በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የውዝግቡ መነሻ

የውዝግቡ መነሻ

የውዝግቡ መነሻ

በዩናይትድ ስቴትስ፣ ኦሃዮ የምትገኘው ስትራተን ኦሃዮን ከዌስት ቨርጅንያ ከሚያዋስነው የኦሃዮ ወንዝ አጠገብ የምትገኝ ትንሽ መንደር ናት። በመንደርነት የምትታወቅ ብትሆንም የራስዋ ከንቲባ አላት። ከሦስት መቶ ያነሱ ነዋሪዎች ያሏት ይህች መንደር በ1999 ባለ ሥልጣኖችዋ ሌሎች ሃይማኖቶችን ጨምሮ የይሖዋ ምሥክሮች በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተውን መልእክታቸውን ለሰዎች ለማድረስ ከቤት ወደ ቤት ከመሄዳቸው በፊት ፈቃድ እንዲያወጡ የሚያስገድድ ደንብ ባወጡ ጊዜ የውዝግብ ማዕከል ሆነች።

ይህ ጉዳይ ይህን ያህል ትልቅ ቦታ የተሰጠው ለምንድን ነው? እንዲህ ዓይነቱ መንግሥታዊ ድንጋጌ የይሖዋ ምሥክሮችን ብቻ ሳይሆን በዩናይትድ ስቴትስ የሚኖሩ ሰዎችን በሙሉ በነጻ የመናገር መብት የሚገድብ እንደሆነ ንባብህን እየቀጠልክ ስትሄድ ታገኘዋለህ።

ውዝግቡ እየተባባሰ የሄደው እንዴት ነው?

በስትራተን አካባቢ የሚገኘው የዌልስቪል የይሖዋ ምሥክሮች ጉባኤ አባላት እቤታቸው ድረስ እየሄዱ የስትራተንን ነዋሪዎች ሲጎበኙ በርካታ ዓመታት አልፈዋል። ሆኖም የመንደሪቱ ባለ ሥልጣናት ከ1979 ጀምሮ ይህን ከቤት ወደ ቤት እየሄዱ የሚያደርጉትን አገልግሎት ሲቃወሙ ቆይተዋል። በ1990ዎቹ ዓመታት መጀመሪያ ላይ አንድ የፖሊስ መኮንን “ስለ መብታችሁ ደንታ አይሰጠኝም” በማለት ጥቂት ምሥክሮችን ከከተማዋ አባሯል።

የስትራተን ከንቲባ በ1998 ከአራት የይሖዋ ምሥክሮች ጋር በተጋጩ ጊዜ ጉዳዩ ይበልጥ ተባባሰ። ምሥክሮቹ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ውይይት ለማድረግ ፍላጎት ያሳዩ ሰዎችን ካነጋገሩ በኋላ ወደቤታቸው በመመለስ ላይ ነበሩ። አንዷ ምሥክር እንደተናገረችው ወንዶች ቢሆኑ ኖሮ እስር ቤት ይጥሏቸው እንደነበረ ከንቲባው መናገራቸውን ገልጻለች።

የዚህ ግጭት መንስዔ “በየቤቱ እየዞሩ የሚሸጡና ገንዘብ የሚጠይቁ ሰዎችን ለመቆጣጠር” የወጣው የመንደሩ ድንጋጌ ሲሆን ይህ ድንጋጌ ለንግድ ወይም ለሌላ ዓላማ በየቤቱ መሄድ የፈለገ ማንኛውም ሰው ከከንቲባው ያለ ምንም ክፍያ ፈቃድ ማግኘት እንደሚኖርበት ያስገድዳል። የይሖዋ ምሥክሮች ይህ ድንጋጌ የመናገርንና የሃይማኖት ነጻነትን እንዲሁም እምነታቸውን ለማስፋፋት ያላቸውን መብት የሚጋፋ ሆኖ ታይቷቸዋል። ስለዚህም መንደሩ ይህን ድንጋጌ እንዲያሻሽል ተጠይቆ እምቢተኛ ሆኖ በመገኘቱ የይሖዋ ምሥክሮች በፌደራል ፍርድ ቤት ክስ መሠረቱ።

ጉዳዩ ሐምሌ 27 ቀን 1999 በኦሃዮ ደቡባዊ ወረዳ በዩናይትድ ስቴትስ የወረዳ ፍርድ ቤት ተሰማ። ይህ ፍርድ ቤት የመንደሩ ድንጋጌ ሕገ መንግሥቱን አይቃወምም ሲል ደነገገ። ከዚያም በኋላ የካቲት 20 ቀን 2001 የስድስተኛው አውራጃ ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት በተመሳሳይ ድንጋጌው ሕገ መንግሥቱን አይጥስም ሲል አረጋገጠ።

ክርክሩ የመጨረሻ እልባት እንዲያገኝ ኒው ዮርክ የሚገኘው የመጠበቂያ ግንብ መጽሐፍ ቅዱስና ትራክት ማኅበር ከዌልስቪል የይሖዋ ምሥክሮች ጉባኤ ጋር ሆኖ ለዩናይትድ ስቴትስ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጉዳዩ እንደገና እንዲታይ አመለከተ።

[በገጽ 3 ላይ የሚገኝ ሥዕል/ካርታ]

(መልክ ባለው መንገድ የተቀናበረውን ለማየት ጽሑፉን ተመልከት)

ሎስ አንጀለስ

ኒው ዮርክ

ኦሃዮ

ስትራተን