በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የጥናት ርዕስ 41

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶቻችን እድገት አድርገው እንዲጠመቁ መርዳት—ክፍል አንድ

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶቻችን እድገት አድርገው እንዲጠመቁ መርዳት—ክፍል አንድ

“አገልጋዮች በሆንነው በእኛ አማካኝነት የተጻፋችሁ የክርስቶስ ደብዳቤ እንደሆናችሁ በግልጽ ታይቷል።”—2 ቆሮ. 3:3

መዝሙር 78 ‘የአምላክን ቃል ማስተማር’

ማስተዋወቂያ *

አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እድገት አድርጎ ሲጠመቅ መላው ጉባኤ በእጅጉ ይደሰታል (አንቀጽ 1⁠ን ተመልከት)

1. በ2 ቆሮንቶስ 3:1-3 መሠረት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶች ሲጠመቁ ምን ይሰማናል? (ሽፋኑን ተመልከት።)

በጉባኤህ ክልል ውስጥ ያለ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ሲጠመቅ ስታይ ምን ይሰማሃል? በጣም እንደምትደሰት ጥያቄ የለውም። (ማቴ. 28:19) ግለሰቡን * ያስጠናኸው አንተ ከነበርክ ደግሞ ሲጠመቅ ማየትህ ይበልጥ እንደሚያስደስትህ የታወቀ ነው! (1 ተሰ. 2:19, 20) አዲስ ተጠማቂዎች፣ ላስጠኗቸው ክርስቲያኖች ብቻ ሳይሆን ለመላው ጉባኤ ግሩም “የምሥክር ወረቀት” ናቸው።2 ቆሮንቶስ 3:1-3ን አንብብ።

2. (ሀ) የትኛውን አስፈላጊ ጥያቄ መመርመር ያስፈልገናል? ለምንስ? (ለ) የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ምንድን ነው? (የግርጌ ማስታወሻውን ተመልከት።)

2 ባለፉት አራት ዓመታት ውስጥ በዓለም ዙሪያ በየወሩ በአማካይ 10,000,000 ገደማ የሚሆኑ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶች * እንደተመሩ ሪፖርት ተደርጓል፤ ይህም በጣም የሚያስደስት ነው። በእነዚሁ ዓመታት ውስጥ በየዓመቱ በአማካይ ከ280,000 የሚበልጡ ሰዎች ተጠምቀው የይሖዋ ምሥክሮችና የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ሆነዋል። ታዲያ በሚሊዮኖች ከሚቆጠሩት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶች መካከል ተጨማሪ ሰዎች እንዲጠመቁ መርዳት የምንችለው እንዴት ነው? ይሖዋ ታጋሽ በመሆን፣ ሰዎች የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት መሆን የሚችሉበት ጊዜና አጋጣሚ ሰጥቷል፤ ይህ ጊዜ እስካለ ድረስ እነዚህ ሰዎች ፈጣን እድገት አድርገው እንዲጠመቁ ለመርዳት አቅማችን የሚፈቅደውን ሁሉ ማድረግ እንፈልጋለን። የቀረው ጊዜ በጣም አጭር ነው!—1 ቆሮ. 7:29ሀ፤ 1 ጴጥ. 4:7

3. የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መምራትን በተመለከተ በዚህ ርዕስ ላይ ምን እንመለከታለን?

3 ደቀ መዛሙርት የማድረጉ ሥራ አጣዳፊ ከመሆኑ አንጻር ተጨማሪ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶች እድገት አድርገው እንዲጠመቁ እንዴት መርዳት እንደምንችል ለማወቅ በተለያዩ ቅርንጫፍ ቢሮዎች ጥናት ተደርጎ ነበር። ተሞክሮ ካላቸው አቅኚዎች፣ ሚስዮናውያንና የወረዳ የበላይ ተመልካቾች የምናገኘውን ትምህርት በዚህና በሚቀጥለው ርዕስ ላይ እንመለከታለን። * (ምሳሌ 11:14፤ 15:22) እነዚህ ክርስቲያኖች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ውይይቱ ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን የመጽሐፍ ቅዱስ አስተማሪዎቹም ሆነ ጥናቶቻቸው ማድረግ ስለሚችሉት ነገር ሐሳብ ሰጥተዋል። በዚህ ርዕስ ላይ እያንዳንዱ ጥናት እድገት አድርጎ ለመጠመቅ የትኞቹን አምስት ነገሮች ማድረግ እንዳለበት እንመለከታለን።

