በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አጉል እምነት ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ጋር ይስማማል?

አጉል እምነት ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ጋር ይስማማል?

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

አጉል እምነት ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ጋር ይስማማል?

አንድ ጋዜጠኛ፣ ሕይወቱን የሚያጣው በአውሮፕላን አደጋ እንደሆነ አንድ ጠንቋይ ስለነገረው ለአንድ ዓመት ያህል በአውሮፕላን ከመጓዝ ተቆጥቦ ነበር። የፖለቲካ ሰዎችን፣ ነጋዴዎችን፣ የፊልም ተዋናዮችን፣ አትሌቶችንና የኮሌጅ ተማሪዎችን ጨምሮ በየትኛውም ማኅበራዊ ሁኔታና የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ሰዎች ከአጉል እምነት ጋር የተያያዙ ድርጊቶችን ይፈጽማሉ። እነዚህ ሰዎች ስለ አንድ ነገር ጥርጣሬ ሲያድርባቸው እንዲሁም ውጥረት አሊያም ጭንቀት ሲያጋጥማቸው እንዲህ ያለው ልማድ ከአደጋ እንደሚጠብቃቸው ወይም ያሰቡት ግብ ላይ ለመድረስ እንደሚረዳቸው ይሰማቸዋል።

በርካታ ሰዎች የተለያዩ አጉል እምነቶችን የሚመለከቷቸው አስደሳች እንደሆኑ ጥንታዊ ልማዶች አሊያም ሥነ ልቦናዊ ድጋፍ እንደሚሰጡ ጉዳት የሌላቸው ነገሮች አድርገው ነው። አሁን በሕይወት የሌሉት አንትሮፖሎጂስቷ ማርግሬት ሚድ የሚከተለውን አስተያየት ሰጥተው ነበር:- “አጉል እምነት፣ አንድ ነገር እንደጠበቅነው ሲሆን ለማየት ወይም ደግሞ መጥፎ ነገር እንዳይደርስ ለመከላከል ያለንን ከፍተኛ ፍላጎት የሚያንጸባርቅ ነው። በአጉል እምነት ሙሉ በሙሉ ባናምንም ይህን ዓይነቱን እምነት መቀበላችን፣ በአጉል እምነት እንደተተበተብን ሳይሰማን እምነቱ ከሚሰጠው ሥነ ልቦናዊ ድጋፍ ለመጠቀም ያስችለናል።” ያም ቢሆን አምላክን ለማስደሰት ቁርጥ ውሳኔ ያደረጉ ሰዎች፣ ‘እውነተኛ ክርስቲያኖች አጉል እምነት ተጽዕኖ ሊያሳድርባቸው ይገባል?’ ብለው ራሳቸውን መጠየቅ ይኖርባቸዋል።

አጉል እምነት ምንጩ ምንድን ነው?

አብዛኞቹ የሰው ልጆች የሚፈሯቸው በርካታ ነገሮች አሉ፤ ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ያህል ሰዎች ሞትን፣ የማይታወቁ ሁኔታዎችንና ከሞት በኋላ አለ የሚባለውን ሕይወት ይፈራሉ። የአምላክ ተቃዋሚ የሆነው ዓመጸኛው ሰይጣን፣ ሰዎችን ባሪያዎቹ ለማድረግ ቆርጦ የተነሳ ሲሆን ተንኮል ያዘሉ የሐሰት ትምህርቶችን በማስፋፋት ሰዎች ቀደም ሲል የጠቀስናቸውን ሁኔታዎች እንዲፈሩ ያደርጋል። (ዮሐንስ 8:44፤ ራእይ 12:9) ሰይጣን ሰዎችን ከአምላክ ለማራቅ ጥረት የሚያደርገው ብቻውን አይደለም። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሰይጣን ‘የአጋንንት አለቃ’ ተብሎ ተጠርቷል። (ማቴዎስ 12:24-27) አጋንንት እነማን ናቸው? በኖኅ ዘመን በርካታ መላእክት በአምላክ ላይ ያመጸውን የሰይጣንን ፈለግ በመከተል ራሳቸውን አጋንንት አድርገው ነበር። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በሰዎች አስተሳሰብ ላይ ተጽዕኖ ለማሳደር ጥረት ሲያደርጉ ቆይተዋል። ይህን ዓላማቸውን ለማሳካት ከሚጠቀሙባቸው ዘዴዎች መካከል አንዱ አጉል እምነት ነው።—ዘፍጥረት 6:1, 2፤ ሉቃስ 8:2, 30፤ ይሁዳ 6

ሰይጣን ካስፋፋቸው የሐሰት ትምህርቶች ውስጥ አንዱ፣ ሰዎች በአጉል እምነት እንዲያምኑ መሠረት ሆኗል። ይህም፣ ሰው ከሞተ በኋላ በሕይወት መኖሯን የምትቀጥል አንዲት የማትታይ ረቂቅ ነገር እንዳለችና ይህች ረቂቅ ነገር በሕይወት ያሉትን ሰዎች ለመጥቀም አሊያም ለመጉዳት ተመልሳ እንደምትመጣ የሚገልጸው ትምህርት ነው። ይሁንና መጽሐፍ ቅዱስ “ሙታን ግን ምንም አያውቁም” ይላል። አክሎም ሲገልጽ አንድ ሰው ከሞተ በኋላ “መሥራትም ሆነ ማቀድ” እንደማይችል እንዲሁም “ዕውቀትም ሆነ ጥበብ” እንደማይኖረው ይናገራል።—መክብብ 9:5, 10

