በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በይሖዋ ላይ እምነት ማሳደር የእሱን ሞገስ ያስገኛል

በይሖዋ ላይ እምነት ማሳደር የእሱን ሞገስ ያስገኛል

‘አምላክ ቃል የገባቸውን ነገሮች በእምነትና በትዕግሥት የሚወርሱትን ምሰሉ።’—ዕብ. 6:12

መዝሙሮች፦ 86, 54

1, 2. ዮፍታሔና ሴት ልጁ ምን ከባድ ሁኔታ አጋጥሟቸዋል?

ወጣቷ የአባቷን መመለስ በጭንቀት ስትጠባበቅ ቆይታለች። አባቷ ድል ተቀዳጅቶ ከጦር ሜዳ በሰላም መመለሱን ስታይ በደስታ ልትቀበለው ወጣች። አባቷ ግን ከእሷ ጋር አብሮ በመደሰትና በመጨፈር ፋንታ ልብሱን ቀዶ “ወዮ፣ ልጄ! ልቤን ሰበርሽው” አላት። ከዚያም ሕይወቷን ለዘለቄታው የሚቀይር ብሎም እንደማንኛውም ሰው የመኖር ምኞቷንና ተስፋዋን የሚያከስም ነገር ተናገረ። እሷ ግን ምንም ሳታመነታ፣ አባቷ ለይሖዋ የገባውን ቃል እንዲፈጽም የሚያበረታታ ግሩም ምላሽ ሰጠችው። የተናገረችው ነገር ታላቅ እምነት እንዳላት ያሳያል። ይሖዋ የሚጠይቃት ማንኛውም ነገር፣ እሷን የሚጠቅም እንደሆነ እምነት ነበራት። (መሳ. 11:34-37) አባቷም የእሷን ምላሽ ሲሰማ ልቡ በኩራት ተሞላ፤ ምክንያቱም ውሳኔውን በፈቃደኝነት መደገፏ የይሖዋን ሞገስ እንደሚያስገኝ ያውቃል።

2 ዮፍታሔና ፈሪሃ አምላክ ያላት ልጁ፣ የይሖዋን ፈቃድ ማድረግ ከባድ በሚሆንበት ጊዜም እንኳ አምላክ ነገሮችን በሚያከናውንበት መንገድ ላይ እምነት እንዳላቸው አሳይተዋል። የይሖዋን ሞገስ ለማግኘት ሲባል ማንኛውንም መሥዋዕት መክፈል ፈጽሞ እንደማያስቆጭ እርግጠኞች ነበሩ።

3. ዮፍታሔና ልጁ የተዉት ምሳሌ በዛሬው ጊዜ የሚጠቅመን እንዴት ነው?

3 በይሖዋ ላይ እምነት እንዳለን ማሳየት ቀላል የማይሆንባቸው ጊዜያት እንዳሉ እናውቃለን። እንዲያውም ‘ለእምነት ብርቱ ተጋድሎ ማድረግ’ ያስፈልገናል። (ይሁዳ 3) በመሆኑም ዮፍታሔና ልጁ የተቋቋሟቸውን ተፈታታኝ ሁኔታዎች መመልከታችን እኛም በአምላክ ላይ እምነት ለማሳደር ይረዳናል። ዮፍታሔና ልጁ ምንጊዜም በይሖዋ እንደሚታመኑ ያሳዩት እንዴት ነው?

የዓለም ተጽዕኖ ቢኖርም በአምላክ ላይ እምነት ማሳደር

4, 5. (ሀ) እስራኤላውያን ወደ ተስፋይቱ ምድር ሲገቡ ይሖዋ ምን ትእዛዝ ሰጥቷቸው ነበር? (ለ) መዝሙር 106 እንደሚገልጸው እስራኤላውያን ታዛዥ ባለመሆናቸው ምን ደርሶባቸዋል?

