በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከዓለም አካባቢ

ከዓለም አካባቢ

ከዓለም አካባቢ

በ2000 በዓለም ዙሪያ በግምት 8.3 ሚሊዮን አዳዲስ የሳንባ ነቀርሳ በሽተኞች የተገኙ ሲሆን ወደ ሁለት ሚሊዮን የሚጠጉ የበሽታው ተጠቂዎች ደግሞ ለሞት ተዳርገዋል። ሟቾቹ በአጠቃላይ ማለት ይቻላል፣ ዝቅተኛ ገቢ ባላቸው አገሮች ውስጥ የሚኖሩ ናቸው።​—⁠የአውስትራሊያ የሕክምና መጽሔት

“በአሁኑ ጊዜ ከኤች አይ ቪ ጋር የሚኖሩ ወጣቶች ቁጥር 10 ሚሊዮን የደረሰ ሲሆን በዓለም ዙሪያ በየዓመቱ በበሽታው ከሚያዙት 4.9 ሚሊዮን ሰዎች መካከል ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ከ15 እስከ 24 ዓመት ባለው የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ናቸው።”​—⁠የተባበሩት መንግሥታት የምጣኔ ሕዝብ ተቋም

የሚጓዙበት አቅጣጫ የጠፋቸው አልባጥሮሶች በዓለም ክበብ ዙሪያ ያደረጉት ጉዞ በሳተላይት የተቀረጸ ሲሆን ፈጣን የሆነው ምድርን ዞሮ ለመጨረስ የፈጀበት ጊዜ 46 ቀናት ብቻ ነው።​—⁠ሳይንስ መጽሔት፣ ዩ ኤስ ኤ

“ዓለማችን በቀን ውስጥ በእያንዳንዱ ሰዓት ለወታደሮች በጀት እንዲሁም የጦር መሣሪያና ቦምቦች ለማምረት ከ100 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር በላይ ታወጣለች።”​—⁠ቫይታል ሳይን 2005፣ ዎርልድዎች ኢንስቲትዩት

በቀሳውስት ላይ የሚሰነዘረው ጥቃት እየጨመረ ነው?

“ቄስ መሆን [ብሪታንያ] ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ ለአደጋ ከሚያጋልጡ ሙያዎች መካከል አንዱ ነው” ሲል የለንደኑ ዴይሊ ቴሌግራፍ በ2005 ዘግቧል። መንግሥት በ2001 ያካሄደው ጥናት፣ ቃለ ምልልስ ከተደረገላቸው ቀሳውስት መካከል ሦስት አራተኛ የሚሆኑት ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ ተገቢ ያልሆነ ነገር ወይም ጥቃት እንደተፈጸመባቸው አሳይቷል። ከ1996 አንስቶ ቢያንስ ሰባት ቄሶች በሰው እጅ ተገድለዋል። መርዚሳይድ በሚባል በአንድ የከተማ ክልል ውስጥ “ከሚገኙት 1, 400 የአምልኮ ቦታዎች መካከል በቀን በአማካይ በአንዱ ላይ ጥቃት፣ ስርቆት ወይም የንብረት ቃጠሎ ይፈጸማል።”

በዓይነታቸው ልዩ የሆኑ የዕፅዋትና የእንስሳት ዝርያዎች

የደን መጨፍጨፍ ቢኖርም እንኳ “የቦርኒዮ ደሴት በዓይነታቸው ልዩ የሆኑ በርካታ ዕፅዋትና እንስሳት ይገኙበታል” ሲል ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ ገልጿል። ዓለም አቀፍ የእንስሳት ሕይወት ተቋም እንዳለው ከ1994 እስከ 2004 ባለው ጊዜ ውስጥ ብሩኒ፣ ኢንዶኔዥያና ማሌዥያ በሚጋሯት በዚህች ደሴት ላይ የሥነ ሕይወት ተመራማሪዎች 361 አዳዲስ የዕፅዋትና የእንስሳት ዝርያዎች አግኝተዋል። ከተገኙት ዝርያዎች መካከል 260 አዳዲስ ነፍሳት፣ 50 ዕፅዋት፣ 30 ዓሦች፣ 7 እንቁራሪቶች፣ 6 እንሽላሊቶች፣ 5 ሸርጣኖች፣ 2 እባቦች እና አንድ ጉርጥ ይገኙበታል። ሆኖም ይህ ደን በምድር ወገብ አካባቢ የሚገኝ ጠንካራ እንጨትና የጎማ ዛፍ እንዲሁም የዘንባባ ዘይት ለማግኘት በሚካሄደው እየጨመረ የመጣ የደን ጭፍጨፋ ለአደጋ ሊጋለጥ ይችላል።

