በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ማንም ሰው ብቸኛ የማይሆንበት ጊዜ

ማንም ሰው ብቸኛ የማይሆንበት ጊዜ

ማንም ሰው ብቸኛ የማይሆንበት ጊዜ

በዘፍጥረት 2:18 ላይ የሚገኘው ዘገባ “እግዚአብሔር አምላክ ‘ሰው ብቻውን መሆኑ መልካም አይደለምና የሚስማማውን ረዳት አበጅለታለሁ’ አለ” ይላል። የሰው ልጆች የተፈጠሩት አብረው እንዲኖሩና እርስ በርስ እንዲረዳዱ ሆነው ነው።

ከይሖዋ አምላክ የተሻለ ወዳጅ ልናገኝ አንችልም። ሐዋርያው ጳውሎስ ይሖዋ “የርኅራኄ አባት፣ የመጽናናትም ሁሉ አምላክ” እንደሆነና ‘በመከራችን ሁሉ እንደሚያጽናናን’ ተናግሯል። (2 ቆሮንቶስ 1:3, 4) ማንኛውም አገልጋዩ ሥቃይ ሲደርስበት እንደሚያዝን ተናግሯል። የሌሎች ችግር የሚሰማው አምላክ ነው። “እርሱ አፈጣጠራችንን ያውቃልና፤ ትቢያ መሆናችንንም ያስባል።” (መዝሙር 103:14) ወደ ይሖዋ አምላክ ለመጠጋት አትገፋፋም? ስለ ፍቅሩ፣ ስለ ደግነቱና ስለ አሳቢነቱ አታመሰግነውም?

ይሖዋ ብቸኝነት የሚሰማቸውን ይረዳል

በጥንት ዘመናት የአምላክ አገልጋዮች ብቸኝነት እንዲሰማቸው የሚያደርግ ሁኔታ አጋጥሟቸው ነበር። ለእነርሱ ይሖዋ የብርታትና የመጽናናት ምንጭ ሆኖላቸዋል። ለምሳሌ ያህል ገና ወጣት ሳለ ለነቢይነት ሥራ የተጠራውን ኤርምያስን እንውሰድ። አርባ ከሚያክሉት የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊዎች መካከል የኤርምያስን ያህል ስለግል ስሜቱ የገለጸ የለም ለማለት ይቻላል። ከአምላክ ለመጀመሪያ ጊዜ የሥራ ምድቡን በሚቀበልበት ጊዜ ፈርቶና ብቃት እንደሌለው ተሰምቶት ነበር። (ኤርምያስ 1:6) ይህን የተሰጠውን ሥራ ለማከናወን ሙሉ በሙሉ በይሖዋ መመካት ነበረበት። በእርግጥም ይሖዋ “እንደ ኀያል ተዋጊ” ከእርሱ ጋር ነበር።—ኤርምያስ 1:18, 19፤ 20:11

ከኤርምያስ ዘመን 300 ዓመት ያህል ቀደም ብሎ ንግሥት ኤልዛቤል የበዓል ነቢዮቿ እንደተገደሉባት ስትሰማ ኤልያስን እንደምትገድል ማለች። ኤልያስ 460 ኪሎ ሜትር ያህል ርቆ በሲና ባሕረ ሰላጤ ወደሚገኘው ወደ ኮሬብ ተራራ ሸሸ። በዚያም ሌሊቱን ለማሳለፍ ወደ አንድ ዋሻ ሲገባ ይሖዋ “ኤልያስ ሆይ፣ እዚህ ምን ታደርጋለህ?” ሲል ጠየቀው። ኤልያስም በመላው የእስራኤል ምድር ከእርሱ በቀር ይሖዋን የሚያመልክ እንደሌለና ካለእሱ ለይሖዋ አገልግሎት የሚቀና አንድም ነቢይ እንደሌለ ገለጸ። ይሖዋ ብቻውን እንዳልሆነ አረጋገጠለት። ይሖዋ አብሮት እንደሆነና ኤልያስ ባያውቃቸውም 7,000 የሚያክሉ እስራኤላውያን ወገኖቹ ከእርሱ ጋር እንደሆኑ ነገረው። ይሖዋ ካጽናናውና ካረጋጋው በኋላ እምነቱን ገነባለት። ሥራውን ትቶ እንዳይሸሽ በማበረታታት ልቡን አነሳሳ። (1 ነገሥት 19:4, 9-12, 15-18) እኛም እንደ ኤልያስ ብቸኛ እንደሆንን ወይም ዋጋ እንደሌለን ሆኖ ከተሰማን ይሖዋ እንዲያበረታን ልንጸልይ እንችላለን። በተጨማሪም ክርስቲያን ሽማግሌዎች ታማኝ ወንድሞቻቸውን በማስተዋል ችሎታቸው በመጠቀም ሊያጽናኗቸውና በአምላክ ዓላማ አፈጻጸም ውስጥ ምን ቦታ እንዳላቸው እንዲያስተውሉ ሊረዷቸው ይችላሉ።—1 ተሰሎንቄ 5:14

