በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የጥናት ርዕስ 38

የሰላሙን ጊዜ በጥበብ ተጠቀሙበት

የሰላሙን ጊዜ በጥበብ ተጠቀሙበት

“ምድሪቱ እረፍት አግኝታ [ነበር]፤ ይሖዋ እረፍት ሰጥቶት ስለነበር በእነዚያ ዓመታት በእሱ ላይ ጦርነት የከፈተ አልነበረም።”—2 ዜና 14:6

መዝሙር 60 ስብከታችን ሰው ያድናል

ማስተዋወቂያ *

1. ይሖዋን ማገልገል ተፈታታኝ የሚሆነው መቼ ሊሆን ይችላል?

ይሖዋን ማገልገል ይበልጥ ተፈታታኝ የሚሆነው መቼ ይመስልሃል? አስቸጋሪ ሁኔታዎች ባሉበት ወቅት ወይስ በአንጻራዊ ሁኔታ ሰላም በሰፈነበት ጊዜ? ተፈታታኝ ሁኔታዎች ሲያጋጥሙን በይሖዋ መታመን አይከብደንም። ይሁንና ነገሮች ሰላማዊ በሆኑበት ወቅት ምን እናደርጋለን? ትኩረታችን ተከፋፍሎ ለይሖዋ የምናቀርበውን አገልግሎት ችላ እንል ይሆን? ይሖዋ እስራኤላውያንን እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ሊያጋጥማቸው እንደሚችል አስጠንቅቋቸዋል።—ዘዳ. 6:10-12

ንጉሥ አሳ የሐሰት አምልኮን ለማስወገድ ቆራጥ እርምጃ ወስዷል (አንቀጽ 2⁠ን ተመልከት) *

2. ንጉሥ አሳ ምን ምሳሌ ትቷል?

2 ንጉሥ አሳ በይሖዋ ሙሉ በሙሉ ታምኖ የጥበብ እርምጃ በመውሰድ ረገድ ግሩም ምሳሌ ይሆነናል። አሳ በአስቸጋሪ ጊዜም ሆነ በሰላሙ ጊዜ ይሖዋን አገልግሏል። አሳ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ “ሙሉ በሙሉ ለይሖዋ ያደረ” ሰው ነበር። (1 ነገ. 15:14 ግርጌ) አሳ ለይሖዋ ያደረ መሆኑን ያሳየበት አንዱ መንገድ የሐሰት አምልኮን ከይሁዳ ማስወገዱ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ “የባዕድ አማልክቱን መሠዊያዎችና ከፍ ያሉትን የማምለኪያ ቦታዎች አስወገደ፤ የማምለኪያ ዓምዶቹንም ሰባበረ፤ እንዲሁም የማምለኪያ ግንዶቹን ቆራረጠ” ይላል። (2 ዜና 14:3, 5) ሌላው ቀርቶ አያቱን ማአካን ከእመቤትነቷ ሽሯታል። ለምን? የጣዖት አምልኮ ታስፋፋ ስለነበር ነው።—1 ነገ. 15:11-13

3. በዚህ ርዕስ ውስጥ ምን እንመረምራለን?

3 አሳ የሐሰት አምልኮን በማስወገድ ብቻ አልተወሰነም። የይሁዳ ሕዝብ ወደ ይሖዋ እንዲመለስ በመርዳት ንጹሑን አምልኮ አስፋፍቷል። ይሖዋም አሳን እና እስራኤላውያንን ሰላም * በመስጠት ባርኳቸዋል። በአሳ የግዛት ዘመን ለአሥር ዓመት ያህል “ምድሪቱ እረፍት አግኝታ [ነበር]።” (2 ዜና 14:1, 4, 6) አሳ ይህን የሰላም ጊዜ እንዴት እንደተጠቀመበት በዚህ ርዕስ ውስጥ እንመረምራለን። ከዚያም ልክ እንደ አሳ የሰላሙን ጊዜ በጥበብ የተጠቀሙበትን የመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኖችን ምሳሌ እንመለከታለን። በመጨረሻም፣ ‘የአምልኮ ነፃነት ባለበት አገር ውስጥ የምትኖር ከሆነ ይህን የሰላም ጊዜ በጥበብ መጠቀም የምትችለው እንዴት ነው?’ የሚለውን ጥያቄ መልስ እናያለን።

አሳ የሰላሙን ጊዜ የተጠቀመበት እንዴት ነው?

