በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ማበረታቻ በመስጠት ረገድ ግሩም ምሳሌ የሆነውን ይሖዋን ምሰሉ

ማበረታቻ በመስጠት ረገድ ግሩም ምሳሌ የሆነውን ይሖዋን ምሰሉ

“አምላክ . . . በሚደርስብን መከራ ሁሉ ያበረታታናል።”—2 ቆሮ. 1:3, 4 ግርጌ

መዝሙሮች፦ 7, 3

1. በኤደን ዓመፅ በተነሳበት ወቅት ይሖዋ ምን አበረታች ተስፋ ሰጥቶ ነበር?

የሰው ዘር በኃጢአት ከወደቀበትና ፍጽምናውን ካጣበት ጊዜ አንስቶ ይሖዋ ማበረታቻ በመስጠት ረገድ ግሩም ምሳሌ መሆኑን አሳይቷል። በኤደን ዓመፅ በተነሳበት ወቅት ይሖዋ ገና ወደፊት ለሚወለዱት የአዳም ዘሮች ወዲያውኑ አበረታች የሆነ ተስፋ ሰጥቷል። በዘፍጥረት 3:15 ላይ የሚገኘው ትንቢት ትርጉሙን ለተረዱት የሰው ዘሮች ሁሉ ተስፋ የሚፈነጥቅ ነበር፤ ይህ ትንቢት “የጥንቱ እባብ” ማለትም ሰይጣን ዲያብሎስ ከጊዜ በኋላ ከነክፉ ሥራዎቹ እንደሚጠፋ ይገልጻል።—ራእይ 12:9፤ 1 ዮሐ. 3:8

ይሖዋ በጥንት ዘመን የነበሩ አገልጋዮቹን አበረታቷል

2. ይሖዋ ኖኅን ያበረታታው እንዴት ነው?

2 የይሖዋ አገልጋይ የነበረው ኖኅ የኖረው ፈሪሃ አምላክ በሌለው ዓለም ውስጥ ሲሆን በዚያ ወቅት ከነበሩት ሰዎች መካከል ይሖዋን የሚያመልከው የእሱ ቤተሰብ ብቻ ነበር። በወቅቱ ዓመፅና ከተፈጥሮ ውጭ የሆነ የፆታ ግንኙነት በጣም ከመስፋፋቱ የተነሳ ኖኅ ተስፋ ሊቆርጥ ይችል ነበር። (ዘፍ. 6:4, 5, 11፤ ይሁዳ 6) ይሁንና ይሖዋ ለኖኅ እስከ መጨረሻው ‘ከአምላክ ጋር መሄዱን’ እንዲቀጥል የሚረዳ ማበረታቻ ሰጥቶታል። (ዘፍ. 6:9) ይሖዋ ያን ክፉ ዓለም እንደሚያጠፋው የነገረው ከመሆኑም ሌላ ቤተሰቡን ለማዳን ምን ማድረግ እንዳለበት ገልጾለታል። (ዘፍ. 6:13-18) በእርግጥም ይሖዋ ለኖኅ የብርታት ምንጭ ሆኖለታል።

3. ኢያሱ ምን ማበረታቻ ተሰጥቶታል? (በመግቢያው ላይ ያለውን ሥዕል ተመልከት።)

3 ከጊዜ በኋላ ኢያሱ የአምላክን ሕዝብ ወደ ተስፋይቱ ምድር የማስገባት ከባድ ኃላፊነት ተሰጥቶት ነበር። ይህ ደግሞ ክልሉን የተቆጣጠሩትን ኃያላን ብሔራት ተዋግቶ ድል ማድረግን የሚጠይቅ ነበር። ኢያሱ ይህ ተልእኮ ሲሰጠው እንዲሰጋ የሚያደርገው በቂ ምክንያት ነበረው። ይሖዋም ይህን በመገንዘብ ኢያሱን እንዲያበረታታው ሙሴን አዘዘው። አምላክ እንዲህ ብሏል፦ “በዚህ ሕዝብ ፊት የሚሻገረውም ሆነ አንተ ያየሃትን ምድር እንዲወርሱ የሚያደርገው ኢያሱ ስለሆነ እሱን መሪ አድርገህ ሹመው፤ አደፋፍረው፤ አበረታታውም።” (ዘዳ. 3:28) ኢያሱ ሥራውን ከመጀመሩ በፊት ይሖዋ እንዲህ በማለት አበረታቶታል፦ “ደፋርና ብርቱ ሁን ብዬ አዝዤህ አልነበረም? አምላክህ ይሖዋ በምትሄድበት ሁሉ ከአንተ ጋር ስለሆነ አትሸበር፤ አትፍራ።” (ኢያሱ 1:1, 9) ይህ እንዴት ያለ ግሩም ማበረታቻ ነው!

