በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ለዓለም ሰላም ያመጡ ይሆን?

ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ለዓለም ሰላም ያመጡ ይሆን?

የመጽሐፍ ቅዱስ አመለካከት

ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ለዓለም ሰላም ያመጡ ይሆን?

ማንኛውም ጦርነት አብቅቶ ማየት ትፈልጋለህ? በእርግጥም፣ ለብሔራዊና ለዓለም አቀፋዊ ግጭቶች ዲፕሎማሲያዊ መፍትሔ ሊኖራቸው ይገባል። ብዙዎች የዓለም መሪዎች ተባብረው ቢሠሩ ጦርነት ሊወገድ እንደሚችል ይሰማቸዋል። ይሁን እንጂ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ምንም ውጤት ባለማስገኘታቸው ተስፋ ቆርጠህ ይሆናል። ዲፕሎማቶች ባለፉት መቶ ዘመናት ሁሉ ስምምነቶችን ሲያጸድቁ፣ የአቋም መግለጫዎችን ሲያዘጋጁና የመሪዎች ጉባኤዎችን ሲያካሄዱ ቢኖሩም ዘላቂ መፍትሔ ያስገኙት ለጥቂት ችግሮች ብቻ ነው።

መጽሐፍ ቅዱስ ችግሮችን በውይይት በመፍታት ሰላም ስለማስፈን ብዙ የሚናገረው ነገር አለ። ለሚከተሉት ጥያቄዎች መልስ ይሰጣል:- በአሁኑ ጊዜ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ሰላም እንዳያመጣ እንቅፋት የሆኑት ነገሮች ምንድን ናቸው? ክርስቲያኖች በዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ውስጥ ጣልቃ መግባት አለባቸው? በመጨረሻ እውነተኛ ሰላም የሚገኘው እንዴት ይሆን?

ለሰላም እንቅፋት የሆነው ነገር ምንድን ነው?

ሰዎች በግምባር ተገናኝተው መነጋገራቸው ሰላም ሊያስገኝ እንደሚችል የሚያሳዩ አያሌ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች አሉ። ለምሳሌ ያህል አቢግያ፣ ዳዊትና ሠራዊቱ በቤተሰቧ ላይ የበቀል እርምጃ እንዳይወስዱ በዘዴ አሳምናቸዋለች። (1 ሳሙኤል 25:18-35) ኢየሱስ በሰጠው አንድ ምሳሌ ላይ እርቅ እንዲለምኑ አምባሳደሮች ከመላክ በቀር ሌላ አማራጭ ስላልነበረው አንድ ንጉሥ ተናግሯል። (ሉቃስ 14:31, 32) አዎን፣ መጽሐፍ ቅዱስ አንዳንዶቹ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ግጭቶችን ሊፈቱ እንደሚችሉ ይገልጻል። ታዲያ ጦርነት በሚያካሂዱ ወገኖች መካከል ሰላም ለማምጣት የሚደረጉ ስብሰባዎች በአብዛኛው ስኬት አልባ የሚሆኑት ለምንድን ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ ዘመናችን አስቸጋሪ ጊዜ እንደሚሆን በትክክል ተንብዮአል። በሰይጣን ዲያብሎስ ክፉ ተጽዕኖ ምክንያት ሰዎች “ዕርቅን የማይሰሙ፣ . . . ጨካኞች፣ መልካም የሆነውን የማይወዱ፣ ከዳተኞች፣ ችኩሎች፣ በትዕቢት የተነፉ” ይሆናሉ። (2 ጢሞቴዎስ 3:3, 4፤ ራእይ 12:12) በተጨማሪም የዚህ ሥርዓት መደምደሚያ ምልክት ‘ጦርነትና የጦርነት ወሬ’ እንደሚሆን ኢየሱስ ተንብዮአል። (ማርቆስ 13:7, 8) ጦርነት ከጊዜ ወደጊዜ እየተስፋፋ መሄዱን ማን ሊክድ ይችላል? ታዲያ በብሔራት መካከል ሰላም ለማምጣት የሚደረጉ ጥረቶች መና መቅረታቸው ያስደንቃል?

