቦታ ትክክለኛ አመለካከት አለው። አንድ ሰው ትሑት ከሆነ፣ ሁሉም ሰው በሆነ መንገድ ከእሱ እንደሚበልጥ ይገነዘባል።—ፊልጵ. 2:3, 4

4-5. እውነተኛ ትሕትና ከላይ ከላይ በምናሳየው ምግባር ብቻ ሊለካ አይችልም የምንለው ለምንድን ነው?

4 አንዳንዶች ከላይ ሲታዩ ትሑት ይመስሉ ይሆናል። ምናልባትም በባሕርያቸው ዓይናፋር ወይም ዝምተኛ ሊሆኑ ይችላሉ። አሊያም ደግሞ በባሕላቸው ወይም በአስተዳደጋቸው ምክንያት ለሌሎች አክብሮት እንዳላቸው የሚያሳዩ ነገሮችን ያደርጉ ይሆናል። በውስጣቸው ግን በጣም ኩሩዎች ሊሆኑ ይችላሉ። ይዋል ይደር እንጂ እውነተኛ ማንነታቸው መገለጡ አይቀርም።—ሉቃስ 6:45

5 በሌላ በኩል ደግሞ አንዳንድ ሰዎች በራሳቸው የሚተማመኑ ስለሚመስሉ ወይም የተሰማቸውን ነገር ፊት ለፊት ስለሚናገሩ ብቻ ኩሩ ናቸው ማለት ላይሆን ይችላል። (ዮሐ. 1:46, 47) እርግጥ እንዲህ ያለ ባሕርይ ያላቸው ሰዎች በተፈጥሮ ባገኙት ችሎታ እንዳይመኩ መጠንቀቅ አለባቸው። በባሕርያችን ዓይናፋር ሆንም አልሆን ሁላችንም እውነተኛ ትሕትናን ለማዳበር ጥረት ማድረግ ይኖርብናል።

ሐዋርያው ጳውሎስ ትሑትና ለራሱ ሚዛናዊ አመለካከት ያለው ሰው ነበር (አንቀጽ 6⁠ን ተመልከት) *

6. ሐዋርያው ጳውሎስ በ1 ቆሮንቶስ 15:10 ላይ ከተናገረው ሐሳብ ምን ትምህርት እናገኛለን?

6 እስቲ የሐዋርያው ጳውሎስን ምሳሌ እንመልከት። ይሖዋ በተለያዩ ከተሞች ጉባኤዎችን ለማቋቋም ጳውሎስን በእጅጉ ተጠቅሞበታል። ምናልባትም በአገልግሎት ረገድ ከሌሎች የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያት ሁሉ ይበልጥ ብዙ ያከናወነው እሱ ሳይሆን አይቀርም። ያም ሆኖ ጳውሎስ ከሌሎች ወንድሞቹ እንደሚበልጥ አልተሰማውም። እንዲያውም “እኔ የአምላክን ጉባኤ አሳድድ ስለነበር ከሐዋርያት ሁሉ የማንስና ሐዋርያ ተብዬ ልጠራ የማይገባኝ ነኝ” በማለት በትሕትና ተናግሯል። (1 ቆሮ. 15:9) በተጨማሪም በይሖዋ ፊት ጥሩ አቋም ሊኖረው የቻለው በራሱ ብቃት ወይም ባከናወናቸው ነገሮች የተነሳ ሳይሆን በአምላክ ጸጋ እንደሆነ ገልጿል። (1 ቆሮንቶስ 15:10ን አንብብ።) ጳውሎስ በትሕትና ረገድ እንዴት ያለ ግሩም ምሳሌ ትቷል! ከእሱ እንደሚበልጡ ለማሳየት የሚሞክሩ ሰዎች ላሉበት ለቆሮንቶስ ጉባኤ በጻፈው ደብዳቤ ላይ እንኳ ስለ ራሱ በጉራ አልተናገረም።—2 ቆሮ. 10:10

ካርል ክላይን፣ የበላይ አካል አባል ሆኖ ያገለገለ ትሑት ወንድም (አንቀጽ 7⁠ን ተመልከት)

7. ኃላፊነት ያለው አንድ ወንድም ትሑት መሆኑን ያሳየው እንዴት ነው?

