በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ኤም ሲ ኤስ ያለባቸውን ሰዎች መርዳት

ኤም ሲ ኤስ ያለባቸውን ሰዎች መርዳት

ኤም ሲ ኤስ ያለባቸውን ሰዎች መርዳት

እንደ ሽቶዎች ወይም እንደ ጽዳት መገልገያዎች ባሉ የተለመዱ ኬሚካሎች በቀላሉ የሚጠቁ ሰዎች አካላዊ ብቻ ሳይሆን ማኅበራዊ ችግርም ይገጥማቸዋል። ሰዎች በተፈጥሯቸው ማኅበራዊ ሕይወት ይወዳሉ፤ ሆኖም ሞቅ ያለ መንፈስ ያላቸውና ተጫዋች የሆኑ ብዙ ሰዎች በተለያዩ ኬሚካሎች በቀላሉ መጠቃት ሲጀምሩ የብቸኝነት ሕይወት ለመምራት ይገደዳሉ። “ቀደም ባሉት ጊዜያት ሌሎች የጤና ችግሮች ገጥመውኛል” ትላለች የኤም ሲ ኤስ ተጠቂ የሆነችው ሼሊ፣ “ይኼኛው ግን ከሁሉ የከፋ ነው። ሁኔታውን ይበልጥ አስቸጋሪ የሚያደርገው ደግሞ ከሌሎች ገለልተኛ የሚያደርግ መሆኑ ነው።”

የሚያሳዝነው ነገር፣ አንዳንድ ጊዜ የኤም ሲ ኤስ ተጠቂዎች አጉል የሆነ ባሕርይ ያላቸው ሰዎች እንደሆኑ ተደርገው መታየታቸው ነው። እርግጥ ለዚህ አንዱ ምክንያት ኤም ሲ ኤስ ዓለም ገና በደንብ ያላወቀው ውስብስብ ክስተት መሆኑ ነው። ይሁን እንጂ ስለ ኤም ሲ ኤስ በቂ እውቀት የሌለን መሆኑ በሽታው ያለባቸውን ሰዎች ለመጠራጠር ምክንያት አይሆነንም። አሜሪካን ፋሚሊ ፊዚሺያን የተሰኘው መጽሔት “እነዚህ ሕሙማን አጉል ባሕርይ ያላቸው ሆነው ሳይሆን በእርግጥ በበሽታው የሚሰቃዩ ሰዎች ናቸው” ይላል።

አስተዋይ የሆነ ሰው በሽታው እንቆቅልሽ ስለሆነና በቂ ግንዛቤ ስላላገኘ ብቻ ኤም ሲ ኤስ ያለባቸውን ሰዎች በጥርጣሬ ዓይን ከመመልከት ይልቅ ምሳሌ 18:​13 ላይ ባለው “ሳይሰማ ነገርን በሚመልስ ስንፍናና እፍረት ይሆንበታል” በሚለው መሠረታዊ ሥርዓት ይመራል። ያላንዳች አድልዎ ለታመሙ ሁሉ የክርስቶስ ዓይነት ፍቅር ማሳየት ምንኛ የተሻለ ነው! የሕክምና ሳይንስ ወደፊት የሚደርስበት ነገር ምንም ይሁን ምን እንዲህ ዓይነት ፍቅር በማሳየታችን ፈጽሞ አንቆጭም።

የክርስቶስ ዓይነት ፍቅር ማሳየት

የክርስቶስ ዓይነት ፍቅር ከእያንዳንዱ ሁኔታ ወይም ፍላጎት ጋር የሚስማሙ ውብ ገጽታዎች እንዳሉት አልማዝ ነው። ኤም ሲ ኤስ ያለበት ወዳጅ ካለን ለእሱ ያለን የክርስቶስ ዓይነት ፍቅር እንድናዝንለትና ራሳችንን በእሱ ቦታ አድርገን ችግሩን እንድንመለከት ሊገፋፋን ይገባል። በተጨማሪም ፍቅር “የራሱንም አይፈልግም፣” ወይም በሌላ አባባል የእኔ መብት ይጠበቅ አይልም። ለሌሎች ደህንነት ቅድሚያ ይሰጣል። ‘ታጋሾች እንድንሆን፣ ሁሉን እንድንችል፣ ሁሉን እንድናምንና በሁሉ እንድንጸና’ ይረዳናል። እንዲህ ዓይነቱ ፍቅር “ለዘወትር አይወድቅም።”​—⁠1 ቆሮንቶስ 13:​4-8