በየሳምንቱ አጥኑ

የመጽሐፍ ቅዱስ ውይይታችሁን ቁጭ ብላችሁ ማድረግ ትችሉ እንደሆነ ጥናታችሁን ጠይቁት (ከአንቀጽ 4-6⁠ን ተመልከት)

4. ጥናት ስንመራ ከሰዎች ጋር አጭር ውይይት ማድረግን በተመለከተ ልንገነዘበው የሚገባው ነገር ምንድን ነው?

4 አንዳንድ ወንድሞችና እህቶች የቤቱ ባለቤት በር ላይ ሆነው አጠር ያለ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ይመራሉ። እንዲህ ማድረግ መጀመሪያ አካባቢ ግለሰቡ ለመጽሐፍ ቅዱስ ፍላጎት እንዲያድርበት ሊረዳ ይችላል፤ ሆኖም እንዲህ ያሉት ውይይቶች ብዙውን ጊዜ አጭር ከመሆናቸውም ሌላ በየሳምንቱ በቋሚነት ላይደረጉ ይችላሉ። አንዳንድ ክርስቲያኖች የግለሰቡን ፍላጎት ለማሳደግ ሲሉ የስልክ ቁጥሩን ይጠይቁታል፤ ከዚያም ከቀጠሯቸው በፊት በመሃል ደውለው ወይም የጽሑፍ መልእክት ልከው አጠር ያለ ቅዱስ ጽሑፋዊ ሐሳብ ያካፍሉታል። ውጤታማ የሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ሳይጀመር በዚህ መልኩ ለወራት መወያየታቸውን ይቀጥሉ ይሆናል። ይሁን እንጂ ግለሰቡ የአምላክን ቃል ለማጥናት የሚያውለው ጊዜ ይህ ብቻ ከሆነ እድገት አድርጎ ራሱን መወሰንና ለጥምቀት መብቃት ይችላል? ይህን የማድረግ አጋጣሚው ጠባብ ነው።

5. በሉቃስ 14:27-33 ላይ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በማድረጉ ሥራችን ሊረዳን የሚችል ምን ሐሳብ ጎላ አድርጎ ገልጿል?

5 በአንድ ወቅት ኢየሱስ፣ የእሱ ደቀ መዝሙር መሆን ምን እንደሚጠይቅ በምሳሌ አስረድቶ ነበር። ግንብ ለመገንባት ስለፈለገ ሰው እንዲሁም ወደ ጦርነት ለመዝመት ስላሰበ ንጉሥ ተናግሮ ነበር። ግንብ ለመገንባት የፈለገው ሰው ግንባታውን መጨረስ ይችል እንደሆነ ‘በመጀመሪያ ተቀምጦ ወጪውን ማስላት’ እንዳለበት ኢየሱስ ተናገረ፤ ንጉሡም ቢሆን ሠራዊቱ ድል ማድረግ ይችል እንደሆነ ለማወቅ ‘በቅድሚያ ተቀምጦ መማከር’ እንዳለበት ኢየሱስ ገልጿል። (ሉቃስ 14:27-33ን አንብብ።) በተመሳሳይም የኢየሱስ ደቀ መዝሙር መሆን የሚፈልግ ሰው ሁሉ፣ ይህ ውሳኔ ምን እንደሚጠይቅበት በጥንቃቄ መመርመር አለበት። ጥናታችን፣ ደቀ መዝሙር መሆን ምን እንደሚጠይቅ መገንዘብ እንዲችል በየሳምንቱ አብሮን እንዲያጠና ልናበረታታው ይገባል። ይህን ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?

6. የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶቻችን እድገት እንዲያደርጉ ለመርዳት ምን ማድረግ እንችላለን?

