በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሕይወት የሚያስገኝ የሐሳብ ልውውጥ

ሕይወት የሚያስገኝ የሐሳብ ልውውጥ

ሕይወት የሚያስገኝ የሐሳብ ልውውጥ

ከምድር ፍጥረታት በሙሉ እርስ በርሳቸው በመነጋገር ብቻ ያልተወሰኑት የሰው ልጆች ናቸው። የሰው ልጆች በየትኛውም ብሔር ወይም የማኅበረሰብ ክፍል የሚገኙ ቢሆን፣ ጾታቸው ወይም የትምህርት ደረጃቸው ምንም ይሁን ምን የፍጥረት ሁሉ የበላይ ከሆነው አምላክ ጋር የመነጋገር ውስጣዊ ፍላጎት እንዳላቸው አሳይተዋል።

ይህን የሚያደርጉት አጉል እምነት ስላላቸው ነው? በፍጹም አይደለም! ባለፈው ርዕስ ላይ እንደተጠቀሰው አምላክ የሰው ልጆችን የፈጠረው በገዛ ራሱ አምሳል ነው። እርሱም በውስጣችን መንፈሳዊ ነገሮችን የመፈለግና የመረዳት ችሎታ አስቀምጧል። ይህ ችሎታ ደግሞ ከእርሱ ከሰማዩ አባታችን ጋር የመነጋገር ፍላጎትን ይጨምራል። (ዘፍጥረት 1:27፤ ማቴዎስ 5:3) እንዲያውም አምላክ ከእርሱ ጋር መነጋገርን ከፍተኛ ግምት ስለሚሰጠው እርሱ ራሱ ‘ጸሎት ሰሚ’ ተብሎ ተጠርቷል።—መዝሙር 65:2

ሁሉን ወደሚችለው አምላክ መጸለይ መቻል እንዴት ያለ ታላቅ ክብር ነው! ብዙ ሰዎች እንደ ፕሬዚዳንት ወይም ጠቅላይ ሚኒስትር ካሉ ከፍተኛ ባለ ሥልጣናት ጋር መነጋገር መቻልን እንደ ትልቅ መብት አድርገው ይቆጥሩታል። ይሖዋ አምላክ ግን በመላው አጽናፈ ዓለም ውስጥ አቻ የሌለው ታላቅ ባለ ሥልጣን ነው። ከእርሱ ጋር ለመነጋገር ደግሞ ቀጠሮ መውሰድ አያስፈልገንም። በማንኛውም ጊዜ፣ በማንኛውም ቦታ ሆነን ልንጸልይ እንችላለን። ድምፃችንን ሳናሰማ በልባችን እንኳ ሐሳባችንን ልንገልጽለት እንችላለን። (1 ሳሙኤል 1:12-15) ይሁን እንጂ ይሖዋ ቅኖች እንድንሆንና እርሱን በታዛዥነት እንድናዳምጥ ይፈልግብናል። (ሚክያስ 6:8፤ ማቴዎስ 6:5-13) ጥሩ የሐሳብ ልውውጥ የሚባለው ስንናገር ብቻ ሳይሆን ስናዳምጥም ጭምር ነው።

አምላክ ሲናገር ታዳምጣለህ?

አንድ ሰው አምላክ ሲናገር የሚያዳምጠው እንዴት ነው? በዋነኝነት በጽሑፍ በሰፈረው ቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘውን የእርሱን ትምህርት በማንበብና ሥራ ላይ በማዋል ነው። (2 ጢሞቴዎስ 3:16፤ 2 ጴጥሮስ 1:20, 21) ኢየሱስ “ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም” ብሏል። (ማቴዎስ 4:4) ታዲያ በጽሑፍ የሰፈረውን የአምላክ ቃል በማንበብና ያነበብከውን በሥራ ላይ በማዋል እርሱን ታዳምጣለህ?

ከይሖዋ ጋር አዘውትረው የሚነጋገሩ ሰዎች የእርሱን ሞገስና “አእምሮንም ሁሉ የሚያልፍ የእግዚአብሔር ሰላም” ያገኛሉ። (ፊልጵስዮስ 4:6, 7፤ ምሳሌ 1:33) በተጨማሪም ዛሬ ከሚያጋጥመን ስጋትና ችግር ሁሉ ተላቅቀው ገነት በምትሆነው ምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ አላቸው። (መዝሙር 37:29፤ ዮሐንስ 17:3) ይህ ሁሉ ተአምራዊ የሆነውን ከአምላክ ጋር የሐሳብ ልውውጥ የማድረግ ችሎታችንን በሚገባ በመጠቀማችን የምናገኘው ግሩም በረከት ነው።

[በገጽ 28 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ከአምላክ ጋር መነጋገር መጽሐፍ ቅዱስ ማንበብንና መጸለይን ያካትታል