4. በ2 ዜና መዋዕል 14:2, 6, 7 መሠረት አሳ የሰላሙን ጊዜ የተጠቀመበት እንዴት ነው?

4 ሁለተኛ ዜና መዋዕል 14:2, 6, 7ን አንብብ። አሳ ‘በዙሪያቸው ካሉት ጠላቶቻቸው ሁሉ እረፍት የሰጣቸው’ ይሖዋ መሆኑን ለሕዝቡ ነግሯቸዋል። አሳ ሰላም የሰፈነበት ይህ ጊዜ ዘና የሚሉበት ወቅት እንዳልሆነ ተሰምቶታል። እንዲያውም ከተሞች፣ ቅጥርና ማማዎች እንዲሁም በሮች መሥራት ጀመረ። የይሁዳን ሕዝብ “ምድሪቱ አሁንም በእጃችን ናት” አላቸው። አሳ ምን ማለቱ ነበር? ሕዝቡ የጠላቶቻቸው ተቃውሞ ስለሌለባቸው አምላክ በሰጣቸው ምድር ላይ በነፃነት መንቀሳቀስና መገንባት እንደሚችሉ መግለጹ ነበር። ይህን የሰላም ጊዜ በጥበብ እንዲጠቀሙበት ሕዝቡን አሳስቧቸዋል።

5. አሳ ወታደራዊ ኃይሉን ያጠናከረው ለምንድን ነው?

5 አሳ የሰላሙን ጊዜ ወታደራዊ ኃይሉን ለማጠናከርም ተጠቅሞበታል። (2 ዜና 14:8) ይህ በይሖዋ እንዳልታመነ የሚያሳይ ነው? አይደለም። ከዚህ ይልቅ አሳ ንጉሥ እንደመሆኑ መጠን ሕዝቡን ወደፊት ሊመጣ ለሚችለው ችግር የማዘጋጀት ኃላፊነት እንዳለበት መገንዘቡን የሚጠቁም ነው። አሳ የይሁዳ ሕዝብ ያገኘው የሰላም ጊዜ ለዘለቄታው እንደማይቀጥል ተሰምቶት ነበር፤ ደግሞም ትክክል ነበር።

የመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኖች የሰላሙን ጊዜ የተጠቀሙበት እንዴት ነው?

6. የመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኖች የሰላሙን ጊዜ የተጠቀሙበት እንዴት ነው?

6 በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩት ክርስቲያኖች ብዙ ጊዜ ስደት ይደርስባቸው የነበረ ቢሆንም ሰላም ያገኙባቸው ወቅቶችም ነበሩ። ታዲያ ደቀ መዛሙርቱ እነዚህን ወቅቶች እንዴት ተጠቀሙባቸው? እነዚህ ታማኝ ወንዶችና ሴቶች ምሥራቹን ያለማሰለስ ሰብከዋል። በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ላይ የሚገኘው ዘገባ “ይሖዋን በመፍራት” ይኖሩ እንደነበር ይገልጻል። ምሥራቹን መስበካቸውን በመቀጠላቸው ‘በቁጥር እየበዙ ሄዱ።’ እነዚህ ክርስቲያኖች በሰላሙ ጊዜ በቅንዓት ያከናወኑትን የስብከት ሥራ ይሖዋ እንደባረከላቸው አያጠራጥርም።—ሥራ 9:26-31

7-8. ጳውሎስና ሌሎች ክርስቲያኖች ያገኙትን አጋጣሚ ምን ለማድረግ ተጠቅመውበታል? አብራራ።

7 የመጀመሪያው መቶ ዘመን ደቀ መዛሙርት ምሥራቹን ለመስበክ የሚያስችላቸውን አጋጣሚ ሁሉ ተጠቅመውበታል። አንድ ምሳሌ እንውሰድ፤ ሐዋርያው ጳውሎስ በኤፌሶን ሳለ ትልቅ የሥራ በር እንደተከፈተለት ተገንዝቦ ነበር፤ በመሆኑም ይህን አጋጣሚ በዚያች ከተማ ለመስበክና ደቀ መዛሙርት ለማፍራት ተጠቅሞበታል።—1 ቆሮ. 16:8, 9

