በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከይሖዋ ጋር ያለህን ወዳጅነት አድስ

ከይሖዋ ጋር ያለህን ወዳጅነት አድስ

በየዓመቱ፣ ተወግደው የነበሩ በርካታ ውድ የይሖዋ በጎች ወደ ክርስቲያን ጉባኤ ይመለሳሉ። እያንዳንዱ ክርስቲያን ሲመለስ ‘በሰማይ ምን ያህል ታላቅ ደስታ’ እንደሚሆን መገመት እንችላለን! (ሉቃስ 15:7, 10) አንተም ወደ ክርስቲያን ጉባኤ ተመልሰህ ከሆነ ኢየሱስ፣ መላእክት እና ይሖዋ እንደገና ከእውነት ጎን ለመቆም በመወሰንህ በጣም እንደተደሰቱ አትጠራጠር። ይሁንና ከይሖዋ ጋር ያለህን ወዳጅነት ለማደስ ጥረት ስታደርግ ተፈታታኝ ሁኔታዎች ያጋጥሙህ ይሆናል። ከእነዚህ አንዳንዶቹ የትኞቹ ናቸው? እነዚህን ለመወጣትስ ምን ሊረዳህ ይችላል?

ምን ተፈታታኝ ሁኔታዎች ያጋጥሙሃል?

ብዙዎች ወደ ክርስቲያን ጉባኤ ከተመለሱ በኋላ ከአሉታዊ ስሜቶች ጋር ይታገላሉ። ምናልባት አንተም እንደ ንጉሥ ዳዊት ይሰማህ ይሆናል። ዳዊት ኃጢአቱ ይቅር ከተባለለት በኋላም እንኳ ‘የፈጸምኳቸው ስህተቶች ዋጡኝ’ በማለት ተናግሯል። (መዝ. 40:12፤ 65:3) አንድ ክርስቲያን ወደ ይሖዋ ከተመለሰም በኋላ የጥፋተኝነት ወይም የኀፍረት ስሜት ለበርካታ ዓመታት ሊያሠቃየው ይችላል። ከ20 ዓመት በላይ ተወግዳ የቆየችው ኢዛቤል “‘ይሖዋ ይቅር ሊለኝ ይችላል’ ብዬ ማሰብ በጣም ከብዶኝ ነበር” ብላለች። * አንተም ተስፋ ከቆረጥክ እንደገና በመንፈሳዊ ልትደክም ትችላለህ። (ምሳሌ 24:10) እንዲህ ዓይነት ሁኔታ እንዳያጋጥምህ ጥረት አድርግ።

ሌሎች ደግሞ ከይሖዋ ጋር ያላቸውን ወዳጅነት ማደስ በጣም ብዙ ሥራ እንደሚጠይቅ ይሰማቸዋል። አንትዋን ውገዳው ከተነሳለት በኋላ “የክርስትና ሕይወት ጨርሶ እንደጠፋብኝ ተሰምቶኝ ነበር” ብሏል። እንዲህ ያሉት ስሜቶች አንዳንዶች በመንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ሙሉ ተሳትፎ እንዳያደርጉ እንቅፋት ሊሆኑባቸው ይችላሉ።

ነጥቡን በምሳሌ ለማስረዳት፣ አንድ ሰው ኃይለኛ አውሎ ነፋስ በቤቱ ላይ ከባድ ጉዳት አደረሰበት እንበል። ይህ ሰው ቤቱን ማደስ ምን ያህል ጊዜና ጥረት እንደሚጠይቅበት ሲያስብ ሥራው ከአቅሙ በላይ እንደሆነ ይሰማው ይሆናል። አንተም ከባድ ኃጢአት በመፈጸምህ ምክንያት ከይሖዋ ጋር ያለህ ግንኙነት ተበላሽቶ ከሆነ ወደ ቀድሞው መንፈሳዊ አቋምህ መመለስ በጣም ብዙ ጥረት እንደሚጠይቅ ሊሰማህ ይችላል። ይሁንና ይህን ጥረት ስታደርግ ብቻህን አይደለህም።