7 የበላይ አካል አባል ሆኖ ያገለገለው የወንድም ካርል ክላይን የሕይወት ታሪክ በርካታ የይሖዋ ሕዝቦችን አበረታቷል። ወንድም ካርል በሕይወቱ ውስጥ ስላሳለፋቸው የተለያዩ ተፈታታኝ ሁኔታዎች በትሕትና ተናግሯል። ለምሳሌ ያህል፣ በ1920ዎቹ ለመጀመሪያ ጊዜ ከቤት ወደ ቤት ካገለገለ በኋላ ይህ የአገልግሎት ዘርፍ በጣም ስለከበደው ለቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት ከቤት ወደ ቤት አላገለገለም። ከጊዜ በኋላ ደግሞ በቤቴል ሲያገለግል አንድ ወንድም በሰጠው ምክር ለተወሰነ ጊዜ ያህል ቅር ተሰኝቶ ነበር። በተጨማሪም በአንድ ወቅት ከፍተኛ የስሜት መቃወስ አጋጥሞት ነበር። ይሁን እንጂ በድርጅቱ ውስጥ ግሩም የአገልግሎት መብቶችን አግኝቷል። ወንድም ካርል በብዙዎች ዘንድ የሚታወቅ ወንድም ከመሆኑ አንጻር ድክመቶቹን በግልጽ መናገር ምን ያህል ትሕትና ጠይቆበት ሊሆን እንደሚችል እስቲ አስቡት! በርካታ ወንድሞችና እህቶች የወንድም ካርልን ግልጽና ልብ የሚነካ ተሞክሮ ሲያስታውሱ በጣም ይበረታታሉ። *

ትሕትናን ማዳበር ያለብን ለምንድን ነው?

8. አንደኛ ጴጥሮስ 5:6 ትሕትና ይሖዋን እንደሚያስደስተው የሚያሳየው እንዴት ነው?

8 ትሕትናን እንድናዳብር የሚያነሳሳን ዋነኛው ምክንያት ይህ ባሕርይ ይሖዋን ደስ ስለሚያሰኘው ነው። ሐዋርያው ጴጥሮስ ይህን ነጥብ ግልጽ የሚያደርግ ሐሳብ ተናግሯል። (1 ጴጥሮስ 5:6ን አንብብ።) “ተከታዬ ሁን” የተባለው መጽሐፍ፣ ጴጥሮስ የተናገረውን ሐሳብ ሲያብራራ እንዲህ ብሏል፦ “ትዕቢት ልክ እንደ መርዝ ነው። ለውድቀት ሊዳርግ ይችላል። እንዲህ ያለው ባሕርይ ጥሩ ተሰጥኦ ያለውን ሰው በአምላክ ፊት ዋጋ ቢስ ሊያደርገው ይችላል። በሌላ በኩል ደግሞ ትሕትና ዝቅ ተደርጎ የሚታየውን ሰው እንኳ ይሖዋ እንዲጠቀምበት ሊያደርገው ይችላል። . . . አንተም ትሕትና የምታሳይ ከሆነ አምላካችን ወሮታ ይከፍልሃል።” * ደግሞስ የይሖዋን ልብ ደስ ከማሰኘት የበለጠ ምን ነገር ሊኖር ይችላል?—ምሳሌ 23:15

9. ትሕትና ሌሎች ወደ እኛ እንዲቀርቡ የሚያደርገው እንዴት ነው?

9 ትሕትናን ማዳበራችን ይሖዋን ደስ ከማሰኘት ባለፈ ሌሎች በርካታ ጥቅሞችን ያስገኝልናል። ትሕትና፣ ሰዎች ወደ እኛ እንዲቀርቡ ያደርጋል። ይህ የሆነበትን ምክንያት ለመረዳት ራሳችሁን በሌሎች ቦታ ለማስቀመጥ ሞክሩ። (ማቴ. 7:12) እኔ ያልኩት ብቻ ካልሆነ ከሚልና የሌሎችን አስተያየት ለመቀበል ፈቃደኛ ካልሆነ ሰው ጋር መሆን የሚያስደስተው ማን አለ? በአንጻሩ ግን ሁላችንም ‘የሌላውን ስሜት ከሚረዱ፣ የወንድማማች መዋደድ ካላቸው፣ ከአንጀት ከሚራሩና ትሑታን ከሆኑ’ የእምነት ባልንጀሮቻችን ጋር መሆን ደስ ይለናል። (1 ጴጥ. 3:8) እኛ እንዲህ ያለ ባሕርይ ካላቸው ሰዎች ጋር መሆን እንደሚያስደስተን ሁሉ ትሑት ከሆንን ሌሎችም ከእኛ ጋር መሆን ያስደስታቸዋል።

10. ትሕትና ከአላስፈላጊ ውጥረት የሚጠብቀን እንዴት ነው?