4 ዮፍታሔና ልጁ፣ እስራኤላውያን በይሖዋ አለመታመናቸው ያስከተለውን መዘዝ በዕለት ተዕለት ሕይወታቸው ይመለከቱ ነበር። ወደ 300 ከሚጠጉ ዓመታት በፊት አባቶቻቸው፣ በተስፋይቱ ምድር የነበሩትን ጣዖት የሚያመልኩ ብሔራት በሙሉ ጠራርገው እንዲያጠፉ ታዘው ነበር። (ዘዳ. 7:1-4) ብሔሩ ይህን ትእዛዝ አለመፈጸሙ ብዙዎቹ እስራኤላውያን የከነአናውያንን መጥፎ አካሄድ እንዲከተሉ ምክንያት ሆኗል፤ ይህም የሐሰት አማልክትን እንዲያመልኩና የሥነ ምግባር አቋማቸው እንዲያሽቆለቁል አድርጓል።—መዝሙር 106:34-39ን አንብብ።

5 ይሖዋ ያዘዛቸውን ባለመፈጸማቸው ደግሞ የእሱን ሞገስ ያጡ ከመሆኑም ሌላ ይሖዋ ለእነሱ ጥበቃ ማድረጉን አቁሟል። (መሳ. 2:1-3, 11-15፤ መዝ. 106:40-43) በእነዚያ አስቸጋሪ ጊዜያት የነበሩ ፈሪሃ አምላክ ያላቸው ቤተሰቦች፣ ምንጊዜም ለይሖዋ ታማኝ ሆኖ መኖር በጣም ፈታኝ እንደሆነባቸው መገመት አያዳግትም! ያም ሆኖ እንደ ዮፍታሔና ልጁ እንዲሁም እንደ ሐና፣ ሕልቃና እና ሳሙኤል ያሉ ታማኝ ሰዎች የአምላክን ሞገስ ለማግኘት ቁርጥ ውሳኔ አድርገው እንደነበር መጽሐፍ ቅዱስ ያሳያል።—1 ሳሙ. 1:20-28፤ 2:26

6. በዛሬው ጊዜ ዓለም ምን ዓይነት ተጽዕኖ ያሳድርብናል? እኛስ ምን ማድረግ አለብን?

6 በዛሬው ጊዜ ያሉ አብዛኞቹ ሰዎች የሚያስቡትና የሚያደርጉት ነገር በጥንት ጊዜ ከነበሩት ከነአናውያን ጋር ይመሳሰላል፤ ለፆታ ምኞት ትልቅ ቦታ የሚሰጡ ከመሆኑም ሌላ ዓመፀኞች ናቸው፤ እንዲሁም ቁሳዊ ነገሮችን ያሳድዳሉ። ይሖዋ ለእስራኤላውያን እንዳደረገው ሁሉ ለእኛም እንዲህ ካለው የዓለም ተጽዕኖ እንድንርቅ ግልጽ ማስጠንቀቂያ ሰጥቶናል። ታዲያ እስራኤላውያን ከፈጸሙት ስህተት ትምህርት አግኝተናል? (1 ቆሮ. 10:6-11) ከነአናውያን የነበራቸው ዓይነት አስተሳሰብ በውስጣችን ፈጽሞ እንዳይኖር ከፍተኛ ጥረት ማድረግ አለብን። (ሮም 12:2) እንዲህ ያለ ጥረት በማድረግ ረገድ በይሖዋ ላይ እምነት እያሳየን ነው?

ቅር የሚያሰኝ ሁኔታ ቢያጋጥምም በአምላክ መታመን

7. (ሀ) በዮፍታሔ ላይ የገዛ ወገኖቹ ምን አድርገውበታል? (ለ) ዮፍታሔ በዚህ ጊዜ ምን አደረገ?

7 በዮፍታሔ ዘመን የነበሩት እስራኤላውያን ታዛዥ ባለመሆናቸው የፍልስጤማውያንና የአሞናውያን ባሮች ሆነው ነበር። (መሳ. 10:7, 8) ይሁንና ዮፍታሔ ፈታኝ ሁኔታ ያጋጠመው የእስራኤላውያን ጠላት ከሆኑት ብሔራት ብቻ ሳይሆን ከገዛ ወንድሞቹና ከእስራኤል መሪዎች ጭምር ነው። በቅንዓትና በጥላቻ የተሞሉት ወንድሞቹ የበኩር ልጅ በመሆኑ ሊያገኝ የሚገባውን መብት በመከልከል ከአባቱ ቤት አባረውታል። (መሳ. 11:1-3) ዮፍታሔ፣ የእነሱ መጥፎ ባሕርይ በአመለካከቱ ላይ ተጽዕኖ እንዲያሳድር አልፈቀደም። እንዲያውም የብሔሩ ሽማግሌዎች ለእርዳታ የሚያሰሙትን ጩኸት ሰምቶ እንዳልሰማ ከማለፍ ይልቅ ረድቷቸዋል። (መሳ. 11:4-11) ዮፍታሔ፣ መንፈሳዊ ሰው እንደሆነ የሚያሳይ እንዲህ ዓይነት እርምጃ እንዲወስድ ያነሳሳው ምን ሊሆን ይችላል?

