በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በሚያዩት ነገር ለአደጋ የተጋለጡ ልጆች

በሚያዩት ነገር ለአደጋ የተጋለጡ ልጆች

በሚያዩት ነገር ለአደጋ የተጋለጡ ልጆች

በፊንላንድ የሚገኘው የንቁ! ዘጋቢ እንደጻፈው

በበርካታ ልጆች ዘንድ ፊልም፣ ቴሌቪዥን፣ ቪዲዮ፣ ዲቪዲ፣ የኤሌክትሮኒክ ጨዋታዎች እንዲሁም ኢንተርኔት በጣም የተለመዱ ነገሮች ሆነዋል። የፊንላንድ የፊልም ደረጃዎች መዳቢ ቦርድ በቅርብ ባወጣው ሪፖርት ላይ እንዳለው “አንዳንድ ግምታዊ አኃዞች እንደሚያሳዩት ልጆችና ወጣቶች የቪዲዮ ጨዋታዎችን በመጫወትና ፊልም በማየት የሚያጠፉት ጊዜ ከወላጆቻቸው ጋር ከሚያሳልፉት ጊዜ ጋር ሲነጻጸር ከ20 እስከ 30 ጊዜ በላይ ብልጫ አለው።” * የሚያሳዝነው እንዲህ ያለው ሁኔታ ልጆችን ለጉዳት ያጋልጣቸዋል።

በአንዳንድ አገሮች ባለ ሥልጣናት ለእይታ በሚቀርቡ ፕሮግራሞች ላይ የዕድሜ ገደብ በማበጀትና ደረጃ በማውጣት ልጆችን ከጉዳት ለመጠበቅ ሙከራ አድርገዋል። ሆኖም ሪፖርቱ እንደገለጸው ልጆችም ሆኑ ወላጆች ለደረጃዎቹ ያላቸው ግንዛቤ አናሳ ከመሆኑም በላይ ያላቸውን ጠቀሜታ አቅልለው ይመለከታሉ። በተጨማሪም ሲኒማ ቤቶችም ይሁኑ የቪዲዮ ካሴት ማከራያዎች የተቀመጠውን የዕድሜ ገደብ በቁም ነገር አያዩትም። ከዚህም በላይ አንዳንድ ፕሮግራሞችና ፊልሞች ጨርሶ ደረጃ አልወጣላቸውም።

በጥናቱ ውስጥ ከተካተቱት መምህራን መካከል አንዷ የታዘበችውን ስትናገር “ተማሪዎች በሚያዩት ፊልም ውስጥ የደም መፋሰስ እስከሌለ ድረስ ነውጠኝነትን ያበረታታሉ ከሚባሉት ፊልሞች ጐራ የሚመድቡት አይመስልም” ብላለች። ለሕፃናት ታስበው የተዘጋጁ የአሻንጉሊት ፊልሞችን ጨምሮ ብዙዎቹ የቪዲዮና የኤሌክትሮኒክ ጨዋታዎች ልጆች ላይ ጉዳት ሊያስከትሉ ይችላሉ።

ሪፖርቱ እንደገለጸው እያንዳንዱ ቤተሰብ “ልጆች የሚያዩትን ፊልምና የቴሌቪዥን ፕሮግራም የመቆጣጠር ትልቅ ኃላፊነት ተጥሎበታል።” በመደምደሚያው ላይ የሚከተለውን አመራማሪ ጥያቄ ሰንዝሯል “አዋቂዎች እንደመሆናችን መጠን ልጆችን ከመገናኛ ዘዴዎች ጐጂ ተጽዕኖ ለመታደግ ፍላጎቱ፣ ጥንካሬውና አቅሙ አለን?”

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.3 “ለእይታ በሚቀርቡ ፕሮግራሞች ላይ የሚጣለው የዕድሜ ገደብና ለልጆች የሚደረግ ጥበቃ” በሚል ርዕስ የቀረበው ሪፖርት በ340 የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች እንዲሁም በወላጆቻቸውና በመምህሮቻቸው ላይ የተካሄደን ጥናት መሠረት ያደረገ ነው።