በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ታስታውሳለህ?

ታስታውሳለህ?

በቅርቡ የወጡትን የመጠበቂያ ግንብ እትሞች በደንብ አንብበሃቸዋል? እስቲ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ ሞክር፦

በሌላ አገር የሚኖሩ ወላጆች፣ ልጆቻቸውን በመንፈሳዊ ሲረዱ በየትኛው ቋንቋ ቢጠቀሙ እንደሚሻል በቁም ነገር ሊያስቡበት የሚገባው ለምንድን ነው?

ልጆቻቸው በአካባቢው የሚነገረውን ቋንቋ በትምህርት ቤትና በዙሪያቸው ካሉት ሰዎች መማራቸው አይቀርም። ልጆቹ ከአንድ በላይ ቋንቋ መቻላቸው ይጠቅማቸዋል። ወላጆች፣ ‘ልጆቻችን እውነትን በደንብ መረዳትና መንፈሳዊ እድገት ማድረግ የሚችሉት በአካባቢው በሚነገረው ቋንቋ በሚመራ ጉባኤ ቢካፈሉ ነው? ወይስ በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው በሚመራ ጉባኤ ቢሰበሰቡ?’ የሚለውን ጉዳይ ሊያስቡበት ይገባል። ክርስቲያን ወላጆች ከራሳቸው ፍላጎት ይልቅ የልጆቻቸውን መንፈሳዊነት ሊያስቀድሙ ይገባል።—w17.05 ከገጽ 9-11

ኢየሱስ ጴጥሮስን “ከእነዚህ አስበልጠህ ትወደኛለህ?” ብሎ ሲጠይቀው “እነዚህ” ያለው ምንን ለማመልከት ነው? (ዮሐ. 21:15)

ኢየሱስ፣ አጠገቡ ስለነበሩት ዓሣዎች አሊያም ዓሣ ስለማጥመድ ሥራ እየተናገረ የነበረ ይመስላል። ኢየሱስ ከሞተ በኋላ ጴጥሮስ ወደ ቀድሞ ሥራው ይኸውም ዓሣ ወደ ማጥመድ ተመልሶ ነበር። ክርስቲያኖች ለሰብዓዊ ሥራቸው ምን ያህል ቦታ እንደሚሰጡ ሊያስቡበት ይገባል።—w17.05 ከገጽ 22-23

አብርሃም ሚስቱን እህቱ እንደሆነች አድርጋ እንድትናገር የጠየቃት ለምንድን ነው? (ዘፍ. 12:10-13)

ሣራ ለአብርሃም የአባቱ ልጅ ስለሆነች በእርግጥም እህቱ ነበረች። ሣራ፣ የአብርሃም ሚስት እንደሆነች ብትናገር ኖሮ አብርሃም ሊገደል ይችል ነበር፤ ይህ ከሆነ ደግሞ አብርሃምና ሣራ፣ ተስፋ የተደረገውን ዘር መውለድ አይችሉም ነበር።—wp17.3 ከገጽ 14-15

ኤሊያስ ሁተ የዕብራይስጥ ቋንቋን መማር የሚፈልጉ ሰዎችን ለመርዳት ምን አድርጓል?

ተማሪዎቹ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙትን የዕብራይስጥ ሥርወ ቃላት፣ ከእነዚህ ቃላት ፊትና ኋላ ከሚገቡት ቅጥያ ፊደላት መለየት እንዲችሉ ለመርዳት አሰበ። እያንዳንዱ ሥርወ ቃል ድፍን በሆኑ ፊደላት እንዲጻፍ ያደረገ ሲሆን ከሥርወ ቃሉ ፊትና ኋላ የሚገቡት ቅጥያ ፊደላት ደግሞ ክፍተት ባላቸው ሆሄያት እንዲጻፉ አደረገ። ባለማጣቀሻው የቅዱሳን መጻሕፍት አዲስ ዓለም ትርጉም (እንግሊዝኛ) በግርጌ ማስታወሻዎቹ ላይ ተመሳሳይ ዘዴ ተጠቅሟል።wp17.4 ከገጽ 11-12

አንድ ክርስቲያን፣ ሌሎች ከሚያደርሱበት ጥቃት ራሱን ለመከላከል ሲል የጦር መሣሪያ በመያዝ ረገድ የትኞቹን ነጥቦች ከግምት ማስገባት ይኖርበታል?