8, 9. (ሀ) ዮፍታሔን የረዱት በሙሴ ሕግ ውስጥ የሚገኙት የትኞቹ መሠረታዊ ሥርዓቶች ሊሆኑ ይችላሉ? (ለ) ዮፍታሔ ትልቅ ቦታ የሰጠው ነገር ምንድን ነው?

8 ዮፍታሔ ኃያል ተዋጊ ብቻ አልነበረም፤ አምላክ ከሕዝቦቹ ጋር ስለነበረው ግንኙነት እውቀት ነበረው። ዮፍታሔ ስለ እስራኤላውያን ታሪክ በሚገባ ማወቁ፣ በይሖዋ ዓይን ትክክል ስለሆነውና ስህተት ስለሆነው ነገር ትክክለኛ ግንዛቤ እንዲኖረው አድርጓል። (መሳ. 11:12-27) በሙሴ ሕግ ውስጥ የሚገኙት አምላክ ያወጣቸው መሠረታዊ ሥርዓቶች በዮፍታሔ አስተሳሰብና ስሜት ላይ ተጽዕኖ አሳድረዋል። ይሖዋ ቂም መያዝን ይጠላል፤ ሕዝቦቹም እርስ በርስ እንዲዋደዱ ይፈልጋል፤ ዮፍታሔ ይህን ያውቅ ነበር። በተጨማሪም አንድ ሰው ‘የሚጠሉት’ ሰዎች እንኳ ችግር ላይ ሲወድቁ ዝም ብሎ ማለፉ ተገቢ አለመሆኑን ሕጉ እንደሚያስተምር ያውቃል።—ዘፀአት 23:5ን እና ዘሌዋውያን 19:17, 18ን አንብብ።

9 እንደ ዮሴፍ ያሉ የእምነት ምሳሌዎችም በዮፍታሔ አመለካከት ላይ ተጽዕኖ ሳያሳድሩ አልቀሩም፤ ዮሴፍ ወንድሞቹ ‘ቢጠሉትም’ ምሕረት አሳይቷቸዋል። (ዘፍ. 37:4፤ 45:4, 5) ዮፍታሔ እንዲህ ያሉ ሰዎች በተዉት ምሳሌ ላይ ማሰላሰሉ፣ ይሖዋን የሚያስደስት እርምጃ እንዲወስድ ረድቶታል። ወንድሞቹ ያደረጉት ነገር በጣም እንደጎዳው ግልጽ ነው፤ ይሁንና ይህ ሁኔታ ይሖዋንና ሕዝቦቹን ከማገልገል ወደኋላ እንዲል አላደረገውም። (መሳ. 11:9) ዮፍታሔ ከሌሎች ሰዎች ጋር ከተፈጠረው ግጭት ይልቅ ትልቅ ቦታ የሰጠው የይሖዋን ስም ለማስከበር ሲል ለሚያደርገው ውጊያ ነው። ምንጊዜም በይሖዋ ለመታመን ቁርጥ ውሳኔ አድርጎ ነበር፤ ይህ ደግሞ ለእሱም ሆነ ለሌሎች በረከት አምጥቷል።—ዕብ. 11:32, 33

10. አምላክ ያወጣቸው መሠረታዊ ሥርዓቶች፣ ክርስቲያኖች መሆናችንን የሚያሳይ እርምጃ እንድንወስድ በዛሬው ጊዜ የሚረዱን እንዴት ነው?

