በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በአየር መዛባት ምክንያት የሚደርስ አደጋ አይኖርም!

በአየር መዛባት ምክንያት የሚደርስ አደጋ አይኖርም!

በአየር መዛባት ምክንያት የሚደርስ አደጋ አይኖርም!

“የሰው ልጅ ለምቾት፣ ለፍጥነትና ለትርፍ በሚያደርገው ሩጫ ምክንያት በምድራችን ላይ ብዙ ጉዳት አድርሷል።” እንዲህ የሚለው 5000 ዴይስ ቱ ሴቭ ዘ ፕላኔት (ዓለማችንን ከጥፋት ለማዳን የቀሩን 5000 ቀናት) በተባለ መጽሐፍ ልባስ ላይ የተጻፈ ቃል ነው። የሰው ልጅ ስግብግብነት ያስከተለውን ውጤት እየተመለከትን ነው። ስለ ምድር ሙቀት መጨመር የሚነገሩት ንድፈ ሐሳቦች ትክክል ሆኑም አልሆኑ አንድ የተረጋገጠ ሃቅ አለ። የሰው ልጅ ይህችን ውብ ምድር እያበላሻት ነው። “ምድርን የሚያጠፉትን ታጠፋ ዘንድ ዘመን መጣ” ከሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ሌላ ምንም ተስፋ የለንም።—ራእይ 11:18

አምላክ ይህን በሰብዓዊ አገዛዝ ላይ የተመሠረተ ብልሹ ሥርዓት አጥፍቶ የራሱን አዲስ ሥርዓት ያመጣል። ይህን ተስፋ ሃይማኖታዊ ቅዠት ነው ብለህ ወደ ጎን ገሸሽ ከማድረግህ በፊት ቆም ብለህ አስብ። ምድር ስለሚያስፈልጓት ነገሮች ከፈጣሪዋ ይበልጥ ማን ሊያውቅ ይችላል? በምድር ላይ የሚደርሰውን ሁሉ የመቆጣጠር መብትና ኃላፊነት አይኖረውም? መጽሐፍ ቅዱስ በኢሳይያስ 45:18 ላይ “ሰማያትን የፈጠረ እግዚአብሔር፣ እርሱም ምድርን የሠራና ያደረገ ያጸናትም፣ መኖሪያም ልትሆን እንጂ ለከንቱ እንድትሆን” አልፈጠራትም በማለት መልሱን ይሰጠናል። አምላክ ይህን ዓላማውን ለመፈጸም ጣልቃ ገብቶ እርምጃ መውሰድ ይችላል፣ ይወስዳልም።

አምላክ ምድርን የሚያስተዳድር አዲስ መንግሥት ወይም ንጉሣዊ አስተዳደር በማቋቋም ይህን ያደርጋል። ክርስቲያኖች “መንግሥትህ ትምጣ” ብለው ሲጸልዩ ይህ መንግሥት ሥልጣኑን እንዲረከብ መለመናቸው ነው። (ማቴዎስ 6:9, 10) የአምላክ መንግሥት ወይም ንጉሣዊ አስተዳደር ውስብስብ የሆኑትን የምድር ተፈጥሯዊ ዑደቶች በሚገባ እንደሚያውቀው በተግባር ያሳያል። ስለዚህም በአየር ብክለትና በአካባቢ መበላሸት ምክንያት የተጎዱትን የምድር ክፍሎች ማደስ ይችላል። ኢሳይያስ 35:1, 6 “ምድረ በዳውና ደረቁ ምድር . . . እንደ ጽጌረዳ ያብባል። . . . በምድረ በዳ ውኃ፣ በበረሀም ፈሳሽ ይፈልቃል” ይላል።

አምላክ ጣልቃ ገብቶ እርምጃ እስኪወስድ

በ2002 ከደረሰው የጎርፍ መጥለቅለቅ አደጋ በኋላ የምዕራብ ጀርመን ቻንስለር የነበሩት ሄልሙት ሽሚት “የተፈጥሮ አደጋዎች ግድቦችን እንዳይደረምሱ ማድረግ የሚችል ሰው የለም። አደጋዎች በየጊዜው ይመጣሉ” ሲሉ ጽፈዋል። እውነት ነው። በአየር መዛባት ምክንያት አደጋ በሚደርስበት ጊዜ የሰው ልጆች የተቻላቸውን ያህል አደጋውን ለመቋቋም ጥረት ከማድረግ ያለፈ ነገር ማድረግ አይችሉም። ይሁን እንጂ እነዚህ የተፈጥሮ አደጋዎች ብዙ ጥፋት የሚያደርሱ ቢሆኑም የሚያስገኙት ጠቃሚ ውጤትም አለ። ሰዎችን ለጎረቤቶቻቸው ፍቅርና አሳቢነት እንዲያሳዩ ያነሳሳሉ። (ማርቆስ 12:31) ለምሳሌ በአውሮፓ የደረሰው ጎርፍ በአንዳንድ ሰዎች ላይ ይህን የመሰለ ውጤት አስከትሏል። አንድ ጋዜጣ “ከፍተኛ ጉጉት ያላቸው ፈቃደኛ ሠራተኞች በነፍስ አድኑ ጥረት ለመረባረብ ከሁሉም የጀርመን ክፍሎች መጥተዋል። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ ታይቶ የማይታወቅ ከፍተኛ የበጎ ፈቃድ ዘመቻ ነበር” ሲል ጽፏል።

