በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የጥናት ርዕስ 48

“የጀመራችሁትን ሥራ ዳር አድርሱት”

“የጀመራችሁትን ሥራ ዳር አድርሱት”

“የጀመራችሁትን ሥራ ዳር አድርሱት።”—2 ቆሮ. 8:11

መዝሙር 35 ‘ይበልጥ አስፈላጊ የሆኑትን ነገሮች ለይታችሁ እወቁ’

ማስተዋወቂያ *

1. ይሖዋ ምን እንድናደርግ ፈቅዶልናል?

ይሖዋ፣ በሕይወታችን ውስጥ የራሳችንን ውሳኔ እንድናደርግ ፈቅዶልናል። ጥሩ ውሳኔዎችን ማድረግ እንድንችል የሚያሠለጥነን ከመሆኑም ሌላ እሱን የሚያስደስቱ ውሳኔዎችን ስናደርግ ያሰብነው እንዲሳካልን ይረዳናል። (መዝ. 119:173) በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘውን ጥበብ ተግባራዊ ባደረግን መጠን ደግሞ ጥሩ ውሳኔ የማድረግ ችሎታችን እየተሻሻለ ይሄዳል።—ዕብ. 5:14

2. አንድ ውሳኔ ካደረግን በኋላ ምን ተፈታታኝ ሁኔታ ሊያጋጥመን ይችላል?

2 ይሁንና ያደረግነው ውሳኔ ጥበብ የተንጸባረቀበት ቢሆንም እንኳ የጀመርነውን ዳር ማድረስ ተፈታታኝ ሊሆንብን ይችላል። በዚህ ረገድ እስቲ አንዳንድ ምሳሌዎችን እንመልከት፦ አንድ ወጣት ወንድም መጽሐፍ ቅዱስን ከዳር እስከ ዳር አንብቦ ለመጨረስ ይወስናል። በዕቅዱ መሠረት ለተወሰኑ ሳምንታት ያህል ሲያነብ ቢቆይም በዚያው መቀጠል አልቻለም። አንዲት እህት የዘወትር አቅኚ ሆና ለማገልገል ብትወስንም ዛሬ ነገ ስትል አቅኚነት መጀመር አልቻለችም። የአንድ ጉባኤ የሽማግሌዎች አካል፣ በጉባኤው ውስጥ ላሉ አስፋፊዎች እረኝነት በማድረግ ረገድ የበለጠ ለመሥራት በአንድ ድምፅ ወሰነ፤ ሆኖም ከወራት በኋላም ሽማግሌዎቹ ውሳኔያቸውን ተግባራዊ አላደረጉም። ከላይ የተጠቀሱት ሁኔታዎች የተለያዩ ቢሆኑም አንድ የሚያመሳስላቸው ነገር አለ። ግለሰቦቹ ውሳኔያቸውን ዳር ማድረስ አልቻሉም። በመጀመሪያው መቶ ዘመን በቆሮንቶስ የነበሩ ክርስቲያኖችም እንዲህ ዓይነት ተፈታታኝ ሁኔታ አጋጥሟቸው ነበር። ከእነሱ ምን መማር እንደምንችል እስቲ እንመልከት።

3. የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ምን ውሳኔ አድርገው ነበር? ሆኖም ምን ሳያደርጉ ቀሩ?

