በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የጥናት ርዕስ 51

ይሖዋን ምን ያህል ታውቀዋለህ?

ይሖዋን ምን ያህል ታውቀዋለህ?

“ስምህን የሚያውቁ በአንተ ይታመናሉ፤ ይሖዋ ሆይ፣ አንተን የሚሹትን ፈጽሞ አትተዋቸውም።”—መዝ. 9:10

መዝሙር 56 እውነትን የራስህ አድርግ

ማስተዋወቂያ *

1-2. የአንግሄሊቶ ተሞክሮ እንደሚያሳየው እያንዳንዳችን ምን ማድረግ አለብን?

ወላጆችህ የይሖዋ ምሥክሮች ናቸው? ከሆነ ልትዘነጋው የማይገባ አንድ ነገር አለ፦ ከይሖዋ ጋር የምትመሠርተውን ዝምድና ከእነሱ መውረስ አትችልም። ወላጆቻችን የአምላክ አገልጋዮች ሆኑም አልሆኑ እያንዳንዳችን ከይሖዋ ጋር ወዳጅነት መመሥረት ያለብን ራሳችን ነን።

2 አንግሄሊቶ የተባለውን ወንድም ተሞክሮ እንመልከት። አንግሄሊቶ ያደገው የይሖዋ ምሥክር በሆነ ቤተሰብ ውስጥ ነው። ይሁንና በአሥራዎቹ ዕድሜ ላይ እያለ ከአምላክ ጋር የጠበቀ ወዳጅነት አልነበረውም። አንግሄሊቶ “ይሖዋን የማገለግለው ቤተሰቦቼ እንዲህ ስለሚያደርጉ ብቻ ነበር” በማለት በሐቀኝነት ተናግሯል። ሆኖም አንግሄሊቶ የአምላክን ቃል ለማንበብና ባነበበው ላይ ለማሰላሰል ጊዜ መደበ፤ ወደ ይሖዋም ይበልጥ አዘውትሮ መጸለይ ጀመረ። ታዲያ ምን ውጤት አገኘ? አንግሄሊቶ “ከውዱ አባቴ ከይሖዋ ጋር መቀራረብ የምችለው፣ እኔ ራሴ ስለ እሱ ለማወቅ ጥረት ካደረግኩ ብቻ እንደሆነ ተገነዘብኩ” ብሏል። የአንግሄሊቶ ተሞክሮ የሚከተሉትን አስፈላጊ ጥያቄዎች እንድናነሳ ያደርገናል፦ ስለ ይሖዋ መሠረታዊ ነገሮችን በማወቅና እሱን በሚገባ በማወቅ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው? ደግሞስ ይሖዋን ማወቅ የምንችለው እንዴት ነው?

3. ስለ ይሖዋ በማወቅና እሱን በሚገባ በማወቅ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው?

3 አንድ ሰው የአምላክን ስም እንዲሁም እሱ የተናገራቸውንና ያደረጋቸውን አንዳንድ ነገሮች የሚያውቅ ከሆነ ስለ ይሖዋ ያውቃል ልንል እንችላለን። ይሖዋን በደንብ ማወቅ ግን ከዚህ ያለፈ ነገርን ይጨምራል። ጊዜ መድበን ስለ ይሖዋ እና አስደናቂ ስለሆኑት ባሕርያቱ መማር ያስፈልገናል። ይሖዋ አንድን ነገር እንዲናገር ወይም እንዲያደርግ ያነሳሳው ምን እንደሆነ መረዳት የምንችለው እንዲህ ካደረግን ብቻ ነው። ይህም አስተሳሰባችን፣ ውሳኔያችንና ድርጊታችን በእሱ ዘንድ ተቀባይነት እንዳለውና እንደሌለው ለማስተዋል ይረዳናል። ይሖዋ ከእኛ ምን እንደሚፈልግ ከተረዳን በኋላ ደግሞ የተማርነውን በተግባር ማዋል ይኖርብናል።

4. በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉትን ምሳሌዎች መመርመራችን ምን ጥቅም ያስገኝልናል?

