በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘የምታመሰግኑ ሁኑ’

‘የምታመሰግኑ ሁኑ’

‘የምታመሰግኑ ሁኑ’

መጽሐፍ ቅዱስ አምላክን የሚያመልኩ ሰዎች አመስጋኝ እንዲሆኑ በተደጋጋሚ ያበረታታል። መዝሙር 92:1 “እግዚአብሔርን [“ይሖዋን፣” NW] ማመስገን መልካም ነው” ይላል። ሐዋርያው ጳውሎስም በተመሳሳይ ‘የምታመሰግኑ ሁኑ’ የሚል ምክር ሰጥቶ ነበር።—ቈላስይስ 3:15

አመስጋኝ እንድንሆን የሚያደርግ በቂ ምክንያት አለን። ዴቪስ በሚገኘው የካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር የሆኑት ሮበርት ኤመንስ እንዲህ በማለት ተናግረዋል:- “አመስጋኝነትን በተመለከተ የተደረጉ ጥናቶች እንዳመለከቱት ሰዎች አመስጋኝ መሆናቸው የዕለት ተዕለት ችግሮቻቸውን በተለይ ደግሞ ውጥረትን እንዲቋቋሙ ብሎም ስለራሳቸው ጥሩ አመለካከት እንዲኖራቸው በመርዳት ረገድ ከፍተኛ ጠቀሜታ አለው።”

ታይም መጽሔት አመስጋኝ መሆን ያለውን ሌላ ጥቅም ሲገልጽ እንዲህ ብሏል:- “ያላቸውን የአድናቆት ስሜት የሚገልጹ ሰዎች . . . ይበልጥ ብርታት የሚሰማቸው ከመሆኑም በላይ ብሩህ አመለካከት አላቸው፣ እምብዛም ውጥረት አያጋጥማቸውም እንዲሁም ከአብዛኛው ሕዝብ አንጻር ሲታይ በከባድ የመንፈስ ጭንቀት የመያዛቸው አጋጣሚ በጣም ጠባብ ነው።”

ይሁን እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ “በመጨረሻው ዘመን” ብዙ ሰዎች “ራሳቸውን የሚወዱ” እንዲሁም “የማያመሰግኑ” እንደሚሆኑ አስቀድሞ ተናግሯል። (2 ጢሞቴዎስ 3:1-5) ታዲያ እውነተኛ ክርስቲያኖች እንዲህ ያለው ዝንባሌ እንዳይጋባባቸው መከላከል የሚችሉት እንዴት ነው? መጽሐፍ ቅዱስን ያስጻፈው ይሖዋ አምላክ፣ “የሚበጅህ ምን እንደ ሆነ የማስተምርህ፣ መሄድ በሚገባህ መንገድ የምመራህ [እኔ] ነኝ” ብሏል። (ኢሳይያስ 48:17) የአምላክን ሕግጋት ብንታዘዝ የራሳቸውን ጥቅም በማሳደድ የተጠመዱ ሰዎች ከሚያጋጥማቸው ሥቃይ ራሳችንን መጠበቅ እንችላለን። በተጨማሪም ይሖዋ ጥረታችንን እንደሚመለከትና ዋጋችንን እንደሚከፍለን ቃል ገብቶልናል። (ዕብራውያን 6:10) እንዲህ ያሉት ጥቅሞች ይሖዋን ‘እንድናመሰግነው’ ይገፋፉናል።—መዝሙር 107:8