3 በ55 ዓ.ም. ገደማ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች አንድ አስፈላጊ ውሳኔ አድርገው ነበር። እነዚህ ክርስቲያኖች በኢየሩሳሌምና በይሁዳ ያሉ ወንድሞቻቸው በችግርና በድህነት ውስጥ እንዳሉ እንዲሁም ሌሎች ጉባኤዎች እነሱን ለመርዳት መዋጮ እያሰባሰቡ እንደሆነ ሰሙ። የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ደግነትና ልግስና ማሳየት ስለፈለጉ እነሱም መዋጮ ለማድረግ ወሰኑ፤ በመሆኑም እርዳታ ማድረግ ስለሚችሉበት መንገድ ሐዋርያው ጳውሎስን ጠየቁት። እሱም ለጉባኤው መመሪያ የላከ ከመሆኑም ሌላ መዋጮ በማሰባሰቡ ሥራ እንዲረዳቸው ለቲቶ ኃላፊነት ሰጠው። (1 ቆሮ. 16:1፤ 2 ቆሮ. 8:6) ይህ ከሆነ የተወሰኑ ወራት ቢያልፉም የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ውሳኔያቸውን ተግባራዊ አላደረጉም። በዚህም ምክንያት የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች የሚልኩት የልግስና ስጦታ ከሌሎች ጉባኤዎች መዋጮ ጋር ወደ ኢየሩሳሌም ለመድረስ ዝግጁ የሚሆን አይመስልም ነበር።—2 ቆሮ. 9:4, 5

4. በ2 ቆሮንቶስ 8:7, 10, 11 ላይ እንደተገለጸው ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ምን ማበረታቻ ሰጥቷቸዋል?

4 የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ጥሩ ውሳኔ አድርገው ነበር፤ ጳውሎስም ቢሆን አስደናቂ ለሆነው እምነታቸው እንዲሁም ልግስና ለማድረግ ለነበራቸው ጉጉት አመስግኗቸዋል። ሆኖም የጀመሩትን ዳር እንዲያደርሱ ማበረታታትም አስፈልጎታል። (2 ቆሮንቶስ 8:7, 10, 11ን አንብብ።) ይህ ዘገባ ታማኝ ክርስቲያኖችም እንኳ ያደረጉትን ጥሩ ውሳኔ በተግባር ማዋል ተፈታታኝ ሊሆንባቸው እንደሚችል ያስገነዝበናል።

5. የየትኞቹን ጥያቄዎች መልስ እንመለከታለን?

5 እንደ ቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ሁሉ እኛም ውሳኔያችንን ዳር ማድረስ ያስቸግረን ይሆናል። ለምን? ፍጹማን ባለመሆናችን ዛሬ ነገ የማለት ልማድ ይኖረን ይሆናል። አሊያም ደግሞ ያልተጠበቁ ክስተቶች ውሳኔያችንን በተግባር ማዋል አዳጋች እንዲሆንብን ሊያደርጉ ይችላሉ። (መክ. 9:11፤ ሮም 7:18) ታዲያ ውሳኔያችንን መገምገምና ማስተካከያ ማድረግ ያስፈልገን እንደሆነ ማወቅ የምንችለው እንዴት ነው? የጀመርነውን በመጨረስ ረገድ ይበልጥ ውጤታማ መሆን የምንችለውስ እንዴት ነው?

ውሳኔ ከማድረግህ በፊት

6. ውሳኔያችንን ማስተካከል የሚያስፈልገን ለምን ሊሆን ይችላል?

6 ትልቅ ቦታ የሚሰጣቸው አንዳንድ ውሳኔዎችን ፈጽሞ መቀየር አንችልም። ለምሳሌ ያህል፣ ይሖዋን ለማገልገል ባደረግነው ውሳኔ እስከ መጨረሻው መጽናት ይኖርብናል፤ ለትዳር ጓደኛችን ታማኝ ለመሆን የገባነውን ቃልም መጠበቅ አለብን። (ማቴ. 16:24፤ 19:6) ሌሎች ውሳኔዎቻችንን ግን ማስተካከል ያስፈልገን ይሆናል። ለምን? ሁኔታዎች ስለሚለዋወጡ ነው። ታዲያ ከሁሉ የተሻለ ውሳኔ ለማድረግ የሚረዱን አንዳንድ እርምጃዎች የትኞቹ ናቸው?

7. ምን ለማግኘት መጸለይ ይኖርብናል? ለምንስ?