ከእነዚህ ፈቃደኛ ሠራተኞች መካከል ብዙ የይሖዋ ምሥክሮችም ይገኙበት ነበር። የሚከተለው ርዕስ የይሖዋ ምሥክሮች በከባድ ጎርፍ በተመቱ አራት የተለያዩ አገሮች የፈጸሙትን የነፍስ አድን ሥራ ይገልጻል። እነዚህ ክርስቲያኖች የሠሩት ሥራና ያሳዩት መልካም ባሕርይ ንፉግነትና ራስ ወዳድነት ሳይሆን ፍቅርና የወንድማማች መዋደድ በሚሰፍንበት በመጪው የአምላክ መንግሥት አገዛዝ ምን ዓይነት ኑሮ እንደሚኖር በጥቂቱ የሚያሳይ ነው።—ኢሳይያስ 11:9 *

ክርስቲያኖች አምላክ ለጥንቶቹ እስራኤላውያን በሰጠው ተስፋ ሊጽናኑ ይችላሉ። “እህልህን ወይንህንም ዘይትህንም ትሰበስብ ዘንድ በየጊዜው የበልጉን ዝናብና የክረምቱን ዝናብ ለምድራችሁ አወርዳለሁ” ብሏል። (ዘዳግም 11:14) ይህ ተስፋ በአየር መዛባት ምክንያት የሚደርስ አደጋ በማይኖርበት አዲስ የአምላክ ሥርዓት ውስጥ የመኖር መብት ለሚያገኙ ሁሉ ይፈጸማል።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.7 መጽሐፍ ቅዱስ ስለ አምላክ መንግሥት የሚሰጠውን ተስፋ በይበልጥ ለማወቅ ከፈለግህ በአካባቢህ ከሚገኙ የይሖዋ ምሥክሮች ጋር መገናኘት ወይም ለዚህ መጽሔት አዘጋጆች ደብዳቤ መጻፍ ትችላለህ።

[በገጽ 9 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

የተስተካከለ የአየር ሁኔታ

በአምላክ አዲስ ዓለም ውስጥ ሰዎች ቤታቸው ወይም እርሻቸው ድንገት በጎርፍ ይጥለቀለቃል ብለው አይሰጉም። (2 ጴጥሮስ 3:13) አምላክና ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ የአየር ሁኔታዎችን የመቆጣጠር ችሎታ እንዳላቸው መጽሐፍ ቅዱስ ያሳያል። የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት።

ዘፍጥረት 7:4:- “ከሰባት ቀን በኋላ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት በምድር ላይ ዝናብ አዘንባለሁ።”

ዘጸአት 14:21:- “እግዚአብሔርም ሌሊቱን ሁሉ ጽኑ የምሥራቅ ነፋስ አምጥቶ ባሕሩን አስወገደው፣ ባሕሩንም አደረቀው፣ ውኃውም ተከፈለ።”

1 ሳሙኤል 12:18:- “ሳሙኤልም ወደ እግዚአብሔር ጮኸ፣ እግዚአብሔርም በዚያን ቀን ነጐድጓድና ዝናብ ላከ፤ ሕዝቡም ሁሉ እግዚአብሔርንና ሳሙኤልን እጅግ ፈሩአቸው።”

ዮናስ 1:4:- “እግዚአብሔርም በባሕሩ ላይ ታላቅ ነፋስን አመጣ፣ በባሕርም ላይ ታላቅ ማዕበል ሆነ፣ መርከቢቱም ልትሰበር ቀረበች።”

ማርቆስ 4:39:- “[ኢየሱስ ከአምላክ ባገኘው ኃይል] ነቅቶም ነፋሱን ገሠጸው ባሕሩንም:- ዝም በል፣ ፀጥ በል አለው። ነፋሱም ተወ ታላቅ ፀጥታም ሆነ።”

[በገጽ 8 እና 9 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

በአምላክ አዲስ ዓለም ውስጥ በአየር መዛባት ምክንያት አደጋ ይደርስብኛል ብለን አንሰጋም