4 አንዳንድ ሰዎች ይሖዋን ማገልገል በመፈለጋችን ያሾፉብን ይሆናል፤ ከሕዝቦቹ ጋር መሰብሰብ ስንጀምር ደግሞ ይበልጥ ሊቃወሙን ይችላሉ። በይሖዋ የምንታመን ከሆነ ግን እሱ ፈጽሞ አይተወንም። በአምላክ መታመናችን ከእሱ ጋር የዕድሜ ልክ ወዳጅነት ለመመሥረት ያስችለናል። ለመሆኑ ይሖዋን በደንብ ማወቅ እንችላለን? አዎ እንችላለን! እንደ ሙሴና ንጉሥ ዳዊት ያሉ ፍጹም ያልሆኑ ሰዎች የተዉት ምሳሌ ይህ የሚቻል ነገር መሆኑን ያረጋግጣል። እነዚህ ሰዎች ያደረጉትን ነገር ስንመረምር ለሚከተሉት ሁለት ጥያቄዎች መልስ እናገኛለን፦ ይሖዋን ሊያውቁት የቻሉት እንዴት ነው? ከእነሱ ምሳሌስ ምን እንማራለን?

ሙሴ “የማይታየውን አምላክ” አይቷል

5. ሙሴ ምን ለማድረግ መርጧል?

5 ሙሴ በተማረው ነገር ላይ ተመሥርቶ ውሳኔ አድርጓል። ሙሴ 40 ዓመት ገደማ ሲሆነው፣ “የፈርዖን የልጅ ልጅ” ተብሎ ከመጠራት ይልቅ የአምላክ ሕዝቦች ከሆኑት ዕብራውያን ጋር መተባበርን መረጠ። (ዕብ. 11:24) ሙሴ የነበረውን ከፍተኛ ቦታ መሥዋዕት አድርጓል። በግብፅ ባሪያ ከሆኑት ዕብራውያን ጋር የወገነ ሲሆን ይህን ያደረገው፣ ውሳኔው ኃያል ገዢ የነበረውንና እንደ አምላክ የሚታየውን ፈርዖንን ሊያስቆጣው እንደሚችል እያወቀ ነው። ይህ እንዴት ያለ አስደናቂ እምነት ነው! ሙሴ በይሖዋ ታምኗል። እንዲህ ዓይነቱ የመተማመን ስሜት ደግሞ ዘላቂ ለሆነ ወዳጅነት የመሠረት ድንጋይ ነው።—ምሳሌ 3:5

6. ከሙሴ ምሳሌ ምን እንማራለን?

6 ከዚህ ምን ትምህርት እናገኛለን? ሁላችንም እንደ ሙሴ ልናደርገው የሚገባ ውሳኔ አለ፦ አምላክን ለማገልገልና ከሕዝቡ ጋር ለመተባበር እንመርጣለን? አምላክን ለማገልገል ስንል መሥዋዕት መክፈል ያስፈልገን ይሆናል፤ እንዲሁም ይሖዋን ከማያውቁ ሰዎች ተቃውሞ ሊያጋጥመን ይችላል። በሰማዩ አባታችን የምንታመን ከሆነ ግን እንደሚረዳን መተማመን እንችላለን!

7-8. ሙሴ ስለ ምን መማሩን ቀጥሏል?

7 ሙሴ ስለ ይሖዋ ባሕርያት መማሩንና የእሱን ፈቃድ ማድረጉን ቀጥሏል። አንድ ምሳሌ እንውሰድ፦ ሙሴ እስራኤላውያንን ከባርነት ነፃ እንዲያወጣ በተጠየቀ ጊዜ እንዲህ ለማድረግ ብቃት እንደሌለው ተሰምቶት ነበር፤ በተደጋጋሚ ጊዜም ለይሖዋ ይህንን ነግሮታል። በዚህ ጊዜ አምላክ ርኅራኄ በሚንጸባረቅበት መንገድ መልስ የሰጠው ሲሆን የሚያስፈልገውን እርዳታም አድርጎለታል። (ዘፀ. 4:10-16) በውጤቱም ሙሴ ኃይለኛ የሆኑ የፍርድ መልእክቶችን ለፈርዖን ማድረስ ችሏል። ከዚያም ይሖዋ እስራኤላውያንን በማዳን እንዲሁም ፈርዖንንና ሠራዊቱን በቀይ ባሕር ውስጥ በማስመጥ ኃይሉን ሲገልጥ ሙሴ ተመልክቷል።—ዘፀ. 14:26-31፤ መዝ. 136:15