7 ጥበብ ለማግኘት ጸልይ። ያዕቆብ በይሖዋ መንፈስ መሪነት እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “ከእናንተ መካከል ጥበብ የጎደለው ሰው ካለ አምላክን ያለማሰለስ ይለምን፤ አምላክ . . . ለሁሉም በልግስና ይሰጣልና።” (ያዕ. 1:5) ሁኔታው ይለያይ እንጂ ሁላችንም ‘ጥበብ የሚጎድለን’ ጊዜ አለ። በመሆኑም ውሳኔ ስታደርግም ሆነ ያደረግከውን ውሳኔ ስትገመግም የይሖዋን እርዳታ ለማግኘት ሞክር። ይሖዋም ጥበብ የተንጸባረቀባቸው ውሳኔዎች እንድታደርግ ይረዳሃል።

8. ውሳኔ ላይ ከመድረሳችን በፊት ምን ማድረግ ይኖርብናል?

8 የተሟላ መረጃ ለማግኘት ጥረት አድርግ። የአምላክ ቃል ስለ ጉዳዩ የሚሰጠውን ምክር ተመልከት፤ የይሖዋ ድርጅት ያዘጋጃቸውን ጽሑፎች አንብብ፤ እንዲሁም እምነት የምትጥልባቸውን ሰዎች አማክር። (ምሳሌ 20:18) በዚህ መንገድ መረጃ ለማግኘት ጥረት ማድረግህ ሥራ ከመቀየር፣ ወደ ሌላ አካባቢ ከመዛወር ወይም ራስህን እያስተዳደርክ ይሖዋን ማገልገል እንድትችል ምን ዓይነት ትምህርት መምረጥ እንዳለብህ ከመወሰን ጋር በተያያዘ ጥሩ ውሳኔ ለማድረግ ይረዳሃል።

9. አንድን ውሳኔ ለማድረግ የተነሳሳንበትን ትክክለኛ ዓላማ በሐቀኝነት መመርመር ያለብን ለምንድን ነው?

9 የተነሳሳህበትን ዓላማ ገምግም። ይሖዋ አንድን ነገር ለማድረግ ለተነሳሳንበት ዓላማ ትኩረት ይሰጣል። (ምሳሌ 16:2) በሁሉም ነገር ሐቀኞች እንድንሆን ይፈልጋል። ስለዚህ አንድን ውሳኔ ለማድረግ የተነሳሳንበትን ትክክለኛ ዓላማ በሐቀኝነት መመርመር ይኖርብናል። እንዲህ ካላደረግን በውሳኔያችን መጽናት ሊከብደን ይችላል። አንድ ምሳሌ እንመልከት፦ አንድ ወጣት ወንድም የዘወትር አቅኚ ለመሆን ወሰነ። ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ግን የሰዓት ግቡ ላይ መድረስ የከበደው ከመሆኑም ሌላ ከአገልግሎቱ የሚያገኘው ደስታም እየቀነሰ ሄደ። ይህ ወንድም አቅኚ ለመሆን ያነሳሳው ዋነኛ ምክንያት ይሖዋን ለማስደሰት ያለው ፍላጎት እንደሆነ ተሰምቶት ሊሆን ይችላል። ሆኖም ዋነኛ ምክንያቱ ወላጆቹን ወይም አንድ የሚያደንቀውን ሰው ለማስደሰት ያለው ፍላጎት ይሆን?

10. ለውጥ ለማድረግ ምን ይረዳናል?

10 ሲጋራ ማጨሱን ለማቆም የወሰነን አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትም እናስብ። ለአንድ ወይም ለሁለት ሳምንት ያህል እንደምንም ታግሎ ሱሱን መቆጣጠር ቢችልም በኋላ ላይ አገረሸበት። ውሎ አድሮ ግን ይህን ልማዱን በማሸነፍ ረገድ ተሳካለት! ለይሖዋ ያለው ፍቅርና እሱን ለማስደሰት ያለው ፍላጎት ይህን ልማዱን ለማሸነፍ ረድቶታል።—ቆላ. 1:10፤ 3:23

11. በግልጽ የተቀመጠ ግብ ሊኖርህ የሚገባው ለምንድን ነው?