8 በ49 ዓ.ም. የግርዘት ጉዳይ እልባት ከተሰጠው በኋላም ጳውሎስና አንዳንድ ክርስቲያኖች ሌላ አጋጣሚ አግኝተው ነበር። (ሥራ 15:23-29) እነዚህ ክርስቲያኖች ውሳኔውን ለጉባኤዎቹ ካሳወቁ በኋላ “ምሥራቹን ይኸውም የይሖዋን ቃል” ለማወጅ በትጋት ሠርተዋል። (ሥራ 15:30-35) ውጤቱ ምን ሆነ? መጽሐፍ ቅዱስ “ጉባኤዎቹም በእምነት እየጠነከሩና ከዕለት ወደ ዕለት በቁጥር እየጨመሩ ሄዱ” ይላል።—ሥራ 16:4, 5

በዘመናችን የሰላሙን ጊዜ መጠቀም

9. በዛሬው ጊዜ በብዙ አገሮች ውስጥ ያለው ሁኔታ ምን ይመስላል? ራሳችንን ምን ብለን መጠየቅ እንችላለን?

9 በዛሬው ጊዜ በብዙ አገሮች ውስጥ ያለገደብ መስበክ እንችላለን። አንተስ የምትኖረው የአምልኮ ነፃነት ባለበት አገር ውስጥ ነው? ከሆነ ‘ይህን ነፃነት እንዴት እየተጠቀምኩበት ነው?’ ብለህ ራስህን ጠይቅ። ብዙ ሥራ ባለበት በዚህ የመጨረሻ ዘመን የይሖዋ ድርጅት፣ ታይቶ የማይታወቅ ታላቅ የስብከትና የማስተማር ዘመቻ እያካሄደ ነው። (ማር. 13:10) የይሖዋ ሕዝቦች ብዙ አጋጣሚዎች ተከፍተውላቸዋል።

ብዙዎች ወደ ሌሎች አገራት ሄደው በማገልገል ወይም ሌላ ቋንቋ ለሚናገሩ ሰዎች በመመሥከር የተትረፈረፈ በረከት አግኝተዋል (ከአንቀጽ 10-12⁠ን ተመልከት) *

10. ሁለተኛ ጢሞቴዎስ 4:2 ምን እንድናደርግ ያበረታታናል?

10 የሰላሙን ጊዜ በጥበብ ልትጠቀምበት የምትችለው እንዴት ነው? (2 ጢሞቴዎስ 4:2ን አንብብ።) ለምን ያለህበትን ሁኔታ አትገመግምም? አንተ ወይም ከቤተሰብህ አባላት አንዱ በስብከቱ ሥራ የምታደርጉትን ተሳትፎ መጨመር ምናልባትም አቅኚ ሆናችሁ ማገልገል ትችሉ ይሆን? አሁን ያለንበት ወቅት ሀብትና ቁሳዊ ንብረት የምናካብትበት አይደለም፤ እነዚህ ነገሮች ታላቁን መከራ አያልፉም።—ምሳሌ 11:4፤ ማቴ. 6:31-33፤ 1 ዮሐ. 2:15-17

11. አንዳንዶች ምሥራቹን በተቻለ መጠን ለብዙዎች ለማካፈል ሲሉ ምን አድርገዋል?

11 በርካታ አስፋፊዎች ለስብከቱና ለማስተማሩ ሥራ እንዲረዳቸው ሲሉ አዲስ ቋንቋ ተምረዋል። የአምላክ ድርጅትም በየጊዜው በተጨማሪ ቋንቋዎች መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጽሑፎችን በማዘጋጀት ለእነዚህ አስፋፊዎች እገዛ እያደረገላቸው ነው። ለምሳሌ ያህል፣ በ2010 ጽሑፎቻችን የሚገኙት በ500 ገደማ ቋንቋዎች ነበር። በዛሬው ጊዜ ግን ከ1,000 በሚበልጡ ቋንቋዎች ጽሑፎቻችን ይዘጋጃሉ!