10 በተጨማሪም ትሕትና ከአላስፈላጊ ውጥረት ይጠብቀናል። አንዳንድ ጊዜ ፍትሕ የጎደላቸው ወይም ትክክል ያልሆኑ ነገሮች እንደተፈጸሙ ይሰማን ይሆናል። ጠቢብ የሆነው ንጉሥ ሰለሞን ይህን ሐቅ እንዲህ በማለት ገልጾታል፦ “አገልጋዮች በፈረስ ተቀምጠው ሲጓዙ፣ መኳንንት ግን እንደ አገልጋዮች በእግራቸው ሲሄዱ አይቻለሁ።” (መክ. 10:7) ጥሩ ችሎታ ያላቸው ሰዎች ተገቢውን እውቅና የማያገኙበት ጊዜ አለ። ያን ያህል ችሎታ የሌላቸው ሰዎች ደግሞ የበለጠ ክብር ሲሰጣቸው እናያለን። ያም ቢሆን ሰለሞን አሉታዊ በሆኑ ነገሮች ላይ ከልክ በላይ ከማተኮር ይልቅ እውነታውን መቀበል ጥበብ እንደሆነ ተገንዝቧል። (መክ. 6:9) ትሑት ከሆንን አንዳንድ ነገሮች እኛ እንዳሰብናቸው ባይሆኑ እንኳ ሁኔታውን ተቀብለን ማለፍ ቀላል ይሆንልናል።

ትሕትናችንን ሊፈትኑ የሚችሉ አንዳንድ ሁኔታዎች የትኞቹ ናቸው?

እንዲህ ያሉ ሁኔታዎች ትሕትናችንን ሊፈትኑ የሚችሉት እንዴት ነው? (ከአንቀጽ 11-12⁠ን ተመልከት) *

11. ምክር ሲሰጠን ምላሻችን ምን ሊሆን ይገባል?

11 በየዕለቱ ትሕትናችንን ሊፈትኑ የሚችሉ በርካታ ሁኔታዎች ያጋጥሙናል። እስቲ አንዳንዶቹን እንደ ምሳሌ እንመልከት። ምክር ሲሰጠን። አንድ ሰው ሁኔታችን አሳስቦት እኛን እስከ መምከር ከደረሰ፣ ከምናስበው በላይ አልፈን ሄደን ሊሆን እንደሚችል ማስታወስ ይኖርብናል። ምክር ሲሰጠን በአብዛኛው የሚቀናን ምክሩን ላለመቀበል ሰበብ አስባብ መደርደር ሊሆን ይችላል። ምክሩን የሰጠንን ግለሰብ ወይም ምክሩ የተሰጠበትን መንገድ እንተች ይሆናል። ትሑት ከሆንን ግን ለተሰጠን ምክር ትክክለኛውን አመለካከት ለመያዝ ጥረት እናደርጋለን።

12. በምሳሌ 27:5, 6 መሠረት አንድ ሰው ምክር ሲሰጠን አመስጋኝ መሆን ያለብን ለምንድን ነው? በምሳሌ አስረዳ።

12 ትሑት ሰው ምክር ሲሰጠው በደስታ ይቀበላል። ነገሩን በምሳሌ ለማስረዳት ያህል፣ በአንድ ክርስቲያናዊ ስብሰባ ላይ ተገኝተሃል እንበል። ከተለያዩ ወንድሞችና እህቶች ጋር ስትጫወት ከቆየህ በኋላ አንድ ወንድም ለብቻህ ወስዶ ጥርስህ ላይ የሆነ ነገር ስላለ እንድታጸዳው ይነግርሃል። ሁኔታው ሊያሳፍርህ እንደሚችል የታወቀ ነው። ሆኖም ወንድም እንዲህ ብሎ ስለነገረህ አመስጋኝ አትሆንም? እንዲያውም ‘ምነው የሆነ ሰው ቀደም ብሎ በነገረኝ ኖሮ!’ ብለህ ልታስብ ትችላለህ። በተመሳሳይም አንድ የእምነት ባልንጀራችን ድፍረት በማሳየት አስፈላጊውን ምክር ሲሰጠን ትሑት በመሆን ምክሩን በአመስጋኝነት መቀበል ይኖርብናል። እንዲህ ያለ ምክር የሰጠንን ሰው እንደ ወዳጃችን እንጂ እንደ ጠላታችን አናየውም።—ምሳሌ 27:5, 6ን አንብብ፤ ገላ. 4:16

ሌሎች የአገልግሎት መብት ሲሰጣቸው ትሑት መሆን የሚያስፈልገን ለምንድን ነው? (ከአንቀጽ 13-14⁠ን ተመልከት) *

13. ሌሎች የአገልግሎት መብት ሲሰጣቸው፣ ትሑት እንደሆንን ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