11 በግልጽ የተቀመጠ ግብ ይኑርህ። ግልጽ የሆነ ግብ ካወጣህ የጀመርከውን ዳር ማድረስ ይበልጥ ቀላል ይሆንልሃል። ለምሳሌ ያህል፣ መጽሐፍ ቅዱስን አዘውትረህ ለማንበብ ወስነህ ይሆናል። ይህን ለማድረግ የሚያስችል ፕሮግራም ካላወጣህ ግን ዓላማህን ዳር ማድረስ ላይሳካልህ ይችላል። * በሌላ በኩል ደግሞ የአንድ ጉባኤ ሽማግሌዎች ለመንጋው ይበልጥ እረኝነት ለማድረግ ወስነው ይሆናል፤ ይሁንና የተወሰነ ጊዜ ቢያልፍም ውሳኔያቸውን ተግባራዊ አላደረጉም። ያሰቡት እንዲሳካላቸው በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ማሰባቸው ጠቃሚ ነው፦ “እረኝነት ይበልጥ የሚያስፈልጋቸው ወንድሞችና እህቶች እነማን እንደሆኑ ተወያይተናል? እነዚህን ወንድሞች የምንጎበኝበትን ጊዜ መድበናል?”

12. ምን ማድረግ ሊያስፈልገን ይችላል? ለምንስ?

12 ምክንያታዊ ሁን። ማናችንም ብንሆን ያሰብነውን ሁሉ ለማሳካት የሚያስችል ጊዜ፣ ንብረት ወይም ጉልበት የለንም። ስለዚህ እውነታውን ከግምት ለማስገባት እንዲሁም ምክንያታዊ ለመሆን ጥረት አድርግ። ያደረግከውን ውሳኔ ዳር ማድረስ ከአቅምህ በላይ ከሆነብህ በውሳኔህ ላይ ማስተካከያ ማድረግ ሊያስፈልግህ ይችላል። (መክ. 3:6) በሌላ በኩል ደግሞ ውሳኔህን ከገመገምክና አስፈላጊውን ማስተካከያ ካደረግህ በኋላ ያሰብከውን ነገር በተግባር ለማዋል ዝግጁ እንደሆንክ ይሰማህ ይሆናል። ሁኔታህ እንዲህ ከሆነ የጀመርከውን ለመጨረስ የሚረዱህን አምስት እርምጃዎች ተመልከት።

ውሳኔህን ተግባራዊ ለማድረግ የሚረዱ እርምጃዎች

13. ውሳኔህን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ብርታት ማግኘት የምትችለው እንዴት ነው?

13 ውሳኔህን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ብርታት ለማግኘት ጸልይ። አምላክ ውሳኔህን ዳር ለማድረስ የሚያስፈልግህን “ኃይል” ሊሰጥህ ይችላል። (ፊልጵ. 2:13) እንግዲያው ይሖዋ በቅዱስ መንፈሱ አማካኝነት የሚያስፈልግህን ኃይል እንዲሰጥህ ለምነው። ጸሎትህ ወዲያው መልስ እንዳላገኘ ቢሰማህም እንኳ መጸለይህን አታቋርጥ። ኢየሱስ እንዳለው ‘ደጋግመህ ከለመንክ’ መንፈስ ቅዱስ ‘ይሰጥሃል።’—ሉቃስ 11:9, 13

14. በምሳሌ 21:5 ላይ የሚገኘው መሠረታዊ ሥርዓት ውሳኔህን በተግባር ለማዋል የሚረዳህ እንዴት ነው?