ይሖዋ “ኑና በመካከላችን የተፈጠረውን ችግር ተወያይተን እንፍታ” የሚል ግብዣ አቅርቦልናል። (ኢሳ. 1:18) እስካሁንም ‘ችግሩን ለመፍታት’ ብዙ ጥረት አድርገሃል። እንዲህ ያለ ጥረት በማድረግህም ይሖዋ ይወድሃል። እስቲ አስበው፦ ወደ ጉባኤው በመመለስህ ይሖዋ ሰይጣን ላነሳው ክስ የማያሻማ መልስ መስጠት እንዲችል አድርገሃል!—ምሳሌ 27:11

ይህን በማድረግህ ወደ ይሖዋ ይበልጥ ቀርበሃል፤ እሱም በምላሹ ወደ አንተ እንደሚቀርብ ቃል ገብቷል። (ያዕ. 4:8) ይሁንና እንደገና የጉባኤው ክፍል ሆነህ መቆጠርህ ብቻውን በቂ አይደለም። ከአንተ የሚጠበቅ ሌላም ነገር አለ። ለአባትህና ለወዳጅህ ለይሖዋ ያለህን ፍቅር ማጠናከርህን መቀጠል ይኖርብሃል። ይህን ማድረግ የምትችለው እንዴት ነው?

ልትደርስባቸው የምትችላቸው ግቦች አውጣ

ምክንያታዊ የሆኑ ግቦች ለማውጣት ሞክር። በመንፈሳዊ ሁኔታ እንደ መሠረት የሚቆጠረው ነገር፣ ማለትም ስለ ይሖዋና የወደፊቱን ጊዜ አስመልክቶ ስለሰጣቸው ተስፋዎች ያለህ እውቀት ሙሉ በሙሉ እንዳልጠፋ የታወቀ ነው። ሆኖም ከክርስቲያናዊ ሕይወት ጋር በተያያዘ እንደ ቤት መዋቅር የሚቆጠሩት ነገሮች መታደስ ያስፈልጋቸዋል፤ ይህም ምሥራቹን መስበክን እንዲሁም ከወንድሞችህና ከእህቶችህ ጋር አዘውትሮ መሰብሰብንና ከእነሱ ጋር ጊዜ ማሳለፍን ይጨምራል። የሚከተሉትን ግቦች ማውጣት ትችላለህ።

ወደ ይሖዋ አዘውትረህ ጸልይ። በሰማይ ያለው አባትህ፣ የሚሰማህ የጥፋተኝነት ስሜት ወደ እሱ መጸለይ እንዲከብድህ ሊያደርግ እንደሚችል ይረዳል። (ሮም 8:26) ያም ቢሆን ‘ሳትታክት ጸልይ’፤ የእሱ ወዳጅ ለመሆን ምን ያህል እንደምትጓጓ ለይሖዋ ንገረው። (ሮም 12:12) አንድሬ እንዲህ ብሏል፦ “ከፍተኛ የጥፋተኝነትና የኀፍረት ስሜት ይሰማኝ ነበር። ሆኖም ወደ ይሖዋ በጸለይኩ ቁጥር ይህ ስሜት እየቀነሰ መጣ። ውስጣዊ ሰላም እያገኘሁ ሄድኩ።” ምን ብለህ መጸለይ እንዳለብህ ግራ ከገባህ ንጉሥ ዳዊት ያቀረባቸውን የንስሐ ጸሎቶች መለስ ብለህ አንብብ፤ እነዚህ ጸሎቶች በመዝሙር 51 እና 65 ላይ ተመዝግበው ይገኛሉ።

መጽሐፍ ቅዱስን አዘውትረህ አጥና። እንዲህ ማድረግህ መንፈሳዊነትህን የሚያጠናክረው ከመሆኑም ሌላ ለይሖዋ ያለህ ፍቅር እንዲያድግ ይረዳሃል። (መዝ. 19:7-11) ፌሊፔ እንዲህ ብሏል፦ “መጀመሪያውኑም ቢሆን በመንፈሳዊ የተዳከምኩትና ይሖዋን የሚያሳዝን ነገር የፈጸምኩት መጽሐፍ ቅዱስን የማጥናት ልማድ ስላልነበረኝ ነው። ስህተቴን መድገም አልፈለግኩም፤ ስለዚህ ቋሚ የግል ጥናት ፕሮግራም እንዲኖረኝ አደረግኩ።” አንተም እንዲሁ ማድረግ ትችላለህ። ለግል ጥናት የሚሆኑህ ርዕሶች በመምረጥ ረገድ እርዳታ ካስፈለገህ አንድ የጎለመሰ ወዳጅህን ለምን አታማክረውም?