6 በመጀመሪያ፣ በር ላይ ቆማችሁ የምታደርጉትን አጭር ውይይት ረዘም ማድረግ ትችሉ ይሆናል። ምናልባትም በተገናኛችሁ ቁጥር ተጨማሪ ጥቅስ አንብባችሁ መወያየት ትችሉ ይሆናል። ግለሰቡ ረዘም ያለ ውይይት ማድረግን እየለመደ ሲመጣ፣ ቁጭ ብላችሁ መወያየት ትችሉ እንደሆነ ጠይቁት። ግለሰቡ የሚሰጠው ምላሽ ለመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቱ ያለውን አመለካከት ለማወቅ ያስችላችኋል። ውሎ አድሮ ደግሞ ይበልጥ እድገት እንዲያደርግ ለመርዳት በሳምንት ሁለት ጊዜ ማጥናት ይችል እንደሆነ መጠየቅ ሊያስፈልጋችሁ ይችላል። ይሁንና በሳምንት አንድ ወይም ሁለት ጊዜ ከማጥናት ባለፈ የሚያስፈልግ ነገር አለ።

ለእያንዳንዱ የጥናት ክፍለ ጊዜ ተዘጋጁ

ለመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቱ በደንብ ተዘጋጁ፤ ለጥናታችሁም እንዴት መዘጋጀት እንደሚችል አሳዩት (ከአንቀጽ 7-9⁠ን ተመልከት)

7. አስጠኚው ለእያንዳንዱ የጥናት ክፍለ ጊዜ በደንብ መዘጋጀት የሚችለው እንዴት ነው?

7 የመጽሐፍ ቅዱስ አስጠኚው ለእያንዳንዱ የጥናት ክፍለ ጊዜ በሚገባ መዘጋጀት ይኖርበታል። ለጥናትህ ስትዘጋጅ መጀመሪያ ትምህርቱን ማንበብና ጥቅሶቹን አውጥተህ መመልከትህ አስፈላጊ ነው። ዋና ዋናዎቹን ነጥቦች ለመረዳት ጥረት አድርግ። ስለ ትምህርቱ ርዕስ፣ ስለ ንዑሳን ርዕሶቹ፣ ስለ አንቀጾቹ ጥያቄዎች፣ “አንብብ” ስለሚሉት ጥቅሶች፣ ስለ ሥዕሎቹ እንዲሁም ትምህርቱን ለማብራራት ስለሚረዱ ቪዲዮዎች አስብ። ከዚያም ጥናትህን በአእምሮህ ይዘህ ትምህርቱን ቀላል እና ግልጽ በሆነ መንገድ ማቅረብ የምትችለው እንዴት እንደሆነ አሰላስል፤ ጥናትህ ትምህርቱን መረዳትና ተግባራዊ ማድረግ የሚችለው እንዲህ ካደረግህ ነው።—ነህ. 8:8፤ ምሳሌ 15:28ሀ

8. በቆላስይስ 1:9, 10 ላይ ጳውሎስ የተናገረው ሐሳብ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶቻችን መጸለይን በተመለከተ ምን ያስተምረናል?

8 ለጥናቱ ስትዘጋጅ ስለ ተማሪውና ስለሚያስፈልጉት ነገሮች ወደ ይሖዋ ጸልይ። የሰውየውን ልብ በሚነካ መንገድ ከመጽሐፍ ቅዱስ ለማስተማር እንዲረዳህ ይሖዋን ጠይቀው። (ቆላስይስ 1:9, 10ን አንብብ።) ጥናትህ ለመረዳት ወይም ለመቀበል ሊከብደው የሚችለውን ነገር አስቀድመህ ለማሰብ ሞክር። ዋነኛ ዓላማህ ጥናትህ እድገት አድርጎ እንዲጠመቅ መርዳት እንደሆነ ምንጊዜም አስታውስ።