4, 5. (ሀ) ይሖዋ በጥንት ዘመን ለነበሩ ሕዝቦቹ ምን ማበረታቻ ሰጥቷቸዋል? (ለ) ይሖዋ ልጁን ያበረታታው እንዴት ነው?

4 ይሖዋ አገልጋዮቹን በግለሰብ ደረጃ ብቻ ሳይሆን በቡድን ደረጃም አበረታቷቸዋል። ወደፊት በባቢሎን በግዞት ለሚኖረው ሕዝቡ የሚከተለውን የሚያጽናና ሐሳብ አስቀድሞ ተናግሯል፦ “እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ። እኔ አምላክህ ነኝና አትጨነቅ። አበረታሃለሁ፤ አዎ እረዳሃለሁ፤ በጽድቅ ቀኝ እጄ አጥብቄ እይዝሃለሁ።” (ኢሳ. 41:10) ይሖዋ በመጀመሪያው መቶ ዘመን ለነበሩ ክርስቲያኖችም ሆነ በዛሬው ጊዜ ላሉ ሕዝቦቹ ተመሳሳይ ማረጋገጫ ሰጥቷቸዋል።—2 ቆሮንቶስ 1:3, 4ን አንብብ።

5 ኢየሱስም ከአባቱ ማበረታቻ አግኝቷል። በተጠመቀበት ወቅት “በጣም የምደሰትበት የምወደው ልጄ ይህ ነው” የሚል ድምፅ ከሰማይ ሰምቷል። (ማቴ. 3:17) እነዚህ ቃላት ኢየሱስ ምድራዊ አገልግሎቱን ባከናወነባቸው ጊዜያት ሁሉ ምንኛ አበረታተውት ይሆን!

ኢየሱስ ሌሎችን አበረታቷል

6. ስለ ታላንቱ የሚናገረው ምሳሌ ምን ማበረታቻ ይዟል?

6 ኢየሱስ የአባቱን ምሳሌ ተከትሏል። ስለ ሥርዓቱ መደምደሚያ በተናገረው ትንቢት ላይ የጠቀሰው የታላንቱ ምሳሌ ታማኝነትን ያበረታታል። በምሳሌው ላይ የተጠቀሰው ጌታ ለእያንዳንዱ ታማኝ ባሪያ “ጎበዝ፣ አንተ ጥሩና ታማኝ ባሪያ! በጥቂት ነገሮች ታማኝ ሆነህ ተገኝተሃል። ስለዚህ በብዙ ነገሮች ላይ እሾምሃለሁ። ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” በማለት ተናግሯል። (ማቴ. 25:21, 23) ደቀ መዛሙርቱ ይሖዋን በታማኝነት ማገልገላቸውን እንዲቀጥሉ የሚያደርግ እንዴት ያለ ግሩም ማበረታቻ ነው!

7. ኢየሱስ ሐዋርያቱን በተለይም ጴጥሮስን ያበረታታው እንዴት ነው?

7 የኢየሱስ ሐዋርያት ‘ከመካከላችን ታላቅ የሚሆነው ማን ነው?’ በሚል በተደጋጋሚ ይከራከሩ ነበር፤ ሆኖም ኢየሱስ ትሑት እንዲሆኑና ጌታ ከመሆን ይልቅ አገልጋዮች እንዲሆኑ በትዕግሥት አበረታቷቸዋል። (ሉቃስ 22:24-26) በተለይም ጴጥሮስ በተደጋጋሚ ኢየሱስን የሚያሳዝን ነገር አድርጓል። (ማቴ. 16:21-23፤ 26:31-35, 75) ኢየሱስ ግን በጴጥሮስ ላይ ተስፋ ከመቁረጥ ይልቅ ያበረታታው ከመሆኑም በላይ ወንድሞቹን እንዲያበረታ ተልዕኮ ሰጥቶታል።—ዮሐ. 21:16

ቀደም ባሉት ዘመናት የተሰጡ ማበረታቻዎች

8. ሕዝቅያስ የጦር አለቆቹንና የይሁዳን ሕዝብ ለማበረታታት ምን አድርጓል?