8 ሙሴ እስራኤላውያንን ከግብፅ ካወጣቸው በኋላ በተደጋጋሚ ያጉረመርሙ ነበር። ያም ቢሆን ይሖዋ ከግብፅ ባርነት ነፃ ያወጣቸውን እነዚህን ሰዎች በታላቅ ትዕግሥት እንደያዛቸው ሙሴ ተመልክቷል። (መዝ. 78:40-43) ከዚህም ሌላ ይሖዋ የሙሴን ጥያቄ ለማስተናገድ ሲል ሐሳቡን በመቀየር አስደናቂ ትሕትና አሳይቷል፤ ሙሴም ይህን አስተውሎ መሆን አለበት።—ዘፀ. 32:9-14

9. በዕብራውያን 11:27 መሠረት ሙሴ ከይሖዋ ጋር ምን ያህል ይቀራረብ ነበር?

9 ሙሴ እስራኤላውያንን ከግብፅ ይዞ ከወጣ በኋላም ከይሖዋ ጋር ያለው ዝምድና በጣም ተጠናክሯል፤ እንዲያውም በሰማይ ያለውን አባቱን ያየው ያህል ነበር። (ዕብራውያን 11:27ን አንብብ።) መጽሐፍ ቅዱስ፣ ዝምድናቸው ምን ያህል የጠበቀ እንደነበር ሲገልጽ “አንድ ሰው ከሌላ ሰው ጋር እንደሚነጋገር ይሖዋ ከሙሴ ጋር ፊት ለፊት ይነጋገር ነበር” ይላል።—ዘፀ. 33:11

10. ይሖዋን በደንብ ለማወቅ ምን ማድረግ ያስፈልገናል?

10 ከዚህ የምናገኘው ትምህርት ምንድን ነው? ይሖዋን በደንብ ለማወቅ ስለ ባሕርያቱ መማር ብቻ በቂ አይደለም፤ የእሱን ፈቃድ ማድረግም ያስፈልገናል። በዛሬው ጊዜ የይሖዋ ፈቃድ “ሁሉም ዓይነት ሰዎች እንዲድኑና የእውነትን ትክክለኛ እውቀት እንዲያገኙ ነው።” (1 ጢሞ. 2:3, 4) የአምላክን ፈቃድ የምናደርግበት አንዱ መንገድ ሌሎችን ስለ ይሖዋ ማስተማር ነው።

11. ሌሎችን ስለ ይሖዋ ማስተማራችን እሱን ይበልጥ ለማወቅ የሚያስችለን እንዴት ነው?

11 ሌሎችን ስለ ይሖዋ ስናስተምር ብዙ ጊዜ እኛም እሱን ይበልጥ እያወቅነው እንሄዳለን። ለምሳሌ፣ ይሖዋ ትክክለኛ የልብ ዝንባሌ ወዳላቸው ሰዎች ሲመራን የእሱን ርኅራኄ ይበልጥ መመልከት እንችላለን። (ዮሐ. 6:44፤ ሥራ 13:48) መጽሐፍ ቅዱስን የምናስጠናቸው ሰዎች ከመጥፎ ልማዳቸው ተላቀው አዲሱን ስብዕና መላበስ ሲጀምሩ የአምላክ ቃል ያለውን ኃይል እናያለን። (ቆላ. 3:9, 10) በተጨማሪም ይሖዋ በክልላችን ያሉ ብዙ ሰዎች ስለ እሱ ተምረው ለመዳን የሚያስችሏቸው የተለያዩ አጋጣሚዎች እንዲያገኙ ማድረጉ ስለ ትዕግሥቱ ያስተምረናል።—ሮም 10:13-15

12. በዘፀአት 33:13 ላይ እንደተገለጸው ሙሴ ምን ልመና አቅርቧል? ለምንስ?

12 ሙሴ ከይሖዋ ጋር ያለውን ዝምድና ከፍ አድርጎ ይመለከት ነበር። ሙሴ በይሖዋ ስም አስደናቂ ተአምራትን ከፈጸመ በኋላም እንኳ ስለ እሱ ይበልጥ ማወቅ ፈልጎ ነበር፤ በመሆኑም ይሖዋ ይህን ለማድረግ እንዲረዳው በአክብሮት ልመና አቅርቧል። (ዘፀአት 33:13ን አንብብ።) ሙሴ ይህን ጥያቄ ሲያቀርብ በ80ዎቹ ዕድሜ ውስጥ ነበር፤ ሆኖም ስለ አፍቃሪ ሰማያዊ አባቱ ሊማር የሚችለው ብዙ ነገር እንዳለ ተገንዝቦ ነበር።

13. ከአምላክ ጋር ያለንን ዝምድና ከፍ አድርገን እንደምንመለከት ከምናሳይባቸው መንገዶች አንዱ ምንድን ነው?

