በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

Georgette Douwma/Stone via Getty Images

ፕላኔታችን ትተርፍ ይሆን?

ውቅያኖሶች

ውቅያኖሶች

ብዙ ምግብ የምናገኘው ከውቅያኖሶች ነው። መድኃኒት ለመሥራት የምንጠቀምባቸውን ብዙዎቹን ግብአቶችም የምናገኘው ከዚያው ነው። በዓለማችን ላይ ካለው ኦክስጅን ከግማሽ በላዩ የሚመነጨው በውቅያኖሶች ውስጥ ነው። ከዚህም ሌላ ውቅያኖሶች፣ ሰዎች የሚለቋቸውን አደገኛ የካርቦን ጋዞች ውጠው ያስቀራሉ። ይህ ብቻ ሳይሆን፣ ውቅያኖሶች የምድርን የአየር ንብረት ያስተካክላሉ።

ውቅያኖሶች የተደቀነባቸው አደጋ

የአየር ንብረት ለውጥ በኮራል ሪፎች፣ በባለዛጎል ዓሣዎች እንዲሁም በሌሎች የውቅያኖስ ፍጥረታት ላይ አደጋ እንዲጋረጥ አድርጓል። ሳይንቲስቶች እንደሚተነብዩት በባሕር ውስጥ ካሉት ፍጥረታት መካከል ከሩብ በላይ የሚሆኑትን ተሸክመው የያዙት ኮራል ሪፎች በቀጣዮቹ 30 ዓመታት ውስጥ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ሊጠፉ ይችላሉ።

ባለሙያዎች እንደሚገምቱት የባሕር ዓሣዎችን ከሚመገቡ ወፎች መካከል 90 በመቶ ገደማ የሚሆኑት ፕላስቲክ በልተው ያውቃሉ። በተጨማሪም ውቅያኖስ ውስጥ የሚጣል ፕላስቲክ በየዓመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የባሕር እንስሳትን እንደሚገድል ይገመታል።

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ የሆኑት አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በ2022 እንዲህ ብለው ነበር፦ “ውቅያኖሶቻችንን እየተንከባከብናቸው አይደለም። በዚህም የተነሳ በአሁኑ ወቅት ውቅያኖሶቻችን አደጋ ተጋርጦባቸዋል።”

ፕላኔታችን የተፈጠረችው ለዘላለም እንድትኖር ነው

የሰው ልጆች የሚያደርሱት ብክለት ከመጠን እስካላለፈ ድረስ ውቅያኖሶችና በውስጣቸው ያሉት ሕያዋን ፍጥረታት ራሳቸውን የማጽዳትና ጤንነታቸውን የመጠበቅ ችሎታ አላቸው። ሪጀነሬሽን፣ ኤንዲንግ ዘ ክላይሜት ክራይሲስ ኢን ዋን ጀነሬሽን የተባለው መጽሐፍ እንደሚገልጸው ሰዎች ውቅያኖሶችን መበከላቸውን እንዲያቆሙ ማድረግ ከተቻለ፣ ውቅያኖሶች “በተፈጥሮ ያገኙትን ራሳቸውን በራሳቸው የማጽዳትና የመጠገን ችሎታ ያለምንም ገደብ መጠቀም ይችላሉ።” አንዳንድ ምሳሌዎችን እስቲ እንመልከት።

  • ፋይቶፕላንክተን የተባሉ ጥቃቅን ፍጥረታት ለዓለም ሙቀት መጨመር ዋነኛ መንስኤ እንደሆነ የሚታመነውን ካርቦንዳይኦክሳይድን ወደ ውስጣቸው ያስገባሉ፤ እንዲሁም ያከማቻሉ። ፋይቶፕላንክተኖች የሚያከማቹት የካርቦንዳይኦክሳይድ መጠን በየብስ ላይ ያሉት ዛፎች፣ ሣሮችና ሌሎች ተክሎች በሙሉ በድምሩ ከሚያከማቹት የካርቦንዳይኦክሳይድ መጠን ጋር ተቀራራቢ ነው።

