በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

“እገሌ” የተባለው ሰው ሩትን ማግባቱ የገዛ ርስቱን ‘አደጋ ላይ እንደሚጥልበት’ የተናገረው ለምንድን ነው? (ሩት 4:1, 6)

በመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን አንድ ሰው ልጅ ሳይወልድ ከሞተ ከዚያ ጋር በተያያዘ እንደሚከተሉት ያሉ ጥያቄዎች ይነሳሉ፦ ርስቱ ምን ይሆናል? የቤተሰቡ ስም ለዘላለም ይረሳል? የሙሴ ሕግ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ይሰጣል።

አንድ ሰው ቢሞት ወይም ድሃ በመሆኑ ምክንያት መሬቱን ቢሸጥ ርስቱ ምን ይሆናል? የዚህ ሰው ወንድም ወይም የቅርብ ዘመድ ርስቱን ሊዋጀው አሊያም ሊቤዠው ይችላል። እንዲህ መደረጉ ርስቱ የቤተሰቡ ንብረት ሆኖ እንዲቀጥል ያስችላል።—ዘሌ. 25:23-28፤ ዘኁ. 27:8-11

የቤተሰቡ ስም ሳይጠፋ ተጠብቆ እንዲቆይ የሚደረገው እንዴት ነው? የሟቹ ወንድም ወይም የቅርብ ዘመድ የሟቹን ሚስት በማግባት የዋርሳነት ግዴታውን ይወጣል፤ ከሩት ጋር በተያያዘም የሆነው ነገር ይህ ነው። የሟቹን ሚስት ያገባው ሰው ከእሷ ልጅ በመውለድ የሟቹን ንብረት የሚወርስ ዘር ይተካል። ይህ ፍቅራዊ ዝግጅት ለሟች ሚስትም ጠቃሚ ነው።—ዘዳ. 25:5-7፤ ማቴ. 22:23-28

የናኦሚን ሁኔታ እንደ ምሳሌ እንመልከት። ኤሊሜሌክ የሚባል ሰው አግብታ ነበር። ባሏና ሁለት ልጆቻቸው ሲሞቱ ናኦሚ የሚያስተዳድራት ሰው አጥታ ብቻዋን ቀረች። (ሩት 1:1-5) ወደ ይሁዳ ከተመለሰች በኋላ ምራቷን ሩትን መሬታቸውን በመግዛት እንዲቤዣቸው ቦዔዝን እንድትጠይቀው ነገረቻት። ቦዔዝ የኤሊሜሌክ የቅርብ ዘመድ ነው። (ሩት 2:1, 19, 20፤ 3:1-4) ሆኖም ቦዔዝ ለሟቹ ይበልጥ ቅርብ የሆነ ሰው እንዳለ አስተዋለ፤ መጽሐፍ ቅዱስ ይህን ሰው “እገሌ” በማለት ይጠራዋል። በመቤዠት ረገድ ቅድሚያ የሚሰጠው ይህ ሰው ነው።—ሩት 3:9, 12, 13

“እገሌ” የተባለው ሰው መጀመሪያ ላይ ፈቃደኛ ነበር። (ሩት 4:1-4) ይህ ሰው መሬቱን መግዛቱ የተወሰነ ወጪ ሊያስወጣው ቢችልም ናኦሚ ዕድሜዋ ስለገፋ የኤሊሜሌክን ርስት የሚወርስ ልጅ መውለድ እንደማትችል ያውቅ ነበር። ስለዚህ የኤሊሜሌክ ርስት በእሱ ርስት ሥር ይጠቃለላል ማለት ነው፤ ይህ ደግሞ ለዚህ ሰው የሚያዋጣ ነው።

ሆኖም ይህ እገሌ የተባለው ሰው የመቤዠቱ ሂደት ሩትን ማግባትን እንደሚጨምርም ሲያውቅ ሐሳቡን ቀየረ። “የገዛ ርስቴን አደጋ ላይ ልጥል ስለምችል ልቤዠው አልችልም” አለ። (ሩት 4:5, 6) ሐሳቡን የቀየረው ለምንድን ነው?