12. ሰዎች በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው የመንግሥቱን መልእክት መስማታቸው ምን ጥቅም ያስገኝላቸዋል? ምሳሌ ስጥ።

12 ሰዎች በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘውን እውነት በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው መስማታቸው ምን ስሜት ይፈጥርባቸዋል? በሜምፊስ፣ ቴነሲ፣ ዩናይትድ ስቴትስ በተደረገ የክልል ስብሰባ ላይ ተገኝታ የነበረችን የአንዲት እህት ተሞክሮ እንመልከት። ስብሰባውን በኪንያርዋንዳ መከታተል የቻለች ሲሆን ይህ ቋንቋ በዋነኝነት የሚነገረው በሩዋንዳ፣ በኮንጎ (ኪንሻሳ) እና በኡጋንዳ ነው። ኪንያርዋንዳ ተናጋሪ የሆነችው ይህች እህት ከስብሰባው በኋላ እንዲህ ብላለች፦ “ከ17 ዓመት በፊት ወደ ዩናይትድ ስቴትስ ከመጣሁ ወዲህ፣ በስብሰባ ላይ የሚቀርበውን መንፈሳዊ ትምህርት ለመጀመሪያ ጊዜ ሙሉ በሙሉ መረዳት የቻልኩት አሁን ነው።” ይህች እህት ትምህርቱን በቋንቋዋ መስማቷ ልቧን እንደነካው ግልጽ ነው። አንተስ ሁኔታህ የሚፈቅድልህ ከሆነ በክልልህ ውስጥ የሚገኙ አንዳንድ ሰዎችን ለመርዳት ስትል ሌላ ቋንቋ መማር ትችል ይሆን? በጉባኤህ ክልል ውስጥ የሚገኙ አንዳንድ ሰዎች ይበልጥ የሚቀልላቸው ሌላ ቋንቋ ይኖር ይሆን? ለእነዚህ ሰዎች ምሥራቹን በቋንቋቸው መናገርህ ልባቸውን ለመንካት ያስችልህ ይሆን? በዚህ ረገድ የምታደርገው ጥረት ይክስሃል።

13. በሩሲያ ያሉ ወንድሞቻችን የሰላሙን ጊዜ የተጠቀሙበት እንዴት ነው?

13 በነፃነት የመስበክ አጋጣሚ ያላቸው ሁሉም ወንድሞቻችን አይደሉም። አንዳንድ ጊዜ መንግሥታት የጣሉት እገዳ አገልግሎታችንን በጣም ይገድበው ይሆናል። በሩሲያ ያሉ ወንድሞቻችንን እንደ ምሳሌ እንውሰድ። ለበርካታ አሥርተ ዓመታት ስደት ሲደርስባቸው ከቆየ በኋላ መጋቢት 1991 ሥራቸው ሕጋዊ እውቅና አገኘ። በወቅቱ ሩሲያ ውስጥ 16,000 ገደማ የመንግሥቱ አዋጅ ነጋሪዎች ነበሩ። ከሃያ ዓመት በኋላ ቁጥራቸው ጨምሮ ከ160,000 በላይ ሆነዋል! ወንድሞቻችን በነፃነት ለመስበክ የሚያስችላቸውን አጋጣሚ በጥበብ እንደተጠቀሙበት በግልጽ ማየት እንችላለን። ሆኖም ይህ የሰላም ጊዜ አልዘለቀም። ሁኔታቸው መቀየሩ ግን ንጹሑን አምልኮ ለማስፋፋት ያላቸውን ቅንዓት አላቀዘቀዘውም። ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ በመጠቀም ይሖዋን ማገልገላቸውን ቀጥለዋል።

የሰላሙ ጊዜ ማብቂያ አለው

ንጉሥ አሳ ይሖዋን አጥብቆ ከለመነ በኋላ የይሁዳ ሕዝብ፣ ታላቅ የሆነውን የጠላት ሠራዊት ድል እንዲያደርጉ ይሖዋ ረድቷቸዋል (ከአንቀጽ 14-15⁠ን ተመልከት)

14-15. ይሖዋ አሳን ለመርዳት ኃይሉን ያሳየው እንዴት ነው?