8 የይሖዋ ልጅ ወደ ምድር ከመምጣቱና ሌሎችን በማበረታታት ረገድ ፍጹም ምሳሌ ከመተዉ በፊትም እንኳ የይሖዋ ታማኝ አገልጋዮች ማበረታቻ የመስጠትን አስፈላጊነት ተገንዝበው ነበር። አሦራውያን ዛቻ በሰነዘሩበት ወቅት ሕዝቅያስ የጦር አለቆቹንና የይሁዳን ሕዝብ ሰብስቦ አበረታቷል። “ሕዝቡም [እሱ] በተናገረው ቃል ተበረታታ።”—2 ዜና መዋዕል 32:6-8ን አንብብ።

9. ማበረታቻ መስጠትን በተመለከተ ከኢዮብ መጽሐፍ ምን እንማራለን?

9 ኢዮብ እሱ ራሱ ማጽናኛ ያስፈልገው የነበረ ቢሆንም ‘የሚያስጨንቁ አጽናኞች’ ለነበሩት ሦስት ጓደኞቹ ሌሎችን ማበረታታት የሚቻልበትን መንገድ በተመለከተ ጠቃሚ ትምህርት ሰጥቷቸዋል። እሱ በእነሱ ቦታ ቢሆን ኖሮ ‘በአፉ ቃል ያበረታቸውና በከንፈሮቹ ማጽናኛ ያሳርፋቸው እንደነበር’ ገልጾላቸዋል። (ኢዮብ 16:1-5) በመጨረሻም ኢዮብ ከኤሊሁ እንዲሁም ከይሖዋ ከራሱ ማበረታቻ አግኝቷል።—ኢዮብ 33:24, 25፤ 36:1, 11፤ 42:7, 10

10, 11. (ሀ) የዮፍታሔ ሴት ልጅ ማበረታቻ ያስፈልጋት የነበረው ለምንድን ነው? (ለ) በዛሬው ጊዜ ተመሳሳይ ማበረታቻ የሚያስፈልጋቸው እነማን ናቸው?

10 ማበረታቻ ያስፈልጋቸው ከነበሩ ቀደም ባሉት ዘመናት የኖሩ የአምላክ አገልጋዮች መካከል የዮፍታሔ ሴት ልጅ ትገኝበታለች። መስፍኑ ዮፍታሔ አሞናውያንን ለመውጋት ከመውጣቱ በፊት ስእለት ተስሎ ነበር፤ ይሖዋ ድል እንዲያደርግ ከረዳው ከውጊያ ሲመለስ ሊቀበለው የሚወጣውን የመጀመሪያውን ሰው በይሖዋ መቅደስ ውስጥ እንዲያገለግል መሥዋዕት አድርጎ እንደሚሰጥ ተናግሮ ነበር። እንደ አጋጣሚ ሆኖ ድል አድርጎ ሲመለስ እየጨፈረች ልትቀበለው የወጣችው አንድያ ልጁ ነበረች። በዚህ ጊዜ ዮፍታሔ ልቡ ተሰበረ። ያም ቢሆን ድንግል የሆነችው ልጁ ሕይወቷን ሙሉ ሴሎ በሚገኘው የማደሪያ ድንኳን ውስጥ እንድታገለግል በመስጠት ስእለቱን ፈጽሟል።—መሳ. 11:30-35