ሜሪ ኤም ሲ ኤስ የሌለባት ቢሆንም አንዳንድ ጓደኞቿ ግን አለባቸው። “ሽቶ የምወድ ቢሆንም እንኳ” ትላለች ሜሪ፣ “ኤም ሲ ኤስ ያለባቸውን ጓደኞቼን ስጠይቅ ሽቶ አለመቀባት እመርጣለሁ።” ሜሪ የኢየሱስን ምሳሌ በመኮረጅ በራሷ መንገድ “መርዳት እፈልጋለሁ” እያለች ነው። (ማርቆስ 1:​41) ትሬቨር ኤም ሲ ኤስ የያዘው ገና በሕፃንነቱ ነው። እናቱ “አብረውኝ የሚሠሩ ሰዎች ልጄን ለመርዳት ሲሉ የተቻላቸውን ሁሉ አድርገዋል” ስትል ተናግራለች። በአውስትራሊያ የምትኖረውና የይሖዋ ምሥክር የሆነችው ጆይ ኤም ሲ ኤስ ከባድ ሥቃይ ያስከተለባት ቢሆንም አዘውትረው የሚጠይቋትና ችግሯን እንደሚረዱ በግልጽ የሚያሳዩአት ወዳጆቿና ዘመዶቿ ጥሩ የብርታት ምንጭ እንደሆኑላት ትናገራለች።

በሌላ በኩል ደግሞ ኤም ሲ ኤስ ያለባቸው ሰዎች ሽቶ የሚቀቡ ሰዎችን በትዕግሥት ለመያዝ ጥረት ማድረግ አለባቸው። ቀደም ባለው ርዕስ ላይ የተጠቀሰው ኧርነስት “በሽታችን ራሳችን ልንሸከመው የሚገባ ሸክም ነው። ሌሎች ሰዎችም የራሳቸው ችግሮች አሉባቸው። ስለዚህ እኛን ለመርዳት የሚያደርጉትን ጥረት እናደንቃለን” ሲል ለንቁ! ዘጋቢ ተናግሯል። አዎን፣ ምንጊዜም ልንከተለው የሚገባን ከሁሉ የተሻለው መርህ ሌሎችን ለማስገደድ ከመሞከር ይልቅ አክብሮት ባለው መንገድ ትብብራቸውን መጠየቅ ነው። “ሽቶ የተቀቡ ሰዎች ምነው አሞሻል እንዴ? ብለው ሲጠይቁኝ” ትላለች ሎሬን፣ “‘ሽቶ ያሳምመኛል፣ ዛሬ ደግሞ ብሶብኛል መሰለኝ’ እላቸዋለሁ። ብዙውን ጊዜ አስተዋይ ለሆኑ ሰዎች እንዲህ ማለቱ ብቻ በቂ ነው።” እርግጥ፣ እንዲህ ሲባል በኤም ሲ ኤስ የምትሠቃይ ከሆነ ትብብር እንዲያደርጉልህ የምትፈልጋቸውን ጓደኞችህን በደግነት መንፈስ ማሳሰብ አትችልም ማለት አይደለም።