‘በይሖዋ ዘንድ አስጸያፊ’ የሆነ ነገር

ብዙ ሰዎች የሰይጣንን የሐሰት ትምህርቶች ለማመን መርጠዋል። ይሁን እንጂ ከበርካታ ዓመታት በፊት አምላክ በዚህ ጉዳይ ላይ ለሕዝቡ ለእስራኤላውያን ግልጽ መመሪያ ሰጥቷቸው ነበር። የአምላክ ቃል እንዲህ ይላል:- “በመካከልህ . . . ሟርተኛ፣ ወይም መተተኛ፣ ሞራ ገላጭ፣ ጠንቋይ ወይም በድግምት የሚጠነቍል፤ መናፍስት ጠሪ ወይም ሙት አነጋጋሪ በመካከልህ ከቶ አይገኝ። እነዚህን የሚያደርግ ሁሉ በእግዚአብሔር ዘንድ አስጸያፊ ነውና።”—ዘዳግም 18:10-12

የሚያሳዝነው ግን እስራኤላውያን ይህን ማሳሰቢያ ያልታዘዙባቸው ወቅቶች ነበሩ። ለምሳሌ ያህል፣ በነቢዩ ኢሳይያስ ዘመን አንዳንዶች የተትረፈረፈ ምርት ማግኘት የሚችሉት “ዕድል” የተባለውን ጣዖት በማስደሰት እንደሆነ ያምኑ ነበር፤ ይህ አጉል እምነት ከባድ መዘዝ አስከትሎባቸዋል። የይሖዋን ሞገስና በረከት አጥተዋል።—ኢሳይያስ 65:11, 12

ክርስትና በተቋቋመበት ጊዜም ቢሆን ይሖዋ ለአጉል እምነት ያለው አመለካከት አልተለወጠም። ሐዋርያው ጳውሎስ በአጉል እምነት የተተበተቡትን የልስጥራ ሰዎች እንዲህ ብሏቸዋል:- “ከዚህ ከንቱ ነገር ርቃችሁ ሰማይንና ምድርን፣ ባሕርንም በውስጣቸውም የሚኖሩትን ሁሉ ወደ ፈጠረ ወደ ሕያው እግዚአብሔር [ተመለሱ]።”—የሐዋርያት ሥራ 14:15

ከአጉል እምነት መላቀቅ

ቁጥር ስፍር የሌላቸው አጉል እምነቶች ያሉ ሲሆን ሁሉንም የሚያመሳስላቸው አንድ ነገር አለ፤ ይኸውም ሁሉም አሳማኝ ምክንያት የላቸውም። አጉል እምነት ከሚያስከትላቸው ጉዳቶች አንዱ ሰዎች ለሚያጋጥማቸው መጥፎ ነገር ተጠያቂዎቹ ራሳቸው እንደሆኑ አምነው ከመቀበል ይልቅ እንዲህ ያለ ነገር የደረሰባቸው በዕድላቸው ምክንያት እንደሆነ እንዲያምኑ የሚያደርጋቸው መሆኑ ነው።

ደስ የሚለው ግን፣ በርካታ ሰዎች ከአጉል እምነት መላቀቅ ችለዋል። ኢየሱስ “እውነትንም ታውቃላችሁ፤ እውነትም ነጻ ያወጣችኋል” በማለት ተናግሯል። (ዮሐንስ 8:32) ለ25 ዓመታት ጠንቋይ የነበረችው ብራዚላዊቷ ክሌሜንቲና “የምተዳደረው በጥንቆላ ብቻ ነበር። ይሁን እንጂ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ከአጉል እምነት ነፃ አውጥቶኛል” ብላለች። እንደ እውነቱ ከሆነ፣ መጽሐፍ ቅዱስን አዘውትሮ ማጥናትና ለይሖዋ አምላክ ልባዊ ጸሎት ማቅረብ ውስጣዊ ጥንካሬ ማዳበር እንድንችል ይረዳናል። እንዲህ ማድረጋችን በተረጋጋና ምክንያታዊ በሆነ መንገድ ማሰብ እንድንችል ያደርገናል፤ ይህ ደግሞ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ እንዳንገባ የሚያደርጉንና ከጭንቀት የሚገላግሉን ጥበብ የተንጸባረቀባቸው ውሳኔዎች እንድናደርግ ያስችለናል።—ፊልጵስዩስ 4:6, 7, 13

መጽሐፍ ቅዱስ “ብርሃንስ ከጨለማ ጋር ምን ኅብረት አለው? ክርስቶስ ከቤልሆር [ከሰይጣን] ጋር ምን ስምምነት አለው?” የሚል ጥያቄ ያነሳል። በመሆኑም እውነተኛ ክርስቲያኖች ከአጉል እምነት መራቅ ይኖርባቸዋል።—2 ቆሮንቶስ 6:14-16

ይህን አስተውለኸዋል?

▪ በኢሳይያስ ዘመን የነበሩት በአጉል እምነት የተጠላለፉ እስራኤላውያን የታመኑት በአምላክ ሳይሆን በማን ላይ ነበር?—ኢሳይያስ 65:11, 12

▪ ሐዋርያው ጳውሎስ በአጉል እምነት የተተበተቡትን የልስጥራ ሰዎች ምን እንዲያደርጉ አሳስቧቸዋል?—የሐዋርያት ሥራ 14:15

▪ እውነተኛ ክርስቲያኖች አጉል እምነት ተጽዕኖ ሊያሳድርባቸው ይገባል?—2 ቆሮንቶስ 6:14-16

[በገጽ 10 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

አጉል እምነት፣ ሰዎች እውነተኛ ያልሆነ የደኅንነት ስሜት እንዲኖራቸው ያደርጋል