14 በአሳ ዘመን የነበረው የሰላም ጊዜ ውሎ አድሮ አበቃ። አንድ ሚሊዮን ወታደሮችን ያቀፈ ታላቅ ሠራዊት ከኢትዮጵያ መጣባቸው። የሠራዊቱ አዛዥ የሆነው ዛራ ይሁዳን ድል እንደሚያደርግ ተማምኖ ነበር። ንጉሥ አሳ የተማመነው ግን በሠራዊቱ ብዛት ሳይሆን በአምላኩ በይሖዋ ነበር። አሳ “ይሖዋ አምላካችን ሆይ፣ እርዳን፤ በአንተ ታምነናልና፤ በስምህ ይህን ታላቅ ሠራዊት ለመግጠም ወጥተናል” በማለት ጸለየ።—2 ዜና 14:11

15 የኢትዮጵያውያን ወታደሮች ብዛት ከይሁዳ ሠራዊት በእጥፍ ያህል የሚበልጥ ቢሆንም ይሖዋ ሕዝቡን ለማዳን የሚያስችል ኃይልና ችሎታ እንዳለው አሳ ተናግሯል። ይሖዋም ቢሆን አላሳፈረውም፤ የኢትዮጵያውያን ሠራዊት ሽንፈት እንዲከናነብ አደረገ።—2 ዜና 14:8-13

16. አሁን ያለን የሰላም ጊዜ እንደሚያበቃ እንዴት እናውቃለን?

16 ወደፊት በግለሰብ ደረጃ የሚገጥመንን እያንዳንዱን ነገር አናውቅም፤ የምናውቀው ነገር ቢኖር ዛሬ የአምላክ ሕዝቦች ያገኙት ሰላም ጊዜያዊ እንደሆነ ነው። ኢየሱስ ስለ መጨረሻዎቹ ቀናት ለደቀ መዛሙርቱ ሲናገር “በሕዝቦች ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ” ማለቱን አስታውስ። (ማቴ. 24:9) ሐዋርያው ጳውሎስም በተመሳሳይ “የክርስቶስ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በመሆን ለአምላክ ያደሩ ሆነው መኖር የሚፈልጉ ሁሉ ስደት ይደርስባቸዋል” ብሏል። (2 ጢሞ. 3:12) ሰይጣን ‘በታላቅ ቁጣ ተሞልቷል’፤ ስለዚህ የእሱን ቁጣ በሆነ መንገድ ማምለጥ እንደምንችል ማሰብ ሞኝነት ነው።—ራእይ 12:12

17. እምነታችንን የሚፈትኑ ምን ሁኔታዎች ሊያጋጥሙን ይችላሉ?

17 በቅርቡ ሁላችንም ንጹሕ አቋማችንን የሚፈትን ነገር እንደሚገጥመን የታወቀ ነው። ብዙም ሳይቆይ፣ “ከዓለም መጀመሪያ አንስቶ እስካሁን ድረስ ሆኖ የማያውቅ ዳግመኛም የማይሆን ታላቅ መከራ” ይመጣል። (ማቴ. 24:21) በዚያ ወቅት የቤተሰባችን አባላት ይነሱብን እንዲሁም ሥራችን ይታገድ ይሆናል። (ማቴ. 10:35, 36) ታዲያ እያንዳንዳችን እንደ አሳ ይሖዋ እንደሚረዳንና እንደሚጠብቀን እንተማመናለን?

18. የሰላሙ ጊዜ ለሚያበቃበት ወቅት ራሳችንን ማዘጋጀት ስለምንችልበት መንገድ ዕብራውያን 10:38, 39 ምን ይጠቁመናል?

18 ይሖዋ መንፈሳዊነታችንን እንድናጠናክር በመርዳት ወደፊት ለሚመጣው ነገር ሲያዘጋጀን ቆይቷል። ‘ታማኝና ልባም ባሪያን’ በመጠቀም በአምልኳችን ለመጽናት የሚያስፈልገንን ገንቢ መንፈሳዊ ምግብ “በተገቢው ጊዜ” እያቀረበልን ነው። (ማቴ. 24:45) ሆኖም እኛም በይሖዋ ላይ የማይናወጥ እምነት ለማዳበር ጥረት በማድረግ የራሳችንን ድርሻ መወጣት አለብን።ዕብራውያን 10:38, 39ን አንብብ።

19-20. በ1 ዜና መዋዕል 28:9 ላይ ካለው ሐሳብ አንጻር ራሳችንን የትኞቹን ጥያቄዎች መጠየቅ ይኖርብናል? እንዲህ ማድረግ ያለብንስ ለምንድን ነው?