ከወንድሞችህና ከእህቶችህ ጋር ያለህን ወዳጅነት አድስ። ወደ ጉባኤ የተመለሱ አንዳንዶች፣ ‘ወንድሞችና እህቶች ለእኔ አሉታዊ አመለካከት ይኖራቸዋል’ የሚል ስጋት ያድርባቸዋል። ላሪሳ እንዲህ ብላለች፦ “በጣም ተሸማቅቄ ነበር። ወንድሞቼንና እህቶቼን እንደከዳኋቸው ተሰምቶኝ ነበር። ይህ ስሜት ለረጅም ጊዜ አሠቃይቶኛል።” መንፈሳዊነትህን እንደገና ለመገንባት በምታደርገው ጥረት የጉባኤ ሽማግሌዎችም ሆኑ ሌሎች የጎለመሱ ክርስቲያኖች ሊረዱህ እንደሚፈልጉ እርግጠኛ መሆን ትችላለህ። (“ ሽማግሌዎች ምን ማድረግ ይችላሉ?” የሚለውን ሣጥን ተመልከት።) እነዚህ ክርስቲያኖች ወደ ጉባኤ በመመለስህ በጣም ደስ ብሏቸዋል፤ መንፈሳዊነትህ እየተጠናከረ እንዲሄድም ይፈልጋሉ።—ምሳሌ 17:17

ከጉባኤው ጋር ይበልጥ እንድትቀራረብ ምን ሊረዳህ ይችላል? ከወንድሞችህና ከእህቶችህ ጋር አዘውትረህ በመንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ተካፈል፤ አብረሃቸው በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ ተገኝ፤ እንዲሁም አዘውትረህ አብረሃቸው አገልግል። ይህን ማድረግህ የሚረዳህ እንዴት ነው? ፊሊክስ እንዲህ ብሏል፦ “ወንድሞችና እህቶች የምመለስበትን ጊዜ በጉጉት ይጠብቁ ነበር። ከፍ አድርገው እንደሚመለከቱኝ ተሰማኝ። ሁሉም፣ እንደገና የጉባኤው ክፍል እንደሆንኩና ምሕረት እንደተደረገልኝ እንዲሰማኝ አድርገዋል፤ በይሖዋ አገልግሎት መቀጠል እንድችል አበረታተውኛል።”—“ ምን ማድረግ ትችላለህ?” የሚለውን ሣጥን ተመልከት።

ተስፋ አትቁረጥ!

ከይሖዋ ጋር ያለህን ወዳጅነት እንደገና ለመገንባት ጥረት በምታደርግበት ጊዜ ሰይጣን አንተን ለማዳከም እንደ አውሎ ነፋስ ያሉ ፈተናዎችን ማምጣቱን ይቀጥላል። (ሉቃስ 4:13) መንፈሳዊ ቤትህን ከአሁኑ በማጠናከር ለእነዚህ ፈተናዎች ተዘጋጅ።

ይሖዋ በጎቹን በተመለከተ እንዲህ ሲል ቃል ገብቷል፦ “የጠፋውን እፈልጋለሁ፤ የባዘነውን መልሼ አመጣለሁ፤ የተጎዳውን በጨርቅ አስራለሁ፤ የደከመውን አበረታለሁ።” (ሕዝ. 34:16) ይሖዋ በመንፈሳዊ ተዳክመው የነበሩ ብዙዎችን እንዲመለሱ ረድቷቸዋል። አንተም ከእሱ ጋር ጠንካራ ወዳጅነት መገንባትህን እንድትቀጥል ሊረዳህ እንደሚፈልግ አትጠራጠር።

^ አን.4 በዚህ ርዕስ ውስጥ የተጠቀሱት ስሞች ተቀይረዋል።