9. አስተማሪው ተማሪውን ለጥናቱ እንዲዘጋጅ ሊረዳው የሚችለው እንዴት ነው? አብራራ።

9 የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቱ በቋሚነት ከተካሄደ ተማሪው ይሖዋና ኢየሱስ ላደረጉት ነገር አድናቆት እንደሚያድርበትና ተጨማሪ እውቀት ለመቅሰም እንደሚነሳሳ እንጠብቃለን። (ማቴ. 5:3, 6) ተማሪው ከጥናቱ ሙሉ ጥቅም እንዲያገኝ ከተፈለገ ለሚማረው ነገር ሙሉ ትኩረት ሊሰጥ ይገባል። ለዚህም ሲባል ለእያንዳንዱ የጥናት ክፍለ ጊዜ መዘጋጀቱ ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ ጎላ አድርገህ ግለጽለት፤ ለጥናቱ ሲዘጋጅ፣ አስቀድሞ ትምህርቱን ማንበቡና የተማረውን እንዴት ተግባራዊ ማድረግ እንደሚችል ማሰላሰሉ ጠቃሚ መሆኑን አስረዳው። አስተማሪው በዚህ ረገድ ሊረዳው የሚችለው እንዴት ነው? ዝግጅት ማድረግ የሚቻለው እንዴት እንደሆነ ለማሳየት አንዱን ትምህርት አብረኸው ተዘጋጅ። * ለአንቀጾቹ ጥያቄዎች ቀጥተኛ መልስ ማግኘት የሚችለው እንዴት እንደሆነ አብራራለት፤ ከዚያም ቁልፍ በሆኑ ቃላት ወይም ሐረጎች ላይ ብቻ ምልክት ማድረጉ መልሱን ለማስታወስ እንዴት እንደሚረዳው አሳየው። በራሱ አባባል መልስ እንዲሰጥ አበረታታው። ይህን ማድረጉ ትምህርቱ ምን ያህል እንደገባው ለማወቅ ያስችልሃል። ሆኖም ተማሪው ሊያደርገው የሚገባ ሌላም ነገር አለ።

በየዕለቱ ከይሖዋ ጋር እንዲነጋገር አስተምሩት

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናታችሁን ከይሖዋ ጋር መነጋገር የሚችለው እንዴት እንደሆነ አስተምሩት (ከአንቀጽ 10-11⁠ን ተመልከት)

10. መጽሐፍ ቅዱስን በየዕለቱ ማንበብ አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? ከመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ይበልጥ ጥቅም ለማግኘት ምን ማድረግ ያስፈልጋል?

10 ተማሪው በየሳምንቱ ከአስተማሪው ጋር ከሚያደርገው ጥናት በተጨማሪ በየዕለቱ በግሉ አንዳንድ ነገሮችን ቢያደርግ ይጠቀማል። ከይሖዋ ጋር መነጋገር ያስፈልገዋል። ይህን ማድረግ የሚችለው እንዴት ነው? ይሖዋን በማዳመጥና በጸሎት ወደ እሱ በመቅረብ ነው። መጽሐፍ ቅዱስን በየዕለቱ በማንበብ አምላክን ማዳመጥ ይችላል። (ኢያሱ 1:8፤ መዝ. 1:1-3) jw.org ላይ የወጣውን “የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ፕሮግራም” እንዴት መጠቀም እንደሚችል አሳየው፤ ይህን ፕሮግራም አትሞ መጠቀም ይችላል። * እርግጥ ነው፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ ንባቡ ይበልጥ እንዲጠቀም ማሰላሰል ይኖርበታል፤ በመሆኑም የሚያነበው ነገር ስለ ይሖዋ ምን እንደሚያስተምረው እንዲሁም ትምህርቱን በሕይወቱ ተግባራዊ ማድረግ የሚችለው እንዴት እንደሆነ ቆም ብሎ እንዲያስብ አበረታታው።—ሥራ 17:11፤ ያዕ. 1:25

11. ጥናትህ በተገቢው መንገድ መጸለይን የሚማረው እንዴት ነው? አዘውትሮ ወደ ይሖዋ መጸለዩ አስፈላጊ የሆነውስ ለምንድን ነው?