በተጨማሪም ዲፕሎማቶች ግጭቶችን ለማስወገድ የቱንም ያህል ቢጥሩም ዋናው ዓላማቸው የራሳቸውን አገር ጥቅሞች ማራመድ እንደሆነ መዘንጋት አይኖርብንም። የፖለቲካዊ ዲፕሎማሲ አቢይ ተልእኮ ይህ ነው። ታዲያ ክርስቲያኖች እንደዚህ ባሉ ጉዳዮች ራሳቸውን ማጠላለፍ ይኖርባቸዋል?

ክርስቲያኖችና ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች

መጽሐፍ ቅዱስ “ማዳን በማይችሉ በሰው ልጆችና በአለቆች አትታመኑ” በማለት ይመክራል። (መዝሙር 146:3) ይህም፣ የዓለም ዲፕሎማቶች የተነሱበት ዓላማ ምንም ይሁን ምን ዘላቂ መፍትሔ ለማስገኘት ችሎታውም ሆነ ኃይሉ የላቸውም ማለት ነው።

ኢየሱስ በጴንጤናዊው ጲላጦስ ፊት ለፍርድ ቀርቦ ሳለ “መንግሥቴ ከዚህ ዓለም አይደለችም፤ መንግሥቴስ ከዚህ ዓለም ብትሆን፣ ወደ አይሁድ እንዳልሰጥ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበር፤ አሁን ግን መንግሥቴ ከዚህ አይደለችም” በማለት ተናግሯል። (ዮሐንስ 18:36) የሰላም ንድፈ ሐሳቦች ብዙውን ጊዜ በብሔራዊ ጥላቻና በፖለቲካዊ ስግብግብነት የጎደፉ ናቸው። በዚህም ምክንያት እውነተኛ ክርስቲያኖች በዚህ ዓለም ግጭቶችና በዲፕሎማሲያዊ ጥረቶቹ ከመጠላለፍ ይርቃሉ።

ታዲያ ይህ ማለት ክርስቲያኖች ለዓለም ጉዳዮች ደንታ ቢሶች ናቸው ወይም የሰው ልጅ ሥቃይ አይሰማቸውም ማለት ነው? አይደለም። በተቃራኒው እውነተኛ የአምላክ አገልጋዮች በዙሪያቸው በሚፈጸሙ መጥፎ ነገሮች ‘እንደሚያለቅሱና እንደሚተክዙ’ መጽሐፍ ቅዱስ ይገልጻል። (ሕዝቅኤል 9:4) ክርስቲያኖች በእንደነዚህ ዓይነት ጥረቶች የማይካፈሉት አምላክ ቃል በገባው መሠረት ሰላም እንደሚያመጣ ስለሚተማመኑ ብቻ ነው። ሰላም ሲባል ወደ አእምሮህ የሚመጣው ጦርነት መወገዱ ነው? የአምላክ መንግሥት ይህን እንደምታደርግ ጥርጥር የለውም። (መዝሙር 46:8, 9) ከዚህም በተጨማሪ የአምላክ መንግሥት የምድር ነዋሪዎች ሁሉ የተሟላ ጸጥታና ደኅንነት እንዲኖራቸው ታደርጋለች። (ሚክያስ 4:3, 4፤ ራእይ 21:3, 4) እንደዚህ ያለው የላቀ ሰላም በዲፕሎማሲያዊ ጥረት ወይም በሰብዓዊ “ሰላም አስከባሪ” ድርጅቶች ሊደረስበት አይችልም።

የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢትና ከዚህ ቀደም የተፈጸሙ ክንውኖች በግልጽ እንደሚያመለክቱት ሰዎች የሚያደርጓቸው ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ሰላም ያስገኛሉ ብሎ ተስፋ ማድረግ ትርፉ ብስጭት ብቻ ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ያመጣል ብለው ተስፋ የሚያደርጉና የአምላክን መንግሥት የሚደግፉ ግን እውነተኛ ሰላም እውን ሆኖ ለማየት ያላቸው ምኞት ይፈጸማል። አልፎ ተርፎም በዚህ እውነተኛ ሰላም ለዘላለም እየተደሰቱ ይኖራሉ!—መዝሙር 37:11, 29

[በገጽ 13 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

የዓለም ዲፕሎማቶች የተነሱበት ዓላማ ምንም ይሁን ምን ዘላቂ መፍትሔ ለማስገኘት ችሎታውም ሆነ ኃይሉ የላቸውም

[በገጽ 12 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

[በገጽ 12 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]

ከታች:- Photo by Stephen Chernin/Getty Images