13 ከዚህ ምን ትምህርት እናገኛለን? ይሖዋን ለረጅም ዓመታት ስናገለግል ብንቆይም ከእሱ ጋር ያለንን ዝምድና ፈጽሞ አቅልለን መመልከት የለብንም። ከአምላክ ጋር ያለንን ወዳጅነት ከፍ አድርገን እንደምንመለከት ከምናሳይባቸው መንገዶች አንዱ ከእሱ ጋር በጸሎት መነጋገር ነው።

14. ስለ አምላክ ይበልጥ ለመማር ጸሎት በጣም አስፈላጊ ነው የምንለው ለምንድን ነው?

14 ጥሩ የሐሳብ ግንኙነት ጠንካራ ዝምድና ለመመሥረት እጅግ አስፈላጊ ነው። ስለዚህ አዘውትረህ በመጸለይ ወደ አምላክ ቅረብ፤ የውስጥ ስሜትህን አውጥተህ ለእሱ ለመንገር ፈጽሞ አትፍራ። (ኤፌ. 6:18) ክሪስታ የተባለች በቱርክ የምትኖር እህት እንዲህ ብላለች፦ “ሐሳቤን ለይሖዋ በገለጽኩና የእሱን እርዳታ በተመለከትኩ ቁጥር ለእሱ ያለኝ ፍቅር እያደገ ይመጣል፤ እንዲሁም የበለጠ እተማመንበታለሁ። ይሖዋ ጸሎቴን ሲመልስልኝ መመልከቴ እሱ አባቴና ወዳጄ እንደሆነ እንዲሰማኝ አድርጓል።”

ይሖዋ እንደ ልቤ ያለው ሰው

15. ይሖዋ ስለ ንጉሥ ዳዊት ምን ብሏል?

15 ንጉሥ ዳዊት የተወለደው ራሱን ለይሖዋ አምላክ በወሰነ ብሔር ውስጥ ነው። ሆኖም ዳዊት ይሖዋን ያመልክ የነበረው ቤተሰቡ የይሖዋ አገልጋዮች ስለሆኑ አይደለም። ከአምላክ ጋር በግለሰብ ደረጃ ዝምድና መሥርቷል፤ ይሖዋም ዳዊትን በጣም ይወደው ነበር። ይሖዋ ራሱ ስለ ዳዊት ሲናገር “እንደ ልቤ የሆነው” ብሎታል። (ሥራ 13:22) ለመሆኑ ዳዊት ከይሖዋ ጋር ይህን ያህል ሊቀራረብ የቻለው እንዴት ነው?

16. ዳዊት ፍጥረትን በመመልከት ስለ ይሖዋ ምን ተምሯል?

16 ዳዊት ከፍጥረት ስለ ይሖዋ ተምሯል። ዳዊት፣ ልጅ እያለ የአባቱን በጎች በመጠበቅ መስክ ላይ በርካታ ሰዓታት ያሳልፍ ነበር። ይሖዋ በፈጠራቸው ነገሮች ላይ ማሰላሰል የጀመረው በዚህ ጊዜ ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ፣ ዳዊት በምሽቱ ሰማይ ላይ የተረጩትን ከዋክብት በማድነቅ ብቻ አልተወሰነም። ከዋክብቱን የፈጠራቸውን አምላክ ባሕርያትም አስተውሎ መሆን አለበት። በመሆኑም “ሰማያት የአምላክን ክብር ይናገራሉ፤ ጠፈርም የእጆቹን ሥራ ያውጃል” ብሎ ለመጻፍ ተነሳስቷል። (መዝ. 19:1, 2) ዳዊት፣ የሰው ልጆች ስለተሠሩበት መንገድ ማሰላሰሉ የይሖዋን ድንቅ ጥበብ ለማስተዋል አስችሎታል። (መዝ. 139:14) ዳዊት የይሖዋን ሥራዎች ለመረዳት ያደረገው ጥረት እሱ ከይሖዋ አንጻር ሲታይ ኢምንት መሆኑን እንዲገነዘብ አድርጎታል።—መዝ. 139:6

17. በፍጥረት ላይ የምናሰላስል ከሆነ ምን ትምህርት እናገኛለን?