13 ሌሎች የአገልግሎት መብት ሲሰጣቸው። ጄሰን የተባለ የጉባኤ ሽማግሌ እንዲህ ሲል በሐቀኝነት ተናግሯል፦ “ሌሎች ወንድሞች የአገልግሎት መብት ሲሰጣቸው ‘ይህ መብት ለእኔ ያልተሰጠኝ ለምንድን ነው?’ ብዬ አስባለሁ።” አንተስ እንዲህ ተሰምቶህ ያውቃል? እርግጥ ነው፣ ተጨማሪ የአገልግሎት መብቶችን ለማግኘት ‘መጣጣር’ ስህተት አይደለም። (1 ጢሞ. 3:1) ሆኖም አስተሳሰባችንን መጠበቅ ይኖርብናል። ካልተጠነቀቅን በልባችን ውስጥ ኩራት ሊያቆጠቁጥ ይችላል። ለምሳሌ ያህል፣ አንድ ክርስቲያን አንድን ሥራ ለማከናወን ከሁሉ የተሻለ ብቃት ያለው እሱ እንደሆነ ማሰብ ሊጀምር ይችላል። ወይም አንዲት ክርስቲያን ሚስት ‘የእኔ ባል ከወንድም እገሌ የተሻለ ብቃት አለው!’ ብላ ልታስብ ትችላለች። ትሑት ከሆንን ግን እንዲህ ያለ የኩራት መንፈስ በውስጣችን አይኖርም።

14. ሙሴ፣ ሌሎች ሰዎች መብት ሲያገኙ ከሰጠው ምላሽ ምን ትምህርት እናገኛለን?

14 ሙሴ፣ ሌሎች ሰዎች መብት ሲያገኙ ከሰጠው ምላሽ ትልቅ ትምህርት ማግኘት እንችላለን። ሙሴ የእስራኤልን ብሔር እንዲመራ ለተሰጠው ኃላፊነት አድናቆት ነበረው። ሆኖም ይሖዋ ሌሎች አገልጋዮቹ የሙሴን ሥራ እንዲጋሩ ሲፈቅድ ሙሴ ምን ተሰማው? ቅናት አላደረበትም። (ዘኁ. 11:24-29) ሕዝቡን በመዳኘቱ ሥራ ሌሎችም እንዲያግዙት የተደረገውን ዝግጅት በትሕትና ተቀብሏል። (ዘፀ. 18:13-24) ይህ ዝግጅት እስራኤላውያን የተሻለ አገልግሎት እንዲያገኙ ያደርጋል። ከዚህ አንጻር፣ ሙሴ ይህን ዝግጅት በትሕትና መቀበሉ ከመብቱ ይልቅ ለሌሎች ጥቅም እንደሚያስብ ያሳያል። እንዴት ያለ ግሩም ምሳሌ ትቶልናል! ይሖዋ እንዲጠቀምብን ከፈለግን ትሕትናችን ከችሎታችን ልቆ መታየት እንዳለበት እናስታውስ። “ይሖዋ ከፍ ያለ ቢሆንም ትሑት የሆነውን ሰው ይመለከታል።”—መዝ. 138:6

15. በርካታ ወንድሞችና እህቶች ምን ለውጥ አጋጥሟቸዋል?

15 ያለንበት ሁኔታ ሲለወጥ። በይሖዋ አገልግሎት የበርካታ ዓመታት ተሞክሮ ያላቸው ብዙ ወንድሞችና እህቶች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የአገልግሎት ምድብ ለውጥ አጋጥሟቸዋል። ለምሳሌ ያህል፣ የአውራጃ የበላይ ተመልካቾችና ሚስቶቻቸው በሌላ የሙሉ ጊዜ አገልግሎት ዘርፍ እንዲካፈሉ በ2014 ተጠይቀዋል። ከዚያው ዓመት ጀምሮ የወረዳ የበላይ ተመልካቾች 70 ዓመት ሲሞላቸው በዚህ ኃላፊነት ማገልገላቸውን እንዲያቆሙ ተወስኗል። በተጨማሪም 80 ዓመትና ከዚያ በላይ የሆናቸው ወንድሞች በጉባኤ ውስጥ የሽማግሌዎች አካል አስተባባሪ ሆነው ማገልገላቸውን እንዲያቆሙ ተደርጓል። ከዚህም በላይ ባለፉት ዓመታት በርካታ የቤቴል ቤተሰብ አባላት በመስኩ ላይ እንዲያገለግሉ ተመድበዋል። ሌሎች ደግሞ በጤና እክል፣ በቤተሰብ ኃላፊነት ወይም በሌሎች የግል ጉዳዮች የተነሳ የልዩ ሙሉ ጊዜ አገልግሎታቸውን ለማቆም ተገደዋል።

16. በርካታ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን፣ ያጋጠሟቸውን ለውጦች በትሕትና እንደተቀበሉ ያሳዩት እንዴት ነው?

