በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክፉ ሰዎች በገሃነመ እሳት ይቃጠላሉ?

ክፉ ሰዎች በገሃነመ እሳት ይቃጠላሉ?

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

ክፉ ሰዎች በገሃነመ እሳት ይቃጠላሉ?

የፕሮቴስታንት ሰባኪ የሆነችው ገርትሩድ ገሃነመ እሳት እንዳለ አጥብቃ ታምናለች። ገሃነም ላይኖር ይችላል የሚለው አመለካከት ፍትሐዊ እንዳልሆነ ታስባለች። እንዲህ ዓይነት መቃጠያ ቦታ ከሌለ ዘግናኝ የሆኑ የተለያዩ ወንጀሎችን የፈጸሙ ክፉ ሰዎች ሳይቀጡ እንደሚቀሩ ሆኖ ይሰማታል። ገርትሩድ ከዚህ አቋሟ ንቅንቅ ማለት አትፈልግም። “ክፉዎች የሚቃጠሉበት ገሃነመ እሳት ከሌለ አምላክን ማምለክ አልፈልግም” በማለት ተናግራለች።

ብዙ ሃይማኖቶች እንደሚያስተምሩት ክፉ ሰዎች በገሃነመ እሳት ይቃጠላሉ? ካልሆነስ ምን ዓይነት ቅጣት ይጠብቃቸዋል?

የመጀመሪያው መለኮታዊ ቅጣት

መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚገልጸው አምላክ የመጀመሪያዎቹን ሰብዓዊ ባልና ሚስት ፍጹም አድርጎ ፈጥሯቸው ነበር። (ዘፍጥረት 1:27፤ ዘዳግም 32:4) ገነት በሆነች የአትክልት ስፍራ ውስጥ ያስቀመጣቸው ሲሆን ለዘላለም የመኖር አጋጣሚ ሰጥቷቸው ነበር። ይሁንና የመጀመሪያዎቹ ሰዎች ማለትም አዳምና ሔዋን አንድ የተከለከሉት ነገር ነበር። አምላክ ለአዳም እንዲህ ብሎት ነበር፦ “በአትክልት ስፍራው ውስጥ ከሚገኝ ከማንኛውም ዛፍ ፍሬ ትበላለህ። ነገር ግን መልካምና ክፉን ከሚያሳውቀው ዛፍ አትብላ፤ ምክንያቱም ከእርሱ በበላህ ቀን በእርግጥ ትሞታለህ።”—ዘፍጥረት 2:16, 17

የሚያሳዝነው ግን የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን ቀላል የሆነውን ይህን የታማኝነትና የታዛዥነት ፈተና አላለፉም። በዚህም ምክንያት ፈጣሪ በእነሱ ላይ የሞት ቅጣት መበየኑ አስፈላጊ ሆነ። አምላክ አዳምን እንዲህ አለው፦ “ከምድር ስለ ተገኘህ፣ ወደ መጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ እንጀራህን በፊትህ ላብ ትበላለህ፤ ዐፈር ነህና ወደ ዐፈር ትመለሳለህ።”—ዘፍጥረት 3:19

አዳምና ሔዋን በገሃነመ እሳት የሚቃጠሉ ቢሆን ኖሮ አምላክ እንዲህ ስላለው ቅጣት አያስጠነቅቃቸውም ነበር? ሐቁ እንደሚያሳየው ግን አምላክ ከሞት በኋላ ሥቃይ እንደሚኖር ምንም የጠቀሰው ነገር የለም። ደግሞስ እንዴት ሊሠቃዩ ይችላሉ? ምክንያቱም ከሞት በኋላ በሕይወት የምትቀጥል የማትሞት ነፍስ አልነበራቸውም። መጽሐፍ ቅዱስ “ኀጢአት የምትሠራ ነፍስ እርሷ ትሞታለች” በማለት ይህን ግልጽ ያደርገዋል።—ሕዝቅኤል 18:4 *

ፈጣሪያችን የሕይወት ምንጭ እንደመሆኑ መጠን ስለ ሕይወትም ሆነ ስለ ሞት ሁሉንም ነገር ያውቃል። “ሙታን . . . ምንም አያውቁም” በማለት በቃሉ አማካኝነት ነግሮናል። (መክብብ 9:5) አዳምና ሔዋን ከሞቱ በኋላ በገሃነመ እሳት ውስጥ ሊቃጠሉ የማይችሉት ለዚህ ነው። እነዚህ ሰዎች ሲሞቱ ወደ አፈር በመመለስ ከሕልውና ውጭ ሆነዋል። ከሞቱ በኋላ “ምንም አያውቁም።”

ከሞት በኋላ ልንሠቃይ እንችላለን?