ከግምት ማስገባት ከሚኖርበት ነጥቦች አንዳንዶቹ፦ በአምላክ ዓይን ሕይወት ቅዱስ ነው። ኢየሱስ፣ ተከታዮቹ ሰይፍ እንዲይዙ የነገራቸው ራሳቸውን ከጥቃት ለመከላከል እንዲጠቀሙበት አስቦ አይደለም። (ሉቃስ 22:36, 38) ሰይፋችንን ማረሻ እንድናደርግ ይጠበቅብናል። ሕይወት ከማንኛውም ቁሳዊ ነገር የበለጠ ዋጋ አለው። ለሌሎች ሕሊና እንጠነቀቃለን፤ እንዲሁም ምሳሌ ሆነን ለመገኘት ጥረት እናደርጋለን። (2 ቆሮ. 4:2)—w17.07 ከገጽ 31-32

ስለ ኢየሱስ የልጅነት ሕይወት የሚናገሩት የማቴዎስና የሉቃስ ዘገባዎች የሚለያዩት ለምንድን ነው?

የማቴዎስ ዘገባ ትኩረት ያደረገው ከዮሴፍ ጋር በተያያዙ ክንውኖች ላይ ነው፤ ለምሳሌ ዮሴፍ፣ የማርያምን መፀነስ ሲያውቅ ምን እንደተሰማው እንዲሁም ቤተሰቡን ይዞ ወደ ግብፅ እንዲሸሽና በኋላም እንዲመለስ አንድ መልአክ እንደነገረው ዘግቧል። የሉቃስ ዘገባ ይበልጥ የሚያተኩረው በማርያም ላይ ነው፤ ለምሳሌ ያህል፣ ማርያም ኤልሳቤጥን ለመጠየቅ እንደሄደች እንዲሁም ኢየሱስ አብሯቸው ወደ ቤት ከመመለስ ይልቅ ቤተ መቅደሱ ውስጥ በቆየ ጊዜ ምን እንደተሰማት ዘግቧል።—w17.08 ገጽ 32

መጽሐፍ ቅዱስ የትኞቹን ፈተናዎች ተቋቁሞ ጸንቷል?

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተሠራባቸው ቃላትና አገላለጾች በጊዜ ሂደት ትርጉማቸው ተለውጧል። ፖለቲካዊ ለውጦች፣ በአንድ ወቅት በስፋት ይነገር የነበረው ቋንቋ እንዲለወጥ አድርገዋል። መጽሐፍ ቅዱስን ተራው ሕዝብ ወደሚጠቀምበት ቋንቋ ለመተርጎም የተደረገው ጥረት ተቃውሞ አጋጥሞታል።—w17.09 ከገጽ 19-21

ጠባቂ መልአክ አለን?

የለንም። በአንድ ወቅት ኢየሱስ፣ የደቀ መዛሙርቱ መላእክት በአባቱ ፊት እንደሚቀርቡ ተናግሮ ነበር። (ማቴ. 18:10) ይህን የተናገረው፣ መላእክት የእሱን ደቀ መዛሙርት በግለሰብ ደረጃ ትኩረት ሰጥተው እንደሚከታተሏቸው ለማመልከት እንጂ ለእያንዳንዳቸው ተአምራዊ ጥበቃ እንደሚያደርጉላቸው ለመግለጽ አይደለም።—wp17.5 ገጽ 5

ከሁሉ የላቀው የፍቅር ዓይነት የትኛው ነው?

ትክክለኛ በሆኑ መሠረታዊ ሥርዓቶች ላይ የተመሠረተ በሚሆንበት ጊዜ አጋፔ ከሁሉ የላቀው የፍቅር ዓይነት ነው። ይህ የፍቅር ዓይነት ለአንድ ሰው የሚኖረንን የመውደድ ስሜት የሚያካትት ቢሆንም ላቅ ያሉ መሠረታዊ ሥርዓቶች የሚታዩበት ፍቅር ነው፤ ለምሳሌ ይህ ዓይነቱ ፍቅር፣ ለሌሎች ጥቅም ስንል በምናከናውነው ከራስ ወዳድነት ነፃ የሆነ ተግባር ይገለጻል።—w17.10 ገጽ 7