አጉል እምነት እየተስፋፋ ነው

“ቴክኖሎጂና ሳይንስ በተስፋፋበት በዚህ ዘመን እንኳ አጉል እምነት ያለውን ተቀባይነት አላጣም” ሲል አልኤንስባኽ የተባለው የጀርመን ድምፅ ማሰባሰቢያ ተቋም ዘግቧል። ረጅም ጊዜ የፈጀ አንድ ጥናት እንዳሳየው “ኅብረተሰቡ ጥሩና መጥፎ ገድ እንዳለ አሁንም የሚያምን ከመሆኑም በላይ ከሩብ ምዕተ ዓመት በፊት ከነበረው ይልቅ በዛሬው ጊዜ ይህ አጉል እምነት ይበልጥ ተቀባይነት እያገኘ መጥቷል።” በ1970ዎቹ ዓመታት ተወርዋሪ ኮከቦች በሕይወታቸው ላይ ተጽዕኖ እንደሚያሳድሩ የሚያምኑት 22 በመቶ የሚያህሉ ሰዎች ነበሩ። በአሁኑ ጊዜ ግን እንደዚህ ዓይነት እምነት ያላቸው ሰዎች 40 በመቶ ደርሰዋል። በዛሬው ጊዜ ማንኛውንም ዓይነት አጉል እምነት የሚቃወመው ከሦስት ጎልማሶች መካከል አንዱ ብቻ ነው። በጀርመን 1, 000 በሚሆኑ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ላይ የተካሄደ ሌላ ጥናት እንዳሳየው ከመካከላቸው አንድ ሦስተኛ የሚሆኑት መኪናቸው ውስጥ ወይም ቁልፍ መያዣቸው ላይ ጥሩ ገድ ያስገኛል የሚሉትን ነገር መያዝ እንደሚጠቅማቸው ያምናሉ።

የአንታርክቲክ ግግር በረዶ እየቀነሰ ነው

“ባለፉት 50 ዓመታት ውስጥ በአንታርክቲክ ባሕረ ገብ መሬት ላይ የሚገኙት 244 የበረዶ ግግሮች 87 በመቶ ቀንሰዋል”፤ ይህም ጠበብት ከገመቱት በበለጠ ፍጥነት መከሰቱን ክላሪን የተባለው የቦነስ አይረስ ጋዜጣ ዘግቧል። በአካባቢው ስለሚገኙት የበረዶ ግግሮች የተካሄደው የመጀመሪያው አጠቃላይ ጥናት፣ ባለፉት 50 ዓመታት ውስጥ የአየሩ ሙቀት ከ2.5 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ በላይ መጨመሩንም አሳይቷል። የበረዶ ግግሮቹ በከፍተኛ ሁኔታ እያነሱ መምጣታቸው በአመዛኙ በአየር ጠባይ ለውጥ ምክንያት የተከሰተ መሆኑን የብሪታንያ የአንታርክቲክ ጥናት ተቋም ባልደረባ የሆኑት ዴቪድ ቮን ተናግረዋል። እኚህ ግለሰብ “ሰዎች ተጠያቂ ናቸው?” ሲሉ ጠይቀዋል። “በእርግጠኝነት መናገር ባንችልም የዚህን ዐቢይ ጥያቄ መልስ ለማግኘት አንድ እርምጃ ወደፊት ተጠግተናል።”