ቀደም ሲል የተጠቀሰችው ፓም “አሁን የምንሠቃየው ለጊዜው ብቻ ነው” ስትል ብሩሁን ጎን በማየት ጽፋለች። ፓም “ለጊዜው ብቻ ነው” ያለችው ለምንድን ነው? በቅርቡ የአምላክ መንግሥት ማንኛውንም ሥቃይ ከምድር ገጽ እንደሚያስወግድ በሚገልጸው የመጽሐፍ ቅዱስ ተስፋ ስለምታምን ነው። የአምላክ መንግሥት በጣም ጤናማ የሆኑ ሰዎች እንኳ ሳይቀሩ መጨረሻ ላይ ለመጋፈጥ የሚገደዱትን ሞትን ጭምር ያስወግዳል።​—⁠ዳንኤል 2:​44፤ ራእይ 21:​3, 4

እስከዚያው ድረስ ግን በአሁኑ ጊዜ ፈውስ ያልተገኘለትን ሕመም ችለው ለመኖር የተገደዱ ሰዎች በአምላክ መንግሥት አገዛዝ ሥር ‘ታምሜአለሁ የሚል ሰው የማይኖርበትን’ ጊዜ በጉጉት መጠባበቅ ይችላሉ። (ኢሳይያስ 33:​24) አሁን ባለው ሥርዓት ውስጥ ምንም ዓይነት ፈተና ቢደርስብን ሁላችንም እንደ ኢየሱስ ለመሆንና ከፊታችን ያለውን ሽልማት በትኩረት ለመመልከት የተቻለንን ሁሉ ጥረት እናድርግ።​—⁠ዕብራውያን 12:​2፤ ያዕቆብ 1:​2-4

[በገጽ 9 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

አንዳችን ለሌላው ፍቅር ማሳየት

አንድ ወዳጅህ ወይም ዘመድህ ኤም ሲ ኤስ ካለበት ወይም አንተ ራስህ ካለብህ የሚከተሉት የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ሊጠቅሙህ ይችላሉ:-

“እንግዲህ ሰዎች ሊያደርጉላችሁ የምትወዱትን ሁሉ እናንተ ደግሞ እንዲሁ አድርጉላቸው።”​—⁠ማቴዎስ 7:​12

“ባልንጀራህን እንደ ነፍስህ ውደድ።”​—⁠ማቴዎስ 22:​39

ለፍቅርና ለመልካምም ሥራ እንድንነቃቃ እርስ በርሳችን እንተያይ፤ በአንዳንዶችም ዘንድ ልማድ እንደ ሆነው፣ መሰብሰባችንን አንተው እርስ በርሳችን እንመካከር እንጂ፤ ይልቁንም ቀኑ ሲቀርብ እያያችሁ አብልጣችሁ ይህን አድርጉ።” (ዕብራውያን 10:​24, 25) ሁላችንም በተለይ በምንታመምበት ጊዜ መንፈሳዊ ማበረታቻ ያስፈልገናል። ኤም ሲ ኤስ ያለባቸው ብዙዎቹ ክርስቲያኖች በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ ለመገኘት የሚያደርጉት ጥረት የሚያስመሰግናቸው ነው፤ በጣም የታመሙት ደግሞ አንዳንድ ጊዜ በስልክ መስመር በመገናኘት ስብሰባውን ይከታተላሉ። በሌሎች ሁኔታዎች ደግሞ በመንግሥት አዳራሾች ውስጥ ሽቶ የተቀቡ ሰዎች የማይቀመጡባቸው ቦታዎች ኤም ሲ ኤስ ላለባቸው ሰዎች ክፍት እንዲሆኑ ይደረጋል። ይሁን እንጂ እንዲህ ማድረጉ ሁልጊዜ አመቺ ላይሆን ይችላል።

