በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘ሙከራው ፍሬ ቢስ ሆኗል’

‘ሙከራው ፍሬ ቢስ ሆኗል’

‘ሙከራው ፍሬ ቢስ ሆኗል’

በፍጥነት እየተቀራረበችና እንደ አንድ መንደር እየሆነች በመጣችው ዓለማችን በሀብታሞችና በድሆች መካከል ያለው ልዩነት እየሰፋ እንደሆነ ይነገራል። ድንበር የለሽ ኢኮኖሚ ለመገንባት ስለሚደረጉት ጥረቶች አስተያየት የሰጠ አንድ ዓለም አቀፍ የንቅናቄ ቡድን እንዲህ ብሏል:- “ከ50 ዓመት በኋላም ሙከራው ውጤት አልባ ሆኗል። ለሁሉም ሰው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ከማስገኘት ይልቅ በዓለማችን አካባቢያዊ ሀብት ላይ ከፍተኛ ውድመት አድርሷል፣ ይህ ነው የማይባል ማኅበረሰባዊ አለመረጋጋት አምጥቷል፣ የብዙ አገሮች ኢኮኖሚ እንዲንኮታኮትና ድህነት፣ ረሀብ፣ ርስት አልባነት፣ ፍልሰት እንዲሁም ማኅበራዊ ቀውስ እንዲስፋፋ ምክንያት ሆኗል። ሙከራው ያልተሳካ ነበር ሊባል ይችላል።”

ችግሩ ምኑ ላይ ነው? ሰዎች የራስ ወዳድነት ፍላጎታቸውን ለማርካት ሲሯሯጡ ጉዳት ማስከተላቸው አይቀርም። ጆርጅ ሶሮስ የተባሉት ባለ ሀብት “የንግዱ ዓለም የሰው ልጆችን (ሠራተኛ ኃይል) እና ተፈጥሮን (መሬት) ጨምሮ ሁሉም ነገር እንደ ሸቀጥ እንዲታይ አድርጓል” ብለዋል። ሰብዓዊ አለፍጽምናም አስተዋፅዖ አለው። ሶሮስ “የማስተዋል ችሎታችን ከፍጽምና የራቀ መሆኑ አሌ የማይባል ሐቅ ነው፤ ፍጹም እውነት ላይ መድረስና ለማኅበረሰቡ የሚሆን እንከን የለሽ እቅድ መንደፍ ከእኛ አቅም በላይ ነው” ሲሉ ካረል ፖፐር የተባለውን ፈላስፋ አመለካከት አስተጋብተዋል።

ኢኮኖሚያዊ ልዩነቶች በዚህ ዘመን የተፈጠሩ ነገሮች አይደሉም። ኢየሱስ ከመምጣቱ ከስምንት መቶ ዓመት በፊት አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊ ‘ድሆችን ስለሚበድሉ፣ ችግረኞችንም ስለሚያስጨንቁ’ ሰዎች ተናግሯል። (አሞጽ 4:1) ተመሳሳይ የፍትህ መጓደል የተመለከተ አንድ በጥንት ዘመን የኖረ ንጉሥ ከ3,000 ዓመታት በፊት እንዲህ ሲል ጽፎ ነበር:- “ሰው ሰውን ለመጉዳት ገዢ የሚሆንበት ጊዜ አለ።”​—⁠መክብብ 8:9

ታዲያ መፍትሔው ምንድን ነው? ሥር የሰደዱት ኢኮኖሚያዊ ልዩነቶች በሰብዓዊ ድርጅቶች ዓለም አቀፋዊ ትብብር ሊወገዱ ይችላሉን? ሶሮስ እንዲህ ይላሉ:- “ሰላምን ማስጠበቅ ይቅርና የግለሰቦችን ነፃነት፣ ሰብዓዊ መብትና የአካባቢ ሀብት ደህንነትን ወይም ማኅበረሰባዊ ፍትሕን ማስጠበቅ የሚችሉ በቂ ዓለም አቀፋዊ ተቋማት የሉንም። ያሉን አብዛኞቹ ተቋማት የመንግሥት ማህበራት ሲሆኑ መንግሥታት ደግሞ ባብዛኛው ከጋራ ጥቅሞች ይልቅ የሚያስቀድሙት የራሳቸውን ጥቅም ነው። በጥቅሉ ሲታይ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በቻርተሩ መቅድም ውስጥ የሰፈሩትን ተስፋዎች ተግባራዊ ማድረግ አልቻለም።”

ታዲያ ተስፋ መቁረጥ ይኖርብናልን? በፍጹም። ጽድቅ የሰፈነበት ዓለም አቀፋዊ መንግሥት ቀርቧል! ይህ መንግሥት የኢየሱስ ስብከት ዋና ጭብጥ ነበር። “የአምላክ መንግሥት” ብሎ የጠራው ሲሆን ይህ መንግሥት እንዲመጣ እንዲጸልዩ ተከታዮቹን አስተምሯቸዋል። (ሉቃስ 11:2፤ 21:31) የአምላክ መንግሥት በሰማይ ተቋቁሟል፣ በቅርቡም የፍትሕ መጓደልን ከምድር ላይ ጠራርጎ ያጠፋል። (ራእይ 11:15, 18) የአምላክ መንግሥት የሙከራ አገዛዝ አይደለም። ከዚህ ይልቅ ለዘላለም ይጸናል። (ዳንኤል 2:44) ድህነትንና ጭቆናን ለዘለቄታው ያስቀራል። ይህ ለድሆችና ለተጨቆኑት አልፎ ተርፎም ለሁሉም ሰው እንዴት ያለ ድንቅ ተስፋ ነው!

[በገጽ 22 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ድንበር የለሽ ኢኮኖሚ የድሆችን ችግር አላስወገደም። አሁንም በቢልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የቧንቧ ውኃ ወይም የኤሌክትሪክ መብራት የላቸውም