10 ዮፍታሔ ከተወው ምሳሌ ምን ትምህርት እናገኛለን? ምናልባት አንዳንድ ወንድሞች ቅር አሰኝተውን ወይም ተገቢ ያልሆነ ነገር አድርገውብን ይሆናል። በዚህ ጊዜ፣ በክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ላይ ከመገኘት ወይም ከጉባኤው ጋር ሙሉ በሙሉ ከመተባበርና ይሖዋን ከማገልገል ወደኋላ ማለት አይኖርብንም። እኛም እንደ ዮፍታሔ፣ እንዲህ ያሉ አስቸጋሪ ሁኔታዎችን ለማሸነፍና መልካም ነገር ማድረጋችንን ለመቀጠል የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች መከተል ይኖርብናል።—ሮም 12:20, 21፤ ቆላ. 3:13

በፈቃደኝነት የምናቀርበው መሥዋዕት እምነታችንን ያሳያል

11, 12. ዮፍታሔ ምን ስእለት ተሳለ? ስእለቱስ ምን ትርጉም አለው?

11 ዮፍታሔ እስራኤላውያንን ከአሞናውያን እጅ ነፃ ለማውጣት የአምላክ እርዳታ እንደሚያስፈልገው ያውቅ ነበር። በመሆኑም ይሖዋ ድል ካቀዳጀው፣ ከጦርነት ሲመለስ ሊቀበለው መጀመሪያ የሚወጣውን ሰው ለይሖዋ “የሚቃጠል መባ” አድርጎ እንደሚያቀርብ ቃል ገባ። (መሳ. 11:30, 31) ዮፍታሔ የገባው ቃል ምን ትርጉም አለው?

12 ሰውን መሥዋዕት አድርጎ ማቅረብ በይሖዋ ዘንድ አስጸያፊ ድርጊት ነው። በመሆኑም ዮፍታሔ ማንንም ሰው ቃል በቃል መሥዋዕት ለማድረግ እንዳላሰበ ግልጽ ነው። (ዘዳ. 18:9, 10) በሙሴ ሕግ መሠረት የሚቃጠል መባ ለይሖዋ ሙሉ በሙሉ የሚቀርብ መሥዋዕት ነው፤ ስለሆነም ዮፍታሔ፣ ግለሰቡን ሙሉ በሙሉ ለይሖዋ አገልግሎት እንደሚሰጥ መናገሩ መሆን አለበት። ዮፍታሔ የገባው ቃል፣ ግለሰቡ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ በማደሪያው ድንኳን ውስጥ እንዲያገለግል መስጠትን ያመለክታል። ይሖዋ የዮፍታሔን ስእለት የተቀበለው ሲሆን በምላሹም ታላቅ ድል እንዲቀዳጅ ይኸውም ጠላቶቹን ማሸነፍና መግዛት እንዲችል አደረገው። (መሳ. 11:32, 33) ይሁንና ለአምላክ “የሚቃጠል መባ” ተደርጎ የሚቀርበው ማን ይሆን?

13, 14. በመሳፍንት 11:35 ላይ የሚገኘው ዮፍታሔ የተናገረው ሐሳብ ስለ እምነቱ ምን ይጠቁማል?

13 በዚህ ርዕስ መግቢያ ላይ የተጠቀሰውን ሁኔታ ለማስታወስ ሞክር። ዮፍታሔ ከጦርነት ሲመለስ እሱን ለመቀበል የወጣችው የሚወዳት አንድያ ልጁ ነበረች! እንግዲህ ፈተናው እዚህ ላይ ነው። ዮፍታሔ፣ ሕይወቷን ሙሉ በማደሪያው ድንኳን እንድታገለግል ልጁን በመስጠት ቃሉን ይጠብቅ ይሆን?

14 ዮፍታሔ በዚህ ጊዜም ትክክለኛ ውሳኔ ለማድረግ የረዳው በመሠረታዊ ሥርዓቶች መመራቱ መሆን አለበት። በዘፀአት 23:19 ላይ የሚገኘውን የአምላክ ሕዝቦች ለይሖዋ ምርጣቸውን እንዲሰጡ የሚያበረታታውን መመሪያ አስታውሶ ይሆናል። በተጨማሪም ሕጉ፣ አንድ ሰው ስእለት ከተሳለ ስእለቱን የመፈጸም ግዴታ እንዳለበት ይናገራል። ሕጉ እንዲህ ይላል፦ “አንድ ሰው ለይሖዋ ስእለት ቢሳል . . . ቃሉን ማጠፍ የለበትም። አደርገዋለሁ ብሎ የማለውን ነገር ሁሉ መፈጸም አለበት።” (ዘኁ. 30:2) ዮፍታሔ፣ ስእለቱን መፈጸሙ በእሱም ሆነ በልጁ ሕይወት ላይ ምን እንደሚያስከትል ቢያውቅም እንደ ታማኟ ሐና ሁሉ እሱም ቃሉን እንዲፈጽም ይጠበቅበት ነበር፤ ሐና የኖረችው በእሱ ዘመን ሳይሆን አይቀርም። ዮፍታሔ ሌላ ልጅ ስላልነበረው የዘር ሐረጉ እንዲቀጥል የሚያደርግም ሆነ ርስቱን የሚወርስ ልጅ ማግኘት የሚችለው በእሷ በኩል ብቻ ነበር። (መሳ. 11:34) ያም ሆኖ መሳፍንት 11:35 እንደሚገልጸው ዮፍታሔ “አንዴ ለይሖዋ ቃል ገብቻለሁ፤ ልመልሰውም አልችልም” በማለት ተናገረ። ከፍተኛ መሥዋዕት ቢያስከፍለውም በይሖዋ ላይ እምነት እንዳለው ማሳየቱ የአምላክን ሞገስና በረከት አስገኝቶለታል። አንተ ብትሆን እንዲህ ታደርግ ነበር?