11 በየዕለቱ በጸሎት ይሖዋን እንዲያነጋግረው ጥናትህን አበረታታው። ጥናታችሁን ከመጀመራችሁ በፊት እንዲሁም ስትደመድሙ ወደ ይሖዋ ልባዊ ጸሎት አቅርብ፤ በጸሎትህ ላይ ስለ ጥናትህ ጥቀስ። የምታቀርበውን ጸሎት ሲሰማ ከልቡ መጸለይ የሚችለው እንዴት እንደሆነ እንዲሁም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ወደ ይሖዋ አምላክ መጸለይ እንዳለበት ይማራል። (ማቴ. 6:9፤ ዮሐ. 15:16) በየዕለቱ መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ (ይሖዋን ማዳመጥ) እና መጸለይ (ይሖዋን ማነጋገር) ጥናትህ ወደ ይሖዋ አምላክ ይበልጥ እንዲቀርብ እንደሚረዳው ጥያቄ የለውም! (ያዕ. 4:8) ጥናትህ እነዚህን ልማዶች ማዳበሩ ራሱን ለመወሰን እና ለጥምቀት እንዲበቃ ይረዳዋል። ጥናትህ ሌላስ ምን ማድረግ ይኖርበታል?

ከይሖዋ ጋር ወዳጅነት እንዲመሠርት እርዱት

12. አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ አስተማሪ ጥናቱን ከይሖዋ ጋር ወዳጅነት እንዲመሠርት ሊረዳው የሚችለው እንዴት ነው?

12 ተማሪው በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቱ ላይ የሚማረው ነገር የጭንቅላት እውቀት ከመሆን ባለፈ ልቡን ሊነካው ይገባል። ለምን? ምክንያቱም ለተግባር የሚያነሳሳን ልባችን ነው፤ ልባችን ምኞታችንን፣ ስሜታችንን እና ዝንባሌያችንን ያካትታል። ኢየሱስ የሰዎችን ግንዛቤ በሚያሰፋ መንገድ ያስተምር ነበር። ሰዎች እሱን የተከተሉት ግን ያስተማራቸው ነገር ልባቸውን ስለነካው ነው። (ሉቃስ 24:15, 27, 32) ጥናትህ ይሖዋ እውን እንዲሆንለት፣ ከእሱ ጋር ዝምድና መመሥረት እንደሚችል እንዲሰማው እንዲሁም እሱን አባቱ፣ አምላኩና ወዳጁ አድርጎ እንዲያየው ልትረዳው ይገባል። (መዝ. 25:4, 5) በምታጠኑበት ወቅት የአምላክ ባሕርያት ጎልተው እንዲወጡ አድርግ። (ዘፀ. 34:5, 6፤ 1 ጴጥ. 5:6, 7) የምትወያዩት በየትኛውም ርዕሰ ጉዳይ ላይ ቢሆን በይሖዋ ማንነት ላይ ትኩረት አድርግ። ተማሪው ስለ ይሖዋ ግሩም ባሕርያት እንዲያውቅ ይኸውም ፍቅሩን፣ ደግነቱን እና ርኅራኄውን እንዲገነዘብ እርዳው። ኢየሱስ ‘ከሁሉ የሚበልጠውና የመጀመሪያው ትእዛዝ ይሖዋን መውደድ’ እንደሆነ ተናግሯል። (ማቴ. 22:37, 38) እንግዲያው ጥናትህ ይሖዋን ከልቡ እንዲወደው ለመርዳት ጥረት አድርግ።

13. አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪ ስለ ይሖዋ ባሕርያት እንዲገነዘብ መርዳት የሚቻለው እንዴት እንደሆነ በምሳሌ አስረዳ።

13 ከጥናትህ ጋር ስትወያዩ ይሖዋን እንድትወደው ያደረገህን ነገር ግለጽለት። ይህም ጥናትህ አምላክን መውደድና ከእሱ ጋር በግለሰብ ደረጃ ወዳጅነት መመሥረት እንደሚያስፈልገው እንዲገነዘብ ያስችለዋል። (መዝ. 73:28) ለምሳሌ ያህል፣ በምታጠኑት ጽሑፍ ወይም በአንድ ጥቅስ ላይ ስለ ይሖዋ ፍቅር፣ ጥበብ፣ ፍትሕ ወይም ኃይል የሚገልጽ ልብህን የነካው ሐሳብ አለ? ከሆነ ይህንን ለጥናትህ ንገረው፤ በሰማይ ያለውን አባታችንን እንድትወደው ካደረጉህ በርካታ ምክንያቶች አንዱ ይህ እንደሆነ ግለጽለት። በእርግጥ፣ አንድ ጥናት እድገት አድርጎ ለመጠመቅ እንዲበቃ ሊወስደው የሚገባ ሌላም እርምጃ አለ።

በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ እንዲገኝ አበረታቱት

ጥናታችሁን በተቻለ መጠን ወዲያውኑ ስብሰባዎች ላይ መገኘት እንዲጀምር አበረታቱት! (ከአንቀጽ 14-15⁠ን ተመልከት)

14. አንድ ጥናት በስብሰባዎች ላይ መገኘቱ እድገት ለማድረግ እንደሚረዳው ዕብራውያን 10:24, 25 የሚጠቁመው እንዴት ነው?

14 ሁላችንም ጥናቶቻችን እድገት አድርገው እንዲጠመቁ እንፈልጋለን። እንዲህ እንዲያደርጉ መርዳት የምንችልበት አንዱ ወሳኝ መንገድ በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ እንዲገኙ ማበረታታት ነው። ተሞክሮ ያካበቱ አስተማሪዎች እንደገለጹት በስብሰባዎች ላይ ወዲያው መገኘት የጀመሩ ተማሪዎች ፈጣን እድገት ያደርጋሉ። (መዝ. 111:1) ተማሪዎቹ በጥናታቸው ወቅት የሚማሩትን ያህል በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ በመገኘትም ብዙ እውቀት እንደሚቀስሙ አንዳንድ አስተማሪዎች ለጥናቶቻቸው ይነግሯቸዋል። ከጥናትህ ጋር ዕብራውያን 10:24, 25ን አንብብ፤ ከዚያም በስብሰባዎች ላይ መገኘቱ ምን ጥቅም እንደሚያስገኝለት ከጥቅሱ ላይ አብራራለት። በስብሰባ አዳራሻችን ውስጥ ምን ይከናወናል? * የሚለውን ቪዲዮ አሳየው። ጥናትህ በስብሰባዎች ላይ በየሳምንቱ መገኘትን ልማድ እንዲያደርግ እርዳው።

15. አንድ ጥናት በስብሰባዎች ላይ አዘውትሮ እንዲገኝ ለማበረታታት ምን ማድረግ እንችላለን?

15 ጥናትህ በጉባኤ ስብሰባ ላይ ተገኝቶ የማያውቅ ወይም አዘውትሮ የማይገኝ ከሆነ ምን ማድረግ ትችላለህ? በስብሰባ ላይ የተማርከው ነገር ምን ያህል እንዳስደሰተህ ንገረው። ጉባኤ እንዲመጣ ከመጋበዝ የበለጠ ጥናትህን ስብሰባ ላይ እንዲገኝ ሊያነሳሳው የሚችለው እንዲህ ማድረግህ ነው። በስብሰባ ላይ የሚጠናውን መጠበቂያ ግንብ ወይም የክርስቲያናዊ ሕይወትና አገልግሎት ስብሰባ አስተዋጽኦ ስጠው። በቀጣዩ ስብሰባ ላይ የሚጠናውን ክፍል አሳየው፤ የእሱን ትኩረት የሚስበው የትኛው ክፍል እንደሆነ ጠይቀው። ጥናትህ ለመጀመሪያ ጊዜ ስብሰባ ላይ ሲገኝ የሚመለከተው ነገር እስከ ዛሬ ከተገኘባቸው ሃይማኖታዊ ስብሰባዎች ሁሉ እጅግ የላቀ እንደሚሆን ጥርጥር የለውም። (1 ቆሮ. 14:24, 25) ጥሩ ምሳሌ ሊሆኑትና እድገት አድርጎ እንዲጠመቅ ሊረዱት ከሚችሉ ሰዎች ጋር የመተዋወቅ አጋጣሚ ያገኛል።

16. የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶቻችን እድገት አድርገው እንዲጠመቁ ለመርዳት ምን ማድረግ ያስፈልጋል? በቀጣዩ ርዕስ ላይ ምን እንመለከታለን?