16 ለእነዚህ ወንድሞችና እህቶች እንዲህ ያሉ ለውጦችን ማድረግ ቀላል አልነበረም። ብዙዎቹ በዚያ የአገልግሎት ዘርፍ ለበርካታ ዓመታት ሲያገለግሉ ስለቆዩ ለአገልግሎት ምድባቸው ከፍተኛ ፍቅር እንደነበራቸው ግልጽ ነው። አንዳንዶች ከተሰማቸው ሐዘን ለማገገምና ከአዲሱ ሁኔታቸው ጋር ለመላመድ ጊዜ ወስዶባቸዋል። ሆኖም ቀስ በቀስ፣ ያጋጠማቸውን ከባድ ሁኔታ መወጣት ችለዋል። በዚህ ረገድ የረዳቸው ምንድን ነው? ከሁሉ በላይ፣ ለይሖዋ ያላቸው ፍቅር ነው። ራሳቸውን የወሰኑት ለአንድ ዓይነት ሥራ፣ መብት ወይም ኃላፊነት ሳይሆን ለአምላክ እንደሆነ ተገንዝበዋል። (ቆላ. 3:23) በየትኛውም ሁኔታ ሥር ይሖዋን በትሕትና ማገልገላቸው ያስደስታቸዋል። ይሖዋ ‘ስለ እነሱ እንደሚያስብ’ ስለሚያውቁ ‘የሚያስጨንቃቸውን ነገር ሁሉ በእሱ ላይ ይጥላሉ።’—1 ጴጥ. 5:6, 7

17. የአምላክ ቃል ትሕትናን እንድናዳብር ለሚሰጠን ማበረታቻ አመስጋኞች የሆንነው ለምንድን ነው?

17 የአምላክ ቃል ትሕትናን እንድናዳብር ለሚሰጠን ማበረታቻ ምንኛ አመስጋኞች ነን! ምክንያቱም ይህን ግሩም ባሕርይ ማዳበራችን ራሳችንንም ሆነ ሌሎችን ይጠቅማል። ትሕትና፣ በሕይወት ውስጥ የሚያጋጥሙንን ተፈታታኝ ሁኔታዎች በተሻለ መንገድ ለመወጣት ያስችለናል። ከሁሉ በላይ ደግሞ በሰማይ ወዳለው አባታችን ይበልጥ እንድንቀርብ ይረዳናል። በእርግጥም “ከፍ ከፍ ያለውና እጅግ የከበረው” ይሖዋ ትሑት አገልጋዮቹን እንደሚወዳቸውና ትልቅ ቦታ እንደሚሰጣቸው ማወቃችን ልባችን በደስታ እንዲሞላ ያደርጋል!—ኢሳ. 57:15

መዝሙር 45 በልቤ የማሰላስለው ነገር

^ አን.5 ልናዳብራቸው ከሚገቡን በጣም አስፈላጊ ባሕርያት መካከል አንዱ ትሕትና ነው። ለመሆኑ ትሕትና ምንድን ነው? ይህን ባሕርይ ማዳበር ያለብን ለምንድን ነው? ሁኔታችን ሲለወጥ ትሕትና ማሳየት ተፈታታኝ ሊሆንብን የሚችለው ለምንድን ነው? ይህ ርዕስ ለእነዚህ ወሳኝ ጥያቄዎች መልስ ይሰጣል።

^ አን.7 በጥቅምት 1, 1984 መጠበቂያ ግንብ (እንግሊዝኛ) ላይ የወጣውን “ይሖዋ በእጅጉ ክሶኛል” የሚለውን ርዕስ ተመልከት።

^ አን.53 የሥዕሉ መግለጫ፦ ትሑት የሆነው ሐዋርያው ጳውሎስ አንድ ወንድም ቤት ተጋብዞ ከልጆች እንዲሁም ከተለያዩ ወንድሞችና እህቶች ጋር ሲጫወት።

^ አን.57 የሥዕሉ መግለጫ፦ አንድ ወንድም በዕድሜ ከእሱ ከሚያንስ ወንድም መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምክር ሲቀበል።

^ አን.59 የሥዕሉ መግለጫ፦ በዕድሜ የገፋው ወንድም በዕድሜ ከእሱ የሚያንሰው ወንድም በጉባኤ ውስጥ ኃላፊነት ስለተሰጠው ቅናት አላደረበትም።