17 ከዚህ የምናገኘው ትምህርት ምንድን ነው? ስለ ፍጥረት የበለጠ የማወቅ ፍላጎት ይኑራችሁ። ይሖዋ ውብ አድርጎ በፈጠራት በዚህች ምድር ላይ ላሉት ነገሮች ትኩረት ስጡ፤ ለፍጥረት ሥራዎች አድናቆት ይኑራችሁ! በዙሪያችሁ ባሉት የፍጥረት ሥራዎች ይኸውም በተክሎች፣ በእንስሳት እንዲሁም በሰዎች አካል ላይ በየዕለቱ በማሰላሰል እነዚህ ነገሮች ስለ ይሖዋ ምን እንደሚያስተምሯችሁ ለማሰብ ሞክሩ። እንዲህ ካደረጋችሁ በእያንዳንዱ ቀን ስለ አፍቃሪው አባታችሁ የምትማሩት ብዙ ነገር ይኖራል። (ሮም 1:20) እንዲሁም በእያንዳንዱ ቀን ለይሖዋ ያላችሁ ፍቅር እያደገ ይሄዳል።

18. በመዝሙር 18 ላይ እንደተገለጸው ዳዊት ምን አምኖ ተቀብሏል?

18 ዳዊት ይሖዋ እየረዳው እንደሆነ አስተውሎ ነበር። ለምሳሌ ያህል፣ ዳዊት የአባቱን በጎች ከአንበሳና ከድብ በታደጋቸው ጊዜ እነዚህን አደገኛ አራዊት እንዲያሸንፍ የረዳው ይሖዋ መሆኑን አስተውሎ ነበር። ግዙፉን ጦረኛ ጎልያድን ድል በነሳበት ወቅትም ይሖዋ እየመራው እንደሆነ በግልጽ አይቷል። (1 ሳሙ. 17:37) ቅናት ከተጠናወተው ከንጉሥ ሳኦል ይሸሽ በነበረበት ወቅት ይሖዋ ከአሳዳጁ እጅ እንዳዳነው ተገንዝቧል። (መዝ. 18 አናት ላይ ያለው መግለጫ) ዳዊት ኩሩ ቢሆን ኖሮ እነዚህን ነገሮች በራሱ ኃይል እንደተወጣቸው ሊሰማው ይችል ነበር። እሱ ግን ትሑት ስለሆነ በሕይወቱ ውስጥ የይሖዋን እርዳታ እንዳገኘ አምኖ ተቀብሏል።—መዝ. 138:6

19. ከዳዊት ምሳሌ ምን ትምህርት እናገኛለን?

19 ከዚህ የምናገኘው ትምህርት ምንድን ነው? የይሖዋን እርዳታ ከመጠየቅ ባለፈ እንዴት እንደሚረዳን ለማስተዋል ጥረት ማድረግ ይኖርብናል። ያለብንን የአቅም ገደብ በትሕትና አምነን ከተቀበልን ይሖዋ የሚጎድለንን ነገር ሲያሟላልን በግልጽ መመልከት እንችላለን። ይሖዋ እንዴት እንደረዳን ባስተዋልን ቁጥር ደግሞ ከእሱ ጋር ያለን ዝምድና ይበልጥ እየተጠናከረ ይሄዳል። በፊጂ የሚኖር አይሳክ የተባለ ይሖዋን ለብዙ ዓመታት ያገለገለ ወንድም ይህ እውነት መሆኑን በራሱ ሕይወት ተመልክቷል። እንዲህ ብሏል፦ “ወደኋላ መለስ ብዬ ሳስብ፣ መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ከጀመርኩበት ጊዜ አንስቶ እስከ ዛሬ ድረስ ይሖዋ በብዙ መንገዶች እንደረዳኝ አስተውላለሁ። ይህም ይሖዋ እውን እንዲሆንልኝ አድርጓል።”

20. ዳዊት ከአምላክ ጋር ከነበረው ዝምድና ምን እንማራለን?