ከእነዚህና ከሌሎች ምሳሌዎች ይሖዋ ብቸኝነት የሚሰማቸውን ለመደገፍና ለማጽናናት ፈቃደኛ እንደሆነ ልንገነዘብ እንችላለን። አዎን፣ “እግዚአብሔር ለተጨቈኑት ዐምባ ነው፤ በመከራም ጊዜ መጠጊያ ይሆናቸዋል።”—መዝሙር 9:9፤ 46:1፤ ናሆም 1:7

በጣም አዛኝና የሰው ችግር የሚገባው ሰው ነበር

ኢየሱስ ክርስቶስ የይሖዋን ባሕርያት በመቅዳት ፍጹም ሚዛናዊ የሆነ ስሜት በማሳየት ረገድ የሚደነቅ አርዓያ ትቶልናል። ኢየሱስ በናይን ከተማ ወደ ቀብር የሚሄዱ ሰዎች ባጋጠሙት ጊዜ ምን እንዳደረገ ሉቃስ ይገልጽልናል:- “እነሆ፤ ሰዎች የአንድ ሰው አስከሬን ተሸክመው ከከተማዋ ወጡ፤ ሟቹም ለእናቱ አንድ ልጅ ብቻ ነበር፤ . . . ጌታም ባያት ጊዜ ራራላትና፣ ‘አይዞሽ፤ አታልቅሺ’ አላት። ቀረብ ብሎም ቃሬዛውን ነካ፤ የተሸከሙትም ሰዎች ቀጥ ብለው ቆሙ፤ ኢየሱስም፣ ‘አንተ ጐበዝ፤ ተነሥ እልሃለሁ!’ አለው። የሞተውም ሰው ቀና ብሎ ተቀመጠ፤ መናገርም ጀመረ። ኢየሱስም ወስዶ ለእናቱ ሰጣት።” (ሉቃስ 7:12-15) የኢየሱስ ስሜት በሐዘን ታውኮ ነበር። በጣም አዛኝ ሰው ነበር። ኢየሱስ ብቸኛ ሆና ለነበረችው መበለት ልጅዋን መልሶ ሲሰጣት እንዴት ያለ ደስታ እንደተሰማት ገምት! ከዚያ በኋላ ብቸኛ አልሆነችም።

ኢየሱስ ‘በድካማችን የሚራራልን’ መሆኑ በጣም ያጽናናናል። ብቸኛ ለሆኑ ቅን ሰዎች ያዝንላቸዋል። በእርግጥም፣ በእርሱ በኩል ‘ምሕረትን መቀበልና በሚያስፈልገንም ጊዜ እርዳታ ማግኘት’ እንችላለን። (ዕብራውያን 4:15, 16) እኛም የኢየሱስን ፈለግ በመከተል ሐዘንና መከራ ለደረሰባቸው እንዲሁም ብቸኝነት ለሚሰማቸው ሰዎች የአዛኝነት ስሜት ልናሳይ እንችላለን። እኛም ብንሆን ሌሎችን የምንረዳ ከሆንን ብቸኝነት አይሰማንም። ይሁን እንጂ ብቸኝነት የሚያሳድርብንን አሉታዊ ስሜት ለማሸነፍ የሚያስችለን እርዳታ የምናገኝበት ሌላ መንገድ አለ።