14 ዕቅድ አውጣ። (ምሳሌ 21:5ን አንብብ።) ማንኛውንም ሥራ ዳር ለማድረስ ዕቅድ ማውጣት ያስፈልግሃል። ከዚያም በዕቅድህ መሠረት ሥራህን ማከናወን ይኖርብሃል። በተመሳሳይም አንድ ውሳኔ ስታደርግ፣ ውሳኔህን ዳር ለማድረስ ልትወስዳቸው ያሰብካቸውን እርምጃዎች በዝርዝር ጻፍ። በተጨማሪም ከበድ ያሉ ሥራዎችን ከፋፍለህ ማስቀመጥህ ምን ያህል ሥራ እንዳከናወንክ መከታተል ቀላል እንዲሆንልህ ያደርጋል። ጳውሎስ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖችን፣ እሱ እስኪመጣ ጠብቀው መዋጮ ከማሰባሰብ ይልቅ “በየሳምንቱ የመጀመሪያ ቀን” ለመዋጮ የሚሆን የተወሰነ ገንዘብ እንዲያስቀምጡ አበረታቷቸዋል። (1 ቆሮ. 16:2) ከበድ ያሉ ሥራዎችን ከፋፍለህ ማስቀመጥህ ሥራው ከአቅምህ በላይ እንደሆነ እንዳይሰማህም ያደርጋል።

15. ዕቅድ ካወጣህ በኋላ ምን ማድረግ ትችላለህ?

15 በጽሑፍ የሰፈረ ግልጽ የሆነ ዕቅድ ውሳኔህን በተግባር ማዋል እንድትችል ይረዳሃል። (1 ቆሮ. 14:40) ለምሳሌ የሽማግሌዎች አካላት በስብሰባቸው ላይ የሚያደርጉትን እያንዳንዱን ውሳኔ የሚመዘግብ አንድ ሽማግሌ እንዲመድቡ መመሪያ ተሰጥቷቸዋል፤ ይህ ሽማግሌ፣ አንድን ሥራ እንዲያከናውኑ የተመደቡትን ወንድሞችና ሥራው እንዲጠናቀቅ የታሰበበትን ቀንም በጽሑፍ ያሰፍራል። ይህን መመሪያ የሚከተሉ ሽማግሌዎች ውሳኔያቸውን ተግባራዊ ማድረግ ይበልጥ ቀላል ይሆንላቸዋል። (1 ቆሮ. 9:26) አንተም ከግል ጉዳዮችህ ጋር በተያያዘ ተመሳሳይ አካሄድ መከተል ትችላለህ። ለምሳሌ ያህል፣ በየዕለቱ ልታከናውናቸው ያሰብካቸውን ሥራዎች የያዘ ፕሮግራም ማዘጋጀትና እነዚህን ሥራዎች ለማከናወን ባሰብክበት ቅደም ተከተል መሠረት ማስፈር ትችላለህ። እንዲህ ማድረግህ የጀመርከውን ለመጨረስ ብቻ ሳይሆን በአጭር ጊዜ ውስጥ ብዙ ነገር ለማከናወንም ያስችልሃል።

16. ውሳኔህን ተግባራዊ ማድረግ ምን ይጠይቃል? ሮም 12:11 ይህን ሐሳብ የሚደግፈውስ እንዴት ነው?

16 ተግተህ ሥራ። ዕቅድህን ተግባራዊ ማድረግና የጀመርከውን ዳር ማድረስ ጥረት ይጠይቃል። (ሮም 12:11ን አንብብ።) ጳውሎስ፣ የማስተማር ችሎታውን ለማሻሻል ‘የተቻለውን ሁሉ ጥረት እንዲያደርግ’ እንዲሁም በሚያደርገው ጥረት ‘እንዲጸና’ ጢሞቴዎስን መክሮታል። ይህ ምክር ከሌሎች መንፈሳዊ ግቦች ጋር በተያያዘም ይሠራል።—1 ጢሞ. 4:13, 16

17. ውሳኔያችንን ተግባራዊ ከማድረግ ጋር በተያያዘ ኤፌሶን 5:15, 16 የሚጠቅመን እንዴት ነው?

