በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መልስ ማግኘት የምትችለው ከየት ነው?

መልስ ማግኘት የምትችለው ከየት ነው?

መልስ ማግኘት የምትችለው ከየት ነው?

ሃይማኖት ሊያሳካቸው ከሚገቡ ግቦች አንዱ የሕይወትን ዓላማ ማስተማር ነው። ይሁን እንጂ ብዙ ሰዎች ሃይማኖታቸው የሚያስተምረው ነገር መንፈሳዊ ፍላጎታቸውን እንዳላረካላቸው ተገንዝበዋል። በካቶሊክ ሃይማኖት ውስጥ ያደገችው ደኒዝ ያሳለፈችውን ሁኔታ እንዲህ ስትል ትገልጻለች፦ “የባልቲሞር የካቶሊክ ሃይማኖት ማስተማሪያ መጽሐፍ ‘አምላክ የፈጠረን ለምንድን ነው?’ የሚለውን ጥያቄና ‘አምላክ የፈጠረን የእሱን ጥሩነት ለማሳየት እንዲሁም በሰማይ ያለውን ዘላለማዊ ደስታውን ከእኛ ጋር ለመካፈል ነው’ የሚለውን መልስ ይዟል።

“ይህ ግን እዚህች ምድር ላይ የምኖረው ለምን እንደሆነ አጥጋቢ ምክንያት አይሰጥም” ስትል አክላ ተናግራለች። “እዚህ ያለሁት ወደ ሰማይ የምሄድበትን ጊዜ ለመጠባበቅ ያህል ብቻ ከሆነ እስከዚያው ድረስ በምድር ላይ ምን እንዳደርግ ነው የሚጠበቅብኝ?” ብዙ ሰዎች የደኒዝ ዓይነት ጥያቄ ይጠይቃሉ። አንድ ጥናት እንዳረጋገጠው ቃለ ምልልስ ከተደረገላቸው ሰዎች መካከል ሁለት ሦስተኛ የሚሆኑት፣ አብዛኞቹ አብያተ ክርስቲያናትና ምኩራቦች ሰዎች የሕይወትን ዓላማ እንዲያገኙ እንዳልረዷቸው ያምናሉ።

ከዚህም የተነሳ ብዙዎች መልስ ፍለጋ ወደ ሌላ አቅጣጫ ማለትም ወደ ሳይንስ ወይም ወደተለያዩ ፍልስፍናዎች ፊታቸውን አዙረዋል። ከእነዚህ ፍልስፍናዎች መካከል ሰብዓዊነት፣ ባዶነትና ትርጉም አልባነት እንዲሁም ዓላማ ቢስነት የሚሉት ይገኙበታል። ታዲያ እርካታ ያገኙ የሚመስሉት ጥቂቶች ሆነው ሳለ ሰዎች የሕይወትን ዓላማ ለማግኘት የሚዳክሩት ለምንድን ነው?

አብሮን የተፈጠረ መንፈሳዊነት

ዶክተር ኬቨን ኤስ ሲቦልድ ይህን መንፈሳዊ ፍላጎት “በዓለም ዙሪያ በሚኖሩ ሰዎች ላይ የሚታይ የሆነ ነገር የማምለክ ዝንባሌ” ሲሉ ጠርተውታል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በርካታ ሳይንቲስቶች ሰዎች የሕይወትን ጥልቅ ትርጉም የማወቅ ተፈጥሯዊ ፍላጎት አላቸው የሚል መደምደሚያ ላይ ደርሰዋል። እንዲያውም አንዳንድ ሳይንቲስቶች ሰዎች በዘር የወረሱት ባሕርይም ሆነ አፈጣጠራቸው ከእነሱ በላይ ከሆነ ኃይል ጋር ዝምድና የመመሥረት ተፈጥሯዊ ፍላጎት እንዳላቸው ያሳያል የሚል እምነት አላቸው።

ሰዎች በተፈጥሯቸው የማምለክ ፍላጎት አላቸው ወይስ የላቸውም የሚለው ጥያቄ በምሑራን ዘንድ ክርክር እየተካሄደበት ያለ ጉዳይ ቢሆንም አብዛኞቹ ሰዎች ግን የሰው ልጆች በተፈጥሯቸው መንፈሳዊ ፍላጎት እንዳላቸው ለማመን የሳይንስ ሊቃውንት ማረጋገጫ አያስፈልጋቸውም። ይህ በውስጣችን ያለው መንፈሳዊ ፍላጎት አንዳንዶች እጅግ አንገብጋቢ የሆኑ ጥያቄዎች ብለው የሚጠሯቸው እንደሚከተሉት ያሉ ጥያቄዎች በአእምሯችን ውስጥ እንዲቀሰቀሱ ያደርጋል፦ እዚህ ምድር ላይ የምንኖረው ለምንድን ነው? በሕይወታችን ምን ልናደርግ ይገባል? ለምናደርገው ነገር ከሁሉ በላይ በሆነ ፈጣሪ ፊት ተጠያቂ ነን?