15. ብዙዎቻችን ምን ስእለት ተስለናል? እምነት እንዳለን ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

15 ሕይወታችንን ለይሖዋ ስንወስን ራሳችንን ምንም ሳንቆጥብ የእሱን ፈቃድ ለመፈጸም ተስለናል። ይህን ቃል መጠበቅ የራሳችንን ጥቅም መሥዋዕት ማድረግ እንደሚጠይቅብን እናውቃለን። ይሁንና የማንወደውን ነገር እንድናደርግ ስንጠየቅ፣ የፈቃደኝነት መንፈስ ያለን መሆን አለመሆኑ ጥያቄ ውስጥ ይገባል። የተጠየቅነውን በማድረግና መሥዋዕትነት በመክፈል ከለመድነው ብሎም ከሚመቸን በተለየ መንገድ አምላክን ስናገለግል እምነት እንዳለን እናሳያለን። የምንከፍለው መሥዋዕት የቱንም ያህል ከባድ ቢሆን፣ ከምናገኘው የላቀ በረከት ጋር ሲወዳደር እዚህ ግባ የሚባል አይሆንም። (ሚል. 3:10) ይሁንና ስለ ዮፍታሔ ልጅስ ምን ማለት ይቻላል?

የዮፍታሔና የልጁ ዓይነት እምነት ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው? (አንቀጽ 16, 17ን ተመልከት)

16. የዮፍታሔ ልጅ አባቷ ከገባው ቃል ጋር በተያያዘ ምን አደረገች? (በመግቢያው ላይ ያለውን ሥዕል ተመልከት።)

16 የዮፍታሔ ልጅ፣ አባቷ ከገባው ቃል ጋር ተስማምታ ለመኖር ፈቃደኛ መሆን ቀላል እንደማይሆንላት ግልጽ ነው። ዮፍታሔ የገባው ቃል፣ ሐና ከተሳለችው ስእለት የተለየ ነው፤ ሐና የተሳለችው ልጇ ሳሙኤል በማደሪያው ድንኳን ናዝራዊ ሆኖ እንዲያገለግል ለመስጠት ነበር። (1 ሳሙ. 1:11) ናዝራውያን ማግባትና ቤተሰብ መመሥረት ይችላሉ። የዮፍታሔ ልጅ ግን ሙሉ በሙሉ ‘እንደሚቃጠል መባ’ ስለምትሆን እነዚህን አስደሳች ነገሮች መሥዋዕት ማድረግ ነበረባት። (መሳ. 11:37-40) አባቷ፣ ታላቅ ድል የተቀዳጀ የእስራኤል አለቃና መሪ በመሆኑ በአገሩ ውስጥ ከሁሉ የተሻለውን ሰው ማግባት ትችል ነበር። አሁን ግን በማደሪያው ድንኳን አገልጋይ ልትሆን ነው። ይህች ወጣት ምን ምላሽ ሰጠች? “አባቴ ሆይ፣ ለይሖዋ ቃል ከገባህ፣ የገባኸውን ቃል በእኔ ላይ ፈጽምብኝ” በማለት የይሖዋን አገልግሎት ከምንም ነገር በላይ እንደምታስቀድም አሳይታለች። (መሳ. 11:36) ንጹሑን አምልኮ ለመደገፍ ስትል፣ ባል የማግባትና ልጅ የመወለድ ተፈጥሯዊ ፍላጎቷን መሥዋዕት አድርጋለች። እሷ ያሳየችውን የራስን ጥቅም መሥዋዕት የማድረግ መንፈስ መኮረጅ የምንችለው እንዴት ነው?