16 የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶቻችንን እድገት አድርገው እንዲጠመቁ ልንረዳቸው የምንችለው እንዴት ነው? ጥናቶቻችንን በየሳምንቱ እንዲያጠኑና ለእያንዳንዱ የጥናት ክፍለ ጊዜ እንዲዘጋጁ እናበረታታቸው፤ በዚህ መንገድ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቱን በቁም ነገር እንዲመለከቱት መርዳት እንችላለን። በየዕለቱ ከይሖዋ ጋር እንዲነጋገሩና ከእሱ ጋር በግለሰብ ደረጃ ወዳጅነት እንዲመሠርቱ እናበረታታቸው። በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ የመገኘት ፍላጎት እንዲያድርባቸው እንርዳቸው። (“ ተማሪዎች እድገት አድርገው ለመጠመቅ ሊወስዷቸው የሚገቡ እርምጃዎች” የሚለውን ሣጥን ተመልከት።) በቀጣዩ ርዕስ ላይ ደግሞ የመጽሐፍ ቅዱስ አስተማሪዎች ጥናቶቻቸው እንዲጠመቁ ለመርዳት ሊያደርጓቸው የሚገቡ አምስት ተጨማሪ ነገሮችን እንመለከታለን።

መዝሙር 76 ምን ይሰማሃል?

^ አን.5 ማስተማር ሲባል “የአንድ ሰው አስተሳሰብ፣ ስሜት ወይም ተግባር አዲስ ወይም ከቀድሞው የተለየ እንዲሆን መርዳት” ማለት ነው። በማቴዎስ 28:19 ላይ የተመሠረተው የ2020 የዓመት ጥቅስ፣ ሰዎችን መጽሐፍ ቅዱስ ማስጠናት እንዲሁም ተጠምቀው የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርት እንዲሆኑ ማስተማር ያለውን አስፈላጊነት ያስታውሰናል። በዚህ በጣም አስፈላጊ ሥራ ስንካፈል ችሎታችንን ማሻሻል የምንችለው እንዴት እንደሆነ በዚህና በቀጣዩ ርዕስ ላይ እንመለከታለን።

^ አን.1 ስለ ተማሪው ስንገልጽ በተባዕታይ ፆታ ብንጠቀምም ሐሳቡ ለሴት ጥናቶችም ይሠራል።

^ አን.2 ተጨማሪ ማብራሪያ፦ ከአንድ ሰው ጋር አዘውትረህ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ በመወያየት መሠረታዊ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶችን እያስተማርከው ከሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እየመራህ ነው። ግለሰቡን እንዴት እንደምታስጠናው ካሳየኸው በኋላ ሁለት ጊዜ ካጠናችሁ እንዲሁም ጥናቱ እንደሚቀጥል ከተሰማህ፣ ጥናት ብለህ ሪፖርት ልታደርገው ትችላለህ።

^ አን.3 እነዚህ ርዕሶች ከሐምሌ 2004 እስከ ግንቦት 2005 ባሉት የመንግሥት አገልግሎታችን እትሞች ላይ “የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶቻችን እድገት እንዲያደርጉ መርዳት” በሚለው ዓምድ ሥር ከወጡ ተከታታይ ርዕሶች ላይ የተወሰዱ አንዳንድ ሐሳቦችንም ይዘዋል።

^ አን.9 ጥናቶቻችን እንዴት መዘጋጀት እንደሚችሉ ማሳየት የሚለውን የአራት ደቂቃ ቪዲዮ ተመልከት። JW Library® ላይ ሚዲያ > ስብሰባዎቻችን እና አገልግሎታችን > ክህሎታችንን ማሻሻል በሚለው ሥር ይገኛል።

^ አን.10 የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች > የመጽሐፍ ቅዱስ ማጥኛ መሣሪያዎች በሚለው ሥር ይገኛል።

^ አን.14 JW Library® ላይ ሚዲያ > ስብሰባዎቻችን እና አገልግሎታችን > ለአገልግሎት የምንጠቀምባቸው መሣሪያዎች በሚለው ሥር ይገኛል።