እገሌ የተባለው ሰው ወይም ሌላ ሰው ሩትን ቢያገባና ወንድ ልጅ ብትወልድ ልጁ የኤሊሜሌክ ርስት ወራሽ ይሆናል። ታዲያ ይህ መሆኑ እገሌ የተባለውን ሰው ‘ርስት አደጋ ላይ ሊጥል’ የሚችለው እንዴት ነው? መጽሐፍ ቅዱስ ስለዚህ ጉዳይ ምንም የሚለው ነገር የለም፤ ግን ይህ ሊሆን የሚችልባቸውን መንገዶች መገመት ይቻላል።

  • አንደኛ፣ የኤሊሜሌክ ርስት የኋላ ኋላ የእሱ ስለማይሆን ያወጣው ገንዘብ ኪሳራ ሊሆንበት ይችላል። ምክንያቱም ርስቱን የሚወርሰው ሩት የምትወልደው ልጅ ነው።

  • ሁለተኛ፣ ናኦሚንና ሩትን የመመገብም ሆነ የማስተዳደር ኃላፊነት የሚወድቀው በእሱ ላይ ይሆናል።

  • ሦስተኛ፣ ሩት ተጨማሪ ልጆች ከወለደችለት ደግሞ እነዚህ ልጆች ከሌሎች ልጆቹ እኩል የእሱን ንብረት የመውረስ መብት ያገኛሉ።

  • አራተኛ፣ ይህ እገሌ የተባለው ሰው የራሱ ልጆች ከሌሉት ደግሞ የእሱንም ሆነ የኤሊሜሌክን ርስት የመውረስ መብት የሚኖረው ሩት የምትወልደው ልጅ ይሆናል። ይህ ማለት ደግሞ ርስቱን የሚያወርሰው በእሱ ሳይሆን በኤሊሜሌክ ስም ለሚጠራ ልጅ ይሆናል ማለት ነው። በመሆኑም እገሌ የተባለው ሰው ናኦሚን ለመርዳት ሲል ርስቱን አደጋ ላይ ለመጣል ፈቃደኛ አልሆነም። ከዚህ ይልቅ ከእሱ ቀጥሎ የመቤዠት መብት ላለው ለቦዔዝ ኃላፊነቱን ለማስተላለፍ መረጠ። ቦዔዝ “የሟቹን ስም ዳግም በርስቱ ለማስጠራት” ስለፈለገ ለመቤዠት ፈቃደኛ ሆነ።—ሩት 4:10

ከዚህ በግልጽ ማየት እንደሚቻለው እገሌ የተባለው ሰው በዋነኝነት ያሳሰበው ስሙንና ርስቱን የማስጠበቁ ጉዳይ ነው። የራስ ወዳድነት አስተሳሰብ አእምሮውን ተቆጣጥሮት ነበር። ምንም እንኳ ስሙን ለማስጠበቅ ከፍተኛ ጥረት ያደረገ ቢሆንም የዚህ ሰው ስም በዛሬው ጊዜ ማን እንደሆነ እንኳ አይታወቅም። ይህ ብቻ ሳይሆን ቦዔዝ ያገኘውን ልዩ መብት ማለትም ወደ መሲሑ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ በሚያደርሰው የዘር ሐረግ ዝርዝር ውስጥ የመካተት መብትም ሳያገኝ ቀርቷል። እገሌ የተባለው ሰው ራስ ወዳድ በመሆን ችግር ላይ የወደቀን ሰው ከመርዳት ወደኋላ ማለቱ ምን ያህል አሳዛኝ ውጤት አስከትሎበታል!—ማቴ. 1:5፤ ሉቃስ 3:23, 32