17. (ሀ) ዮፍታሔንና ልጁን በእምነታቸው መምሰል የምንችለው እንዴት ነው? (ለ) በዕብራውያን 6:10-12 ላይ የሚገኘው ሐሳብ የራስህን ጥቅም መሥዋዕት እንድታደርግ የሚያበረታታህ እንዴት ነው?

17 በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣት ክርስቲያን ወንዶችና ሴቶች፣ ይሖዋን በተሟላ መንገድ ለማገልገል ሲሉ ትዳር የመመሥረት አሊያም ልጆች የመውለድ አጋጣሚያቸውን ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን በፈቃደኝነት መሥዋዕት አድርገዋል። በጉልምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ ክርስቲያኖችም ቢሆኑ በቲኦክራሲያዊ የግንባታ ፕሮጀክቶች ላይ ወይም በመንግሥቱ ወንጌላውያን ትምህርት ቤት ለመካፈል አሊያም የመንግሥቱ ሰባኪዎች ይበልጥ ወደሚያስፈልጉበት ቦታ ሄደው ለማገልገል ሲሉ ከልጆቻቸውና ከልጅ ልጆቻቸው ጋር ሊያሳልፉ የሚችሉትን ጊዜ መሥዋዕት አድርገዋል። ሌሎች ደግሞ በመታሰቢያው በዓል ሰሞን በሚደረገው የአገልግሎት ዘመቻ ላይ ለመካፈል ሲሉ የግል ጉዳዮቻቸውን ለመተው ፈቃደኛ ሆነዋል። እንዲህ ያለው በሙሉ ልብ የሚቀርብ አገልግሎት ይሖዋን በጣም ያስደስተዋል፤ ይሖዋም ሥራቸውንና ለእሱ ያሳዩትን ፍቅር ፈጽሞ አይረሳም። (ዕብራውያን 6:10-12ን አንብብ።) አንተስ ይሖዋን ይበልጥ በተሟላ መንገድ ለማገልገል ስትል ተጨማሪ መሥዋዕት መክፈል ትችል ይሆን?

ምን ትምህርት እናገኛለን?

18, 19. ስለ ዮፍታሔና ልጁ ከሚናገረው የመጽሐፍ ቅዱስ ዘገባ ምን ትምህርት አግኝተናል? የእነሱን ምሳሌ መከተል የምንችለውስ እንዴት ነው?

18 ዮፍታሔ በሕይወቱ ውስጥ ብዙ ተፈታታኝ ሁኔታዎች ቢያጋጥሙትም ውሳኔ ሲያደርግ ይሖዋ እንዲመራው ፈቅዷል። በዙሪያው የነበሩት ሰዎች ተጽዕኖ እንዲያደርጉበት አልፈቀደም። ሌሎች በፈጸሙበት ነገር በጣም የተጎዳ ቢሆንም ይህ በአምላክ ላይ ያለውን እምነት አላዳከመበትም። ይሖዋ፣ ዮፍታሔንም ሆነ ልጁን ንጹሑን አምልኮ ለማራመድ ተጠቅሞባቸዋል፤ በመሆኑም በፈቃደኝነት ተነሳስተው የከፈሉት መሥዋዕት በረከት አስገኝቷል። ሌሎች ሰዎች መለኮታዊ መሥፈርቶችን ችላ ባሉበት ጊዜ ዮፍታሔና ልጁ የይሖዋን መመሪያ በጥብቅ ተከትለዋል።

19 መጽሐፍ ቅዱስ “አምላክ ቃል የገባቸውን ነገሮች በእምነትና በትዕግሥት የሚወርሱትን [እንድንመስል]” ያበረታታናል። (ዕብ. 6:12) ዮፍታሔና ሴት ልጁ ሕይወታቸውን የመሩት ‘በአምላክ ላይ እምነት ማሳደር የእሱን ሞገስ ያስገኛል’ ከሚለው መሠረታዊ እውነታ ጋር በሚስማማ መንገድ ነው፤ እኛም የእነሱን ምሳሌ እንከተል።