11 ይህ ሁኔታ ለዮፍታሔ ከባድ እንደነበር አይካድም፤ የአባቷን ውሳኔ በፈቃደኝነት ለተቀበለችው ለዮፍታሔ ሴት ልጅ ደግሞ ሁኔታው ይበልጥ ከባድ ነበር። (መሳ. 11:36, 37) ትዳር የመመሥረት፣ ልጆች የመውለድ እንዲሁም የቤተሰቡን ስም የማስጠራትና ርስት የማቆየት መብቷን ለመተው ፈቃደኛ ሆናለች። በእርግጥም የዮፍታሔ ሴት ልጅ ከማንም በላይ ማጽናኛና ማበረታቻ ያስፈልጋት ነበር። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “ይህም በእስራኤል ውስጥ ልማድ ሆነ፦ የእስራኤል ወጣት ሴቶች የጊልያዳዊውን የዮፍታሔን ሴት ልጅ ለማመስገን በየዓመቱ ለአራት ቀን ያህል ይሄዱ ነበር።” (መሳ. 11:39, 40) በዛሬው ጊዜ ያሉ ‘ለጌታ ነገር’ ይበልጥ ትኩረት ለመስጠት ሲሉ ሳያገቡ የሚኖሩ ክርስቲያኖችስ አድናቆት ሊቸራቸውና ማበረታቻ ሊሰጣቸው አይገባም?—1 ቆሮ. 7:32-35

ሐዋርያት ወንድሞቻቸውን አበረታተዋል

12, 13. ጴጥሮስ ‘ወንድሞቹን ያበረታው’ እንዴት ነው?

12 ኢየሱስ ከመሞቱ በፊት በነበረው ምሽት ላይ ለሐዋርያው ጴጥሮስ እንዲህ ብሎት ነበር፦ “ስምዖን፣ ስምዖን፣ ሰይጣን ሁላችሁንም እንደ ስንዴ ያበጥራችሁ ዘንድ ጥያቄ አቅርቧል። እኔ ግን እምነትህ እንዳይጠፋ ስለ አንተ ምልጃ አቀረብኩ፤ አንተም በተመለስክ ጊዜ ወንድሞችህን አበርታ።”—ሉቃስ 22:31, 32

ሐዋርያት የጻፏቸው መጻሕፍት በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩ ጉባኤዎችን እንዳበረታቱ ሁሉ እኛንም ያበረታቱናል (ከአንቀጽ 12-17⁠ን ተመልከት)

13 ጴጥሮስ በመጀመሪያው መቶ ዘመን ለነበረው የክርስቲያን ጉባኤ እንደ ዓምድ መሆኑን አስመሥክሯል። (ገላ. 2:9) በጴንጤቆስጤ ዕለትና ከዚያ በኋላ ባሉት ጊዜያት ባከናወናቸው ድፍረት የሚጠይቁ ነገሮች አማካኝነት ወንድሞቹን አበረታቷል። ለበርካታ ዓመታት በዘለቀው አገልግሎቱ መገባደጃ አካባቢ ለእምነት ባልንጀሮቹ ደብዳቤ ጽፎላቸው ነበር። የደብዳቤዎቹን ዓላማ ሲገልጽ እንዲህ ብሏል፦ “የጻፍኩላችሁ . . . እናንተን ለማበረታታትና ይህ የአምላክ እውነተኛ ጸጋ እንደሆነ አጥብቄ ለመመሥከር ነው። ይህን ጸጋ አጥብቃችሁ ያዙ።” (1 ጴጥ. 5:12) ጴጥሮስ በመንፈስ መሪነት የጻፋቸው ደብዳቤዎች በጥንት ዘመን ለኖሩም ሆነ ዛሬ ለሚገኙ ክርስቲያኖች የብርታት ምንጭ ሆነዋል፤ ይሖዋ የሰጣቸው ተስፋዎች የሚፈጸሙበትን ጊዜ እየተጠባበቅን ባለንበት በዛሬው ጊዜ እንዲህ ያለውን ማበረታቻ ማግኘታችን ምንኛ አስፈላጊ ነው!—2 ጴጥ. 3:13

14, 15. ሐዋርያው ዮሐንስ በመንፈስ መሪነት የጻፋቸው መጻሕፍት ጥንትም ሆነ ዛሬ ላሉ ክርስቲያኖች የብርታት ምንጭ የሆኑት እንዴት ነው?