17 ጊዜህን በጥበብ ተጠቀምበት። (ኤፌሶን 5:15, 16ን አንብብ።) ውሳኔህን ተግባራዊ የምታደርግበት ጊዜ መድብ፤ እንዲሁም የመደብከውን ጊዜ አክብረህ ሥራህን አከናውን። ውሳኔህን ተግባራዊ ለማድረግ፣ ሁሉ ነገር እስኪስተካከልልህ አትጠብቅ፤ እንዲህ ዓይነት ጊዜ ላታገኝ ትችላለህ። (መክ. 11:4) እምብዛም አስፈላጊ ያልሆኑ ነገሮች ጊዜህን እንዳይሻሙብህና ይበልጥ አስፈላጊ ለሆኑ ነገሮች የሚያስፈልግህን ጉልበት እንዳያሳጡህ ተጠንቀቅ። (ፊልጵ. 1:10) የሚቻል ከሆነ ሌሎች ነገሮች ትኩረትህን የማይከፋፍሉበትን ጊዜ ምረጥ። የምትሠራው ነገር እንዳለህና እንዳይረብሹህ ለሌሎች ተናገር። አስፈላጊ ከሆነም ስልክህን አጥፋ እንዲሁም በኢ-ሜይል ወይም በማኅበራዊ ድረ ገጽ የሚላኩልህን መልእክቶች ሌላ ጊዜ ተመልከት። *

18-19. ጥሩ ውሳኔ ካደረግህ በኋላ እንቅፋት ቢያጋጥምህ ተስፋ እንዳትቆርጥ ምን ሊረዳህ ይችላል?

18 በምታገኘው ውጤት ላይ ትኩረት አድርግ። ውሳኔህ የሚያስገኘው ውጤት፣ ጉዞ አድርገህ አንድ ቦታ ከመድረስ ጋር ሊመሳሰል ይችላል። ያሰብከው ቦታ ለመድረስ ከልብህ የምትፈልግ ከሆነ መንገዱ ቢዘጋና ሌላ መንገድ መጠቀም ቢያስፈልግህ እንኳ ጉዞህን አታቋርጥም። በተመሳሳይም ውሳኔያችን በሚያስገኘው ውጤት ላይ ትኩረት የምናደርግ ከሆነ እንቅፋት የሚሆኑ ነገሮች ቢያጋጥሙን እንኳ ቶሎ ተስፋ አንቆርጥም።—ገላ. 6:9

19 ጥሩ ውሳኔ ማድረግ ከባድ ነው፤ ውሳኔውን ተግባራዊ ማድረግም ቢሆን ተፈታታኝ ሊሆን ይችላል። ያም ቢሆን በይሖዋ እርዳታ፣ የጀመርከውን ዳር ለማድረስ የሚያስፈልገውን ጥበብና ብርታት ማግኘት ትችላለህ።

መዝሙር 65 ወደፊት ግፋ!

^ አን.5 በሕይወትህ ውስጥ የምትቆጭባቸው ውሳኔዎች አሉ? በሌላ በኩል ደግሞ ጥሩ ውሳኔ ለማድረግም ሆነ ውሳኔህን በተግባር ለማዋል የምትቸገርበት ጊዜ አለ? ይህ ርዕስ እነዚህን ተፈታታኝ ሁኔታዎች መወጣትና የጀመርከውን ዳር ማድረስ እንድትችል ይረዳሃል።

^ አን.17 ጊዜን በአግባቡ ከመጠቀም ጋር በተያያዘ ተጨማሪ ሐሳቦች ለማግኘት በሚያዝያ 2010 ንቁ! ላይ የወጣውን “ተጨማሪ ጊዜ ለማግኘት የሚረዱ 20 መንገዶች” የሚለውን ርዕስ ተመልከት።