የይሖዋ ቃል ብቸኝነታችንን እንድናሸንፍ ሊረዳን ይችላል

ብዙ ሰዎች “ቅዱሳት መጻሕፍት በሚሰጡት መጽናናት ተስፋ” ሊኖራቸው ችሏል። በአምላክ ቃል ውስጥ ብቸኝነታችንን እንድንቋቋም ሊረዱን የሚችሉ በርካታ ጠቃሚ ምክሮች አሉ። (ሮሜ 15:4፤ መዝሙር 32:8) ለምሳሌ የአምላክ ቃል “ከሆናችሁት በላይ ራሳችሁን ከፍ አድርጋችሁ እንዳታስቡ” ሲል ይመክረናል። (ሮሜ 12:3) ይህን ምክር በሥራ ለማዋል አስተሳሰባችንን ማስተካከል ሊያስፈልገን ይችላል። ትሁት መሆናችንና ልካችንን ማወቃችን፣ ስለ አቅማችንና ችሎታችን ተገቢ አመለካከት መያዛችን ሚዛናዊና ምክንያታዊ አመለካከት እንዲኖረን ይረዳናል። በተጨማሪም የአምላክ ቃል ለሌሎች ሰዎች ከልባችን እንድናስብ ይመክረናል። (ፊልጵስዩስ 2:4) ይህም ድርብ ጥቅም ያስገኝልናል። ለሌሎች መልካም ስታደርግ አንተም የምታገኘው ጥቅም ይኖራል። ከሰዎች ጋር የሚኖረን ይህ ዓይነቱ ጥሩ ግንኙነት በሕይወታችን ባዶነት እንዳይሰማንና ሕይወታችን ትርጉም ያለው እንዲሆን ያስችላል።

መጽሐፍ ቅዱስ ‘መሰብሰባችንን እንዳንተው’ ይመክረናል። (ዕብራውያን 10:24, 25) ስለዚህ በይሖዋ ምሥክሮች ስብሰባዎች ላይ እንደመገኘት ባሉት ገንቢ እንቅስቃሴዎች ተካፈል። ክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ለመንፈሳዊ፣ ለስሜታዊና ለአካላዊ ጤንነታችን አስተዋጽኦ እንደሚያደርጉ አያጠራጥርም። ለሌሎች የአምላክን መንግሥት ምሥራች መናገርም ሕይወታችንን ጤናማ በሆኑ እንቅስቃሴዎች ከምናስጠምድባቸው መንገዶች አንዱ ነው። አእምሯችን በትክክለኛ ነገር ላይ እንዲያተኩር ይረዳናል፣ እምነታችንን ያጠናክርልናል ተስፋችንንም ይጠብቅልናል።—ኤፌሶን 6:14-17

ወደ ይሖዋ በጸሎት ቅረብ። “የከበደህን ነገር በእግዚአብሔር ላይ ጣል፤ እርሱ ደግፎ ይይዝሃል።” (መዝሙር 55:22) የአምላክን ቃል በማጥናት ደስ ትሰኛለህ። (መዝሙር 1:1-3) የብቸኝነት ስሜት ሲመጣብህ በቃሉ ስለተገለጸው የይሖዋ ፍቅርና እንክብካቤ አሰላስል። መዝሙራዊው “ነፍሴ ከዐፈር ተጣበቀች። እንደ ቃልህ መልሰህ ሕያው አድርገኝ” ሲል ጽፏል።—መዝሙር 119:25

ማንም ሰው “ብቸኛ ነኝ” የማይልበት ጊዜ

ይሖዋ አምላክ ከጭንቀት፣ ከብስጭትና ከማንኛውም መጥፎ ስሜት የጸዳ አዲስ ዓለም እንደሚመጣ ቃል ገብቶልናል። “እንባን ሁሉ ከዐይናቸው ያብሳል፤ ከእንግዲህ ወዲህ ሞት ወይም ሐዘን ወይም ልቅሶ ወይም ሥቃይ አይኖርም፤ የቀድሞው ሥርዐት ዐልፎአልና” የሚል ተስፋ ሰጥቶናል። (ራእይ 21:4) አዎን፣ የተረሳ ነገር ከሚሆነው የቀድሞ ሥርዓት ውስጥ ባሁኑ ጊዜ እያስጨነቀን ያለው አካላዊ፣ አእምሯዊና ስሜታዊ ሥቃይ ይገኛል።

ምድር ሕይወታችንን በሚያበለጽጉልን ሰው ወዳድ ሰዎች የተሞላች ትሆናለች። ይሖዋ በኢየሱስ ክርስቶስ ሰማያዊ መንግሥት አማካኝነት ከማንኛውም ዓይነት ሕመም ለዘላለም ይፈውሰናል። በእርግጥ ገነት በምትሆነው ምድር ውስጥ አዳዲስና አስደናቂ የሆኑ ሥራዎች ይኖሩናል። ሁለተኛ “ብቸኛ ነኝ” የማንልበት ጊዜ በቅርቡ ይመጣል።

[በገጽ 8, 9 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ይሖዋ ስለሚረዳን ብቻችንን በምንሆንበት ጊዜ እንኳን ብቸኝነት አይሰማንም

[በገጽ 10 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

ስለ ኤርምያስና ስለ ኤልያስ የሚናገረው የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ምን ያስተምረናል?