14 ሐዋርያው ዮሐንስም በመጀመሪያው መቶ ዘመን ለነበረው የክርስቲያን ጉባኤ እንደ ዓምድ ነበር። ስለ ኢየሱስ አገልግሎት የሚናገረው ትኩረት የሚስብ የወንጌል ዘገባው በጥንት ዘመንም ሆነ በዛሬው ጊዜ ላሉ ክርስቲያኖች የብርታት ምንጭ ሆኗል። እንዲያውም የእውነተኛዎቹ ደቀ መዛሙርት መለያ ፍቅር እንደሆነ የሚገልጸው ኢየሱስ የተናገረው ሐሳብ የሚገኘው በዮሐንስ ወንጌል ውስጥ ብቻ ነው።—ዮሐንስ 13:34, 35ን አንብብ።

15 ዮሐንስ የጻፋቸው ሦስት ደብዳቤዎችም ሌሎች ውድ እውነቶችን ይዘዋል። በፈጸምነው ኃጢአት ምክንያት በበደለኝነት ስሜት በምንሠቃይበት ጊዜ “የኢየሱስ ደም ከኃጢአት ሁሉ [እንደሚያነጻን]” የሚገልጸውን ሐሳብ ስናነብ እፎይታ አናገኝም? (1 ዮሐ. 1:7) ልባችን ሁልጊዜ የሚኮንነን ከሆነ ደግሞ “አምላክ ከልባችን ይልቅ ታላቅ” እንደሆነ ስናነብ በአመስጋኝነት ስሜት ከመሞላታችን የተነሳ እንባ አይተናነቀንም? (1 ዮሐ. 3:20) በተጨማሪም “አምላክ ፍቅር ነው” ብሎ የጻፈው ዮሐንስ ብቻ ነው። (1 ዮሐ. 4:8, 16) በሁለተኛና በሦስተኛ ደብዳቤዎቹ ላይ ደግሞ “በእውነት ውስጥ እየተመላለሱ” ላሉ ክርስቲያኖች ያለውን አድናቆት ገልጿል።—2 ዮሐ. 4፤ 3 ዮሐ. 3, 4

16, 17. ሐዋርያው ጳውሎስ በመጀመሪያው መቶ ዘመን ለነበሩ ክርስቲያኖች ምን ማበረታቻ ሰጥቷል?

16 በመጀመሪያው መቶ ዘመን ወንድሞቹን በማበረታታት ረገድ ከሁሉ የላቀ ሚና የተጫወተው ሐዋርያው ጳውሎስ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም። ክርስትና ከተቋቋመ በኋላ በነበሩት የመጀመሪያዎቹ ዓመታት አብዛኞቹ ሐዋርያት የሚኖሩት የበላይ አካሉ በሚገኝበት በኢየሩሳሌም የነበረ ይመስላል። (ሥራ 8:14፤ 15:2) በይሁዳ የነበሩት ክርስቲያኖች በአንድ አምላክ ብቻ ያምኑ ለነበሩት የአይሁድ እምነት ተከታዮች ስለ ክርስቶስ ይሰብኩ ነበር። በሌላ በኩል ደግሞ ሐዋርያው ጳውሎስ ግሪካውያንንና ሮማውያንን ጨምሮ የአይሁድ እምነት ተከታይ ላልሆኑ የተለያዩ አማልክትን የሚያመልኩ ሰዎች እንዲሰብክ በመንፈስ ቅዱስ ተልኮ ነበር።—ገላ. 2:7-9፤ 1 ጢሞ. 2:7

17 ጳውሎስ በዛሬዋ ቱርክ እንዲሁም በመላው የግሪክና የጣሊያን ግዛት ረጅም ጉዞ በማድረግ አይሁዳዊ ባልሆኑ ሰዎች መካከል የክርስቲያን ጉባኤዎችን አቋቁሟል። እነዚህ አዲስ ክርስቲያኖች ‘በገዛ አገራቸው ሰዎች እጅ መከራ’ ይደርስባቸው ስለነበር ማበረታቻ አስፈልጓቸዋል። (1 ተሰ. 2:14) ጳውሎስ በቅርቡ ለተቋቋመው የተሰሎንቄ ጉባኤ በ50 ዓ.ም. አካባቢ እንደሚከተለው በማለት ጽፏል፦ “ሁላችሁንም በጸሎታችን በጠቀስን ቁጥር ሁልጊዜ አምላክን እናመሰግናለን፤ የእምነት ሥራችሁን፣ ከፍቅር የመነጨ ድካማችሁንና . . . የምታሳዩትን ጽናት . . . ዘወትር እናስባለን።” (1 ተሰ. 1:2, 3) በተጨማሪም “እርስ በርስ ተበረታቱ እንዲሁም እርስ በርስ ተናነጹ” በማለት አንዳቸው ለሌላው የብርታት ምንጭ እንዲሆኑ አሳስቧቸዋል።—1 ተሰ. 5:11

የበላይ አካሉ ለሌሎች ማበረታቻ ይሰጣል

18. በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበረው የበላይ አካል ፊልጶስን ያበረታታው እንዴት ነው?