መጽሐፍ ቅዱስ በሮም 5:12 ላይ እንዲህ ይላል፦ “በአንድ ሰው አማካኝነት ኃጢአት ወደ ዓለም ገባ፤ በኃጢአትም ምክንያት ሞት መጣ፤ . . . [በመሆኑም] ሞት ለሰው ሁሉ ተዳረሰ።” ታዲያ በሰው ልጆች ሁሉ ላይ ሞትን ያመጣው አዳም የተበየነበት ቅጣት ከሞተ በኋላ ወደ አፈር መመለስ ብቻ ከሆነ ሰዎች በኃጢአታቸው ምክንያት በገሃነም ለዘላለም ይሠቃያሉ ብሎ ማመን ምክንያታዊ ይሆናል?—1 ቆሮንቶስ 15:22

በአዳም ላይ ተፈጻሚነት የነበረው ሕግ በሁላችንም ላይ ይሠራል። “ኃጢአት የሚከፍለው ደሞዝ ሞት ነው።” ከዚህም በተጨማሪ አንድ ሰው ከሞተ “ከኃጢአቱ ነፃ ወጥቷል።” (ሮም 6:7, 23) ታዲያ ጥሩም ሆነ መጥፎ የሠሩ ሰዎች በሙሉ የሚሞቱ ከሆነና ከሞት በኋላ ማንም የማይሠቃይ ከሆነ አምላክ ነገሮችን የሚያከናውነው ፍትሐዊ በሆነ መንገድ ነው ማለት ይቻላል?

የአምላክ ፍትሕ

አምላክ ታዛዥ ለሆኑ የሰው ልጆች የነበረው ዓላማ የመጀመሪያዎቹን ሰብዓዊ ባልና ሚስት ከፈጠረ እንዲሁም ልጆች እንዲወልዱና ምድርን እንዲንከባከቧት መመሪያ ከሰጣቸው ጊዜ ጀምሮ አልተለወጠም። (ዘፍጥረት 1:28) “ጻድቃን ምድርን ይወርሳሉ፤ በእርሷም ለዘላለም ይኖራሉ” በማለት ከጊዜ በኋላ መናገሩ ይህ ዓላማው እንዳልተለወጠ በግልጽ ያሳያል።—መዝሙር 37:29

ጻድቃን በዚህች ምድር ላይ እንደሚኖሩ ልብ በል። ፍጹም ጤንነትና ደስታ አግኝተው ይኖራሉ። የአምላክ የመጀመሪያ ዓላማ፣ ምድር ጻድቃን በሆኑ ሰዎች እንድትሞላ ነበር፤ ከአፉ የወጣው ይህ ቃሉ “የተላከበትንም ዐላማ ይፈጽማል።” ይህ የሚሆነው አምላክ ክፉ የሆነውን አሁን ያለውን ሥርዓት አጥፍቶ በአዲስ ዓለም ሲተካው ነው።—ኢሳይያስ 55:11፤ ዳንኤል 2:44፤ ራእይ 21:4

አምላክ የሚጠብቅባቸውን ብቃቶች ሳያውቁ የሞቱ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ትንሣኤ የሚያገኙ ሲሆን እሱ ባዘጋጀው አዲስ ዓለም ውስጥ ለመኖር ምን ማድረግ እንዳለባቸው ይማራሉ። (ኢሳይያስ 11:9፤ ዮሐንስ 5:28, 29) በሌላ በኩል ደግሞ የአምላክን ሕግጋት ለመታዘዝ አሻፈረኝ የሚል ማንኛውም ሰው “ሁለተኛ ሞት” ይፈረድበታል። የዚህ ዓይነት ሞት የተፈረደባቸው ሰዎች መቼም ቢሆን አይነቁም።—ራእይ 21:8፤ ኤርምያስ 51:57

በግልጽ ለመመልከት እንደሚቻለው ይሖዋ የፍቅር አምላክ በመሆኑ ሰዎችን በገሃነመ እሳት አያሠቃይም። (1 ዮሐንስ 4:8) በሌላ በኩል ግን ክፉዎችን ለዘላለም አይታገሣቸውም። በመሆኑም መዝሙር 145:20 “እግዚአብሔር የሚወዱትን ሁሉ ይጠብቃል፤ ክፉዎችን ሁሉ ግን ያጠፋል” የሚል ማረጋገጫ ይሰጠናል። ይህ በእርግጥም አምላክ አፍቃሪና ፍትሐዊ መሆኑን የሚያሳይ እርምጃ አይደለም?

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.8 በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ “ነፍስ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሰውየውን ራሱን እንጂ ከሥጋው ተለይታ የምትሄድን ነገር አይደለም። ዘፍጥረት 2:7 እንዲህ ይላል፦ “እግዚአብሔር አምላክ ከምድር ዐፈር ወስዶ ሰውን አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስ እፍ አለበት፤ ሰውም ሕያው ነፍስ ሆነ።” አዳም ከሥጋው የተለየ ነፍስ አልተሰጠውም። ከዚህ ይልቅ አዳም ራሱ ሕያው ነፍስ ነበር።

ይህን አስተውለኸዋል?

▪ የማትሞት ነፍስ አለችን?—ሕዝቅኤል 18:4

▪ ሙታን ያሉበት ሁኔታ ምን ይመስላል?—መክብብ 9:5

▪ አምላክ ክፉዎችን የሚቀጣው እንዴት ነው?—መዝሙር 145:20

[በገጽ 11 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

“ሙታን . . . ምንም አያውቁም።”—መክብብ 9:5

[በገጽ 10 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]

ፎቶ፦ www.comstock.com