20 ዳዊት የይሖዋን ባሕርያት ለማንጸባረቅ ጥረት አድርጓል። ይሖዋ የፈጠረን የእሱን ባሕርያት ማንጸባረቅ እንድንችል አድርጎ ነው። (ዘፍ. 1:26) ስለ ይሖዋ ባሕርያት ይበልጥ ባወቅን መጠን እሱን ይበልጥ እየመሰልን እንሄዳለን። ዳዊት የሰማይ አባቱን በደንብ ያውቀው ስለነበር ከሌሎች ጋር ባለው ግንኙነት ይሖዋን መምሰል ችሏል። አንድ ምሳሌ እንመልከት። ዳዊት ከቤርሳቤህ ጋር ምንዝር በመፈጸምና በኋላም ባሏን በማስገደል በይሖዋ ላይ ኃጢአት ሠርቷል። (2 ሳሙ. 11:1-4, 15) ይሖዋ ግን ለሌሎች ምሕረት ያሳይ ለነበረው ለዳዊት ምሕረት ለማሳየት መርጧል። ዳዊት ከይሖዋ ጋር የጠበቀ ዝምድና ስለነበረው በእስራኤል ውስጥ በጣም ተወዳጅ ንጉሥ ለመሆን በቅቷል፤ ይሖዋም ሌሎች የእስራኤል ነገሥታትን የሚመዝነው ከእሱ አንጻር ነበር።—1 ነገ. 15:11፤ 2 ነገ. 14:1-3

21. ከኤፌሶን 4:24 እና 5:1 ጋር በሚስማማ መልኩ ‘አምላክን መምሰላችን’ ምን ጥቅሞች ያስገኝልናል?

21 ከዚህ ምን ትምህርት እናገኛለን? ‘አምላክን መምሰል’ አለብን። ይህን ማድረጋችን የሚጠቅመን ከመሆኑም ሌላ ይሖዋን ይበልጥ ለማወቅ ያስችለናል። የአምላክን ባሕርያት ለመምሰል የምንጥር ከሆነ የእሱ ልጆች መሆናችንን እናረጋግጣለን።ኤፌሶን 4:24⁠ን እና 5:1ን አንብብ።

ይሖዋን ይበልጥ ለማወቅ ጥረት ማድረግ

22-23. ስለ ይሖዋ የተማርነውን ነገር በተግባር ስናውል ምን ጥቅም እናገኛለን?

22 እስካሁን እንዳየነው ይሖዋ በፍጥረትና በቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ አማካኝነት ራሱን ገልጦልናል። መጽሐፍ ቅዱስ ልንመስላቸው የሚገቡ እንደ ሙሴና ዳዊት ያሉ ታማኝ የአምላክ አገልጋዮችን ታሪክ ይዟል። ይሖዋ የራሱን ድርሻ ተወጥቷል። ስለ እሱ ለመማር ዓይናችንን፣ ጆሯችንን እና ልባችንን ዝግጁ ማድረግ ደግሞ የእኛ ድርሻ ነው።

23 ስለ ይሖዋ መማራችንን መቼም ቢሆን አናቆምም። (መክ. 3:11) ዋናው ነገር ‘ስለ ይሖዋ ምን ያህል እናውቃለን?’ የሚለው ሳይሆን ‘ባወቅነው ነገር ምን እናደርጋለን?’ የሚለው ነው። የተማርነውን በተግባር የምናውልና አፍቃሪ አባታችንን ለመምሰል ጥረት የምናደርግ ከሆነ እሱም ወደ እኛ ይበልጥ ይቀርባል። (ያዕ. 4:8) ይሖዋ፣ እሱን የሚሹትን ሰዎች ፈጽሞ እንደማይተው በቃሉ አማካኝነት አረጋግጦልናል።

መዝሙር 80 “ይሖዋ ጥሩ መሆኑን ቅመሱ፤ እዩም”

^ አን.5 ብዙ ሰዎች አምላክ እንዳለ ያምናሉ፤ ሆኖም በሚገባ አያውቁትም። ለመሆኑ ይሖዋን ማወቅ ሲባል ምን ማለት ነው? ከይሖዋ ጋር ጠንካራ ዝምድና መመሥረት ስለሚቻልበት መንገድ ከሙሴና ከንጉሥ ዳዊት ምን እንማራለን? ይህ ርዕስ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ይሰጣል።