18 በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበረው የበላይ አካል፣ አመራር ለሚሰጡትም ሆነ ለሌሎች ክርስቲያኖች የብርታት ምንጭ እንደሆነ አሳይቷል። ወንጌላዊው ፊልጶስ ለሳምራውያን ስለ ክርስቶስ በሰበከበት ወቅት የበላይ አካሉ አባል የሆኑ ወንድሞች ሙሉ ድጋፍ አድርገውለታል። እነዚህ ወንድሞች፣ በቅርቡ ክርስቲያን የሆኑት አማኞች መንፈስ ቅዱስን እንዲቀበሉ ይጸልዩላቸው ዘንድ ሁለቱን የበላይ አካል አባላት ማለትም ጴጥሮስንና ዮሐንስን ልከዋል። (ሥራ 8:5, 14-17) ፊልጶስም ሆነ እሱ ወደ ክርስትና እንዲለወጡ የረዳቸው ሰዎች የበላይ አካሉ ባደረገላቸው በዚህ ድጋፍ ምንኛ ተበረታተው ይሆን!

19. የበላይ አካሉ የላከው ደብዳቤ በመጀመሪያው መቶ ዘመን በነበረው የክርስቲያን ጉባኤ ላይ ምን በጎ ተጽዕኖ አሳድሯል?

19 ከጊዜ በኋላ የበላይ አካሉ አይሁዳውያን ያልሆኑ ክርስቲያኖች የሙሴ ሕግ አይሁዳውያንን በሚያዘው መሠረት መገረዝ ይኖርባቸው እንደሆነና እንዳልሆነ ለመወሰን ተሰበሰበ። (ሥራ 15:1, 2) የበላይ አካሉ የመንፈስ ቅዱስን አመራር በመቀበልና ቅዱሳን መጻሕፍትን በማመሣከር እንዲህ ማድረጉ አስፈላጊ እንዳልሆነ ወሰነ፤ ይህን ውሳኔ የሚያሳውቅ ደብዳቤም ለጉባኤዎች ጻፈ። ከዚያም የበላይ አካሉ ተወካዮች ደብዳቤውን ለጉባኤዎች እንዲያደርሱ ተላኩ። ውጤቱስ ምን ሆነ? ወንድሞች ደብዳቤውን “ካነበቡት በኋላ ባገኙት ማበረታቻ እጅግ ተደሰቱ።”—ሥራ 15:27-32

20. (ሀ) በዛሬው ጊዜ ያለው የበላይ አካል ለመላው የወንድማማች ማኅበር ማበረታቻ የሚሰጠው እንዴት ነው? (ለ) በቀጣዩ ርዕስ ላይ የየትኛው ጥያቄ መልስ ይብራራል?

20 በዛሬው ጊዜ ያለው የይሖዋ ምሥክሮች የበላይ አካልም ለቤቴል ቤተሰብ አባላት፣ በመስኩ ላይ ለሚያገለግሉ ልዩ የሙሉ ጊዜ አገልጋዮች ብሎም በመላው የወንድማማች ማኅበር ውስጥ ለታቀፉ እውነተኛ ክርስቲያኖች ማበረታቻ ይሰጣል። በመጀመሪያው መቶ ዘመን እንደነበሩት ክርስቲያኖች ሁሉ በዛሬው ጊዜ ያሉ ክርስቲያኖችም በሚያገኙት ማበረታቻ እጅግ ይደሰታሉ! በተጨማሪም በ2015 የበላይ አካሉ ወደ ይሖዋ ተመለስ የሚል ርዕስ ያለውን ብሮሹር አውጥቷል፤ ይህ ብሮሹር በዓለም ዙሪያ ለሚገኙ በርካታ ሰዎች ከፍተኛ የብርታት ምንጭ ሆኗል። ይሁንና ማበረታቻ በመስጠት ረገድ ይሖዋን መምሰል ያለባቸው በኃላፊነት ቦታ ላይ ያሉ ወንድሞች ብቻ ናቸው? የዚህ ጥያቄ መልስ በቀጣዩ ርዕስ ላይ ይብራራል።