“መልካም ማድረግን . . . አትርሱ፤ እንዲህ ያለው መሥዋዕት እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘዋልና።” (ዕብራውያን 13:​16) መልካም ማድረግ ብዙውን ጊዜ የግል ጥቅምን መሥዋዕት ማድረግ እንደሚጠይቅ ልብ በሉ። ኤም ሲ ኤስ ያለበትን ሰው ለመርዳት ስትሉ መሥዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ ናችሁ? በሌላ በኩል ደግሞ ኤም ሲ ኤስ ያለባቸው ሰዎች ከሌሎች በሚጠብቁት ነገር ረገድ ምክንያታዊ መሆን አለባቸው። ለምሳሌ ያህል ክርስቲያን ሽማግሌዎች ስለ ሽቶ አጠቃቀም ደንብ ማውጣትም ሆነ ስለዚህ ጉዳይ በየጊዜው ማስታወቂያ መንገር አይችሉም። በተጨማሪም ሽቶ የተቀቡ ፍላጎት ያሳዩ አዳዲስ ሰዎችና እንግዶች ወደ ጉባኤ ስብሰባዎች ሲመጡ ጥሩ አቀባበል እናደርግላቸዋለን። ስለ ሽቶ አጠቃቀማቸው አስተያየት በመስጠት ልናሳፍራቸው ወይም ልናስጨንቃቸው እንደማንፈልግ የታወቀ ነው።

“ሰላምን ይሻ ይከተለውም።” (1 ጴጥሮስ 3:​11) የጤና ጉዳዮች የክርስቲያኖችን ሰላም ሊሰርቁ እንደማይገባ የታወቀ ነው። ያዕቆብ 3:​17 [NW ] “ላይኛይቱ ጥበብ . . . ሰላም ወዳድ፣ ምክንያታዊ፣ . . . ምሕረት የሞላባት ናት” ይላል። ሰላም ወዳድ የሆኑ ሰዎች ኤም ሲ ኤስ ያለባቸው ሆኑም አልሆኑ የኬሚካል ውጤቶችን ስለ መጠቀምም ሆነ አለመጠቀም አክራሪዎች ወይም ከሌሎች ብዙ የሚጠብቁ አይሆኑም። ልክ እንደዚሁም ‘ምሕረት የሞላባቸው’ ምክንያታዊ ሰዎች ሽቶ መቀባታቸው የሌላ ሰውን ጤንነት ሊያውክ እንደሚችል ካወቁ መብቴ ነው በሚል ግትር አቋም አይዙም። በዚህ መንገድ እነሱም “ሰላምን” እንደሚሹና “ሰላም” እንደሚፈጥሩ ያሳያሉ።​—⁠ያዕቆብ 3:​18

በሌላ በኩል ደግሞ ኤም ሲ ኤስ ያለበት ሰውም ሆነ ሌላ ሰው ምክንያታዊ ያልሆነ ግትር አመለካከት መያዙ ልክ እንደ ሽብልቅ ሰዎችን ይከፋፍላል። እንዲህ ያለው አመለካከት ማንንም ሊጠቅም የማይችል ከመሆኑም በላይ ግለሰቡ ከአምላክ ጋር ያለው ዝምድና ሊበላሽበት ይችላል።​—⁠1 ዮሐንስ 4:​20

እርግጥ ነው፣ ክርስቲያኖች ትልቅ ሀብት የሆነው የይሖዋ መንፈስ አላቸው። ይሖዋ መንፈሱን እንዲሰጣቸው አዘውትረው ሲለምኑት ግሩም የሆኑትን የመንፈስ ፍሬዎች በተለይም ደግሞ “ፍጹም የአንድነት ማሰሪያ” የሆነውን ፍቅርን ያዳብራሉ። (ቆላስይስ 3:​14 NW ) ከዚሁ ጋር ጎን ለጎን ደግሞ ታጋሾች በመሆን ይኸው መንፈስ በሌሎች ውስጥ የክርስቶስ ዓይነት ባሕርያት እንዲያሳድር ይፈቅዳሉ።​—⁠ገላትያ 5:​22, 23

[በገጽ 10 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

እንደ ሌሎች ሰዎች ሁሉ ኤም ሲ ኤስ ያለባቸው ሰዎችም ወዳጆች ያስፈልጓቸዋል