19 እኛም እንደ ንጉሥ አሳ ‘ይሖዋን መፈለግ’ ይኖርብናል። (2 ዜና 14:4፤ 15:1, 2) ይሖዋን ለመፈለግ የሚያስችለን የመጀመሪያው እርምጃ ስለ ይሖዋ መማርና መጠመቅ ነው። ለይሖዋ ያለንን ፍቅር ለማሳደግ የሚያስችሉ አጋጣሚዎችን ሁሉ ለመጠቀም ጥረት እናደርጋለን። በዚህ ረገድ ምን ያህል እየጣርን እንደሆነ ለማወቅ ‘በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ አዘውትሬ እገኛለሁ?’ ብለን ራሳችንን መጠየቅ እንችላለን። የይሖዋ ድርጅት ባዘጋጃቸው ስብሰባዎች ላይ ስንገኝ እረፍት የሚሰጥ መንፈሳዊ ትምህርት እንዲሁም የወንድሞቻችንን እና የእህቶቻችንን ማበረታቻ እናገኛለን። (ማቴ. 11:28) በተጨማሪም ‘መጽሐፍ ቅዱስን አዘውትሬ የማጥናት ልማድ አለኝ?’ ብለን ራሳችንን መጠየቃችን ጠቃሚ ነው። የምትኖረው ከቤተሰብህ ጋር ከሆነ በየሳምንቱ የቤተሰብ አምልኮ ለማድረግ ጊዜ መድባችኋል? የምትኖረው ብቻህን ከሆነ ደግሞ ቤተሰቦች በየሳምንቱ እንደሚያደርጉት የምታጠናበት ጊዜ መድበሃል? በስብከቱና ደቀ መዛሙርት በማድረጉ ሥራ አቅምህ በፈቀደው መጠን የተሟላ ተሳትፎ እያደረግክ ነው?

20 ራሳችንን እንዲህ ብለን መጠየቅ ያለብን ለምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ፣ ይሖዋ ሐሳባችንን እና በልባችን ውስጥ ያለውን ነገር እንደሚመረምር ይገልጻል፤ እኛም እንዲህ ማድረግ ይኖርብናል። (1 ዜና መዋዕል 28:9ን አንብብ።) ግባችንን፣ አስተሳሰባችንን ወይም አመለካከታችንን ማስተካከል እንዳለብን የሚጠቁም ነገር ካስተዋልን እነዚህን ለውጦች ለማድረግ እንዲረዳን ይሖዋን እንለምነው። ወደፊት ለሚመጡት ፈተናዎች ራሳችንን የምናዘጋጅበት ጊዜ አሁን ነው። እንግዲያው የሰላሙን ጊዜ በጥበብ እንዳትጠቀሙበት ምንም ነገር አያግዳችሁ!

መዝሙር 62 አዲሱ መዝሙር

^ አን.5 የምትኖረው ይሖዋን በነፃነት ማምለክ በሚቻልበት አገር ውስጥ ነው? ከሆነ ይህን የሰላም ጊዜ እንዴት እየተጠቀምክበት ነው? ይህ ርዕስ የይሁዳ ንጉሥ የነበረውን አሳን እንዲሁም በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩ ክርስቲያኖችን ምሳሌ መከተል የምትችለው እንዴት እንደሆነ ያብራራል። እነዚህ ሰዎች፣ የሰላሙን ጊዜ በጥበብ ተጠቅመውበታል።

^ አን.3 ተጨማሪ ማብራሪያ፦ “ሰላም” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ጦርነት አለመኖሩን ብቻ አይደለም። የዕብራይስጡ ቃል ጤና መሆንን፣ ከጉዳት መጠበቅንና መልካም ነገር ማግኘትንም ያመለክታል።

^ አን.57 የሥዕሉ መግለጫ፦ ንጉሥ አሳ፣ የሐሰት አምልኮን ታስፋፋ ስለነበር አያቱን ከቦታዋ ሽሯታል። የአሳ ታማኝ ደጋፊዎችም የእሱን ምሳሌ በመከተል ጣዖታትን አስወግደዋል።

^ አን.59 የሥዕሉ መግለጫ፦ ቀናተኛ ክርስቲያን የሆኑ አንድ ባልና ሚስት፣ አስፋፊዎች ይበልጥ በሚያስፈልጉበት ቦታ ለማገልገል ሲሉ አኗኗራቸውን ቀላል አድርገዋል።