በዙሪያህ ያለውን ተፈጥሮ ጊዜ ወስደህ በትኩረት ብትመለከት ከጥያቄዎቹ ውስጥ ለአንዳንዶቹ መልስ ታገኛለህ። ለምሳሌ ያህል፣ አንድ ሴል ብቻ ካላቸው ተሕዋስያን አንስቶ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር የብርሃን ዓመት ርቀት ላይ እስከሚገኙት የከዋክብት ረጨት ክምችቶች ድረስ ያሉትን ከአእምሮ የመረዳት ችሎታ በላይ የሆኑ ውስብስብ ፍጥረታት አስብ። እነዚህ ነገሮች የማሰብ ችሎታ ያለው አንድ ንድፍ አውጪ ወይም ፈጣሪ እንዳለ አይነግሩንም? መጽሐፍ ቅዱስ “ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ የማይታየው የእግዚአብሔር ባሕርይ ይኸውም ዘላለማዊ ኀይሉና መለኮትነቱ፣ ከፍጥረቱ በግልጽ ይታያል፤ ስለዚህ ሰዎች ማመካኛ የላቸውም” ይላል።—ሮሜ 1:20

መንፈሳዊ ፍላጎትህን አርካ

አምላክ ሰዎችን የፈጠረበትን መንገድ በተመለከተ መጽሐፍ ቅዱስ “በሰዎችም ልብ ዘላለማዊነትን አኖረ” ይላል። (መክብብ 3:11) አብሮን የተወለደው ምኞት መሞት ሳይሆን መኖር ነው። የሕይወትን ትርጉም የማወቅና በውስጣችን ለሚፈጠሩት ጥያቄዎች መልስ የማግኘት ተፈጥሯዊ ፍላጎት አለን።

ለጥያቄዎቻችን መልስ መፈለግ ሰው ሆኖ የመፈጠር አንዱ ክፍል ነው ሊባል ይችላል። ዘ ዎል ስትሪት ጆርናል የተባለው ጋዜጣ አዘጋጅ፣ ሰዎች በሳይንስና በቴክኖሎጂ መስክ ያስመዘገቧቸውን የሥራ ክንውኖች ከገለጹ በኋላ “እኛ ማን ነን? እዚህ ምድር ላይ የምንኖረው ለምንድን ነው? ወዴትስ እናመራለን? የሚሉት ጥያቄዎቻችን አሁንም መልስ አላገኙም” በማለት ጽፈዋል። ለእነዚህ ጥያቄዎች ከሁሉ ከተሻለ ምንጭ መልስ ብንፈልግ ብልህነት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ይህንን ምንጭ ሲገልጽ “[አምላክ] ሠራን እንጂ እኛ ራሳችን አይደለንም” ይላል።—መዝሙር 100:3 NW

መንፈሳዊ ፍላጎታችንን ለማርካት በፍጥረት ሥራ ላይ ለሚታዩት ከተአምር የማይተናነሱ ነገሮች ምክንያት ወደሆነው አካል ፊታችንን ማዞራችን ምክንያታዊ አይሆንም? ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን እንድናደርግ ምክር ሰጥቶናል። መንፈሳዊ ፍላጎታችንን ሊያረካልን የሚችለው የሕይወት ምንጭ የሆነው ፈጣሪ ብቻ እንደሆነ እምነት ነበረው።—መዝሙር 36:5, 9፤ ማቴዎስ 5:3, 6

በእርግጥም መንፈሳዊ ፍላጎታችንን ለማርካት ‘እዚህ ምድር ላይ የምንኖረው ለምንድን ነው?’ ለሚለው ጥያቄ አጥጋቢ መልስ ማግኘታችን ወሳኝ ነገር ነው። በዚህ ጉዳይ ላይ ፈጣሪ ያለውን መንፈስ የሚያድስ አመለካከት እንድትመረምር እንጋብዝሃለን።