በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የዓለማችን ትልቁ ዘር

የዓለማችን ትልቁ ዘር

የዓለማችን ትልቁ ዘር

ከብዙ ዓመታት በፊት በውኃ እየተገፋ የመጣ አንድ በጣም ትልቅ ዘር በሞልዳይቪስ እና በኢንዶኔዢያ ደሴቶች ዳርቻ ላይ ሲያርፍ የብዙ ሰዎችን ትኩረት ስቦ ነበር። የዚህን ዘር መነሻ በሚመለከት የተለያዩ አፈ ታሪኮች ይነገሩ ጀመር። አንዳንዶች በባሕር ውስጥ የሚበቅል ዛፍ ዘር እንደሆነ ስለተሰማቸው ኮኮ ደ ሜር ወይም የባሕር ኮኮናት ብለው ሰየሙት። አዳምና ሔዋን በኤደን ገነት እንዳይበሉ የተከለከሉት ፍሬ ነው የሚል እምነት የነበራቸውም ሰዎች ነበሩ። ይሁን እንጂ በ18ኛው መቶ ዘመን አጋማሽ ላይ የፍሬው መነሻ ታወቀ። ይህ ምስጢራዊ ዘር የመጣው በሕንድ ውቅያኖስ ላይ በሚገኙት የሲሸልስ ደሴቶች ላይ ብቻ ከሚበቅል የዘንባባ ዛፍ ነበር።

ኮኮ ደ ሜር በብዛት የሚበቅለው በፕራላን ደሴት ላይ በሚገኘው በቫሊ ደ ሜ ነው። እነዚህ የዘንባባ ዛፎች እስከ 30 ሜትር ድረስ ሊያድጉ የሚችሉ ሲሆን በመቶዎች የሚቆጠሩ ዓመታት እንደሚኖሩ ይገመታል። ይህን ዛፍ ልዩ የሚያደርገው ወንዴና ሴቴ ዛፎች ያሉት መሆኑ ነው። የሴቴው ዛፍ ፍሬ ለማፍራት ከወንዴው ዛፍ በሚገኝ የአበባ ዱቄት መዳበር አለበት። ስለሆነም ይህ ዛፍ ዝርያውን መተካት እንዲችል ከሁለቱም ፆታዎች የደረሱ ዛፎች መኖራቸው የግድ አስፈላጊ ነው።

ከሴቴው ኮኮ ደ ሜር የሚገኘው ፍሬ በዓይነቱ ልዩ ነው። ፍሬው በዛፉ ላይ ሳለ ትልቅ አረንጓዴ ልብ ይመስላል። ውስጡ ግን እስከ 20 ኪሎ ግራም ሊመዝን የሚችል ባለ ሁለት ክፋይ ዘር አለው። አንዳንድ ፍሬዎች ከአንድ በላይ ዘር ይይዛሉ። ስለሆነም የዓለማችን ትልቅ ዘር ተብሎ ዘ ጊነስ ቡክ ኦቭ ሪከርድስ በተባለው የዓለማችን ድንቃድንቅ ነገሮች መዝገብ ላይ መመዝገቡ ምንም አያስደንቅም።

እጅብ ብለው የሚያፈሩትን ትላልቅ ድቡልቡል ድንጋዮች የሚመስሉ ፍሬዎች ከሥር ሆኖ ወደ ላይ የተመለከተ ሰው በአድናቆት መደመሙ አይቀርም። ሆኖም ዛፉ ሥር ቆሞ ወደ ላይ መመልከቱም ራሱ አደገኛ ነው። እነዚህ ፍሬዎች በአንድ ላይ እስከ 180 ኪሎ ግራም ሊመዝኑ ይችላሉ። የሚያስደንቀው ግን እስከ ዛሬ ድረስ ፍሬው ወድቆበት ጉዳት የደረሰበት ሰው የለም። ቢሆንም በነፋሻማ የአየር ሁኔታ ወደ ቫሊ ደ ሜ አለመሄዱ የተሻለ ነው። ደግሞም ይህን በዓይነቱ ልዩ የሆነ ፍሬ ይበልጥ ማድነቅ የሚቻለው ረጋ ያለ የአየር ሁኔታ ሲኖር ነው።