  • ባክቴሪያዎች የሞቱ ዓሣዎችን ቆዳና አጥንት በመብላት የውቅያኖሶችን ብክለት ይከላከላሉ። ከዚያም እነዚህ ባክቴሪያዎች ራሳቸው ለሌሎች የውቅያኖስ ፍጥረታት ምግብ ይሆናሉ። ስሚዝሶኒያን ኢንስቲትዩሽን ኦሽን ፖርታል እንደገለጸው ይህ ቅንጅት “ውቅያኖሶች ምንጊዜም የጸዱና የጠሩ” እንዲሆኑ ያስችላል።

  • በርካታ የውቅያኖስ ፍጥረታት በምግብ መፈጨት ሥርዓታቸው አማካኝነት የውቅያኖሱን አሲዳማነት ይቀንሳሉ። ይህም በኮራሎች፣ በባለዛጎል ዓሣዎችና በሌሎች ፍጥረታት ላይ የሚደርሰውን ጉዳት ይቀንሳል።

እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች

በተደጋጋሚ ጥቅም ላይ ሊውሉ የሚችሉ ከረጢቶችንና የውኃ ኮዳዎችን መጠቀም ወደ ውቅያኖሶች የሚጣለውን ፕላስቲክ ለመቀነስ ይረዳል

ውቅያኖሶችን ለማጽዳት ከመሞከር ይልቅ መጀመሪያውኑ አለማቆሸሹ የተሻለ ነው። በመሆኑም ሰዎች የፕላስቲክ ዕቃዎችን አንዴ ተጠቅመው ከመጣል ይልቅ ከረጢቶችን፣ የተለያዩ ቁሳቁሶችንና የዕቃ ማስቀመጫዎችን በተደጋጋሚ እንዲጠቀሙባቸው ባለሙያዎች ይመክራሉ።

ሆኖም እየተደረገ ያለው ጥረት በቂ አይደለም። በቅርቡ አንድ የአካባቢ ጥበቃ ድርጅት በአንድ ዓመት ውስጥ የውቅያኖስ ሞገድ ወደ ዳርቻ አውጥቶ የጣለውን 9,200 ቶን የሚመዝን ቆሻሻ ከ112 አገሮች አጽድቷል። ይሁንና ይህ ቆሻሻ በየዓመቱ ወደ ውቅያኖስ ከሚገባው ቆሻሻ ከ1,000 እጅ 1 ብቻ ነው።

ናሽናል ጂኦግራፊክ እንደዘገበው ‘እስካሁን የደረሰውን የውቅያኖሶች አሲዳማነት መቀልበስ የሚቻል አይመስልም። የዓለም ኢኮኖሚ የተገነባው ርካሽ በሆነ የነዳጅ ዘይት ላይ ስለሆነ የውቅያኖስ ፍጥረታት ይህ የሚያስከትለውን መጠነ ሰፊ ብክለት ከሥር ከሥር አጽድተው መጨረስ አይችሉም።’

ተስፋ ለማድረግ የሚያበቁ ምክንያቶች—መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

“ምድር በፈጠርካቸው ነገሮች ተሞልታለች። ባሕሩ እጅግ ትልቅና ሰፊ ነው፤ በዚያ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ትናንሽም ሆኑ ትላልቅ ሕያዋን ነገሮች ይርመሰመሳሉ።”—መዝሙር 104:24, 25

ውቅያኖሶችን የሠራቸውና ራሳቸውን የማጽዳት ችሎታ የሰጣቸው ፈጣሪያችን ነው። እስቲ አስበው፦ ፈጣሪያችን ስለ ባሕር እና በውስጡ ስላሉት ፍጥረታት ይህን ያህል እውቀት ካለው በውቅያኖሶቻችን ላይ የደረሰውን ጉዳት ማስተካከል ይችላል ብሎ ማመን ምክንያታዊ አይመስልህም? በገጽ 15 ላይ የሚገኘውን “አምላክ ፕላኔታችን እንደምትተርፍ ቃል ገብቷል” የሚለውን ርዕስ ተመልከት።