በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከዓለም አካባቢ

ከዓለም አካባቢ

ከዓለም አካባቢ

“ሲጋራ የማያጨሱ፣ ብዙ እንቅስቃሴ የሚያደርጉ፣ አልኮል በመጠኑ የሚጠጡ፣ እንዲሁም በቀን ለአምስት ጊዜ ያህል ፍራፍሬ ወይም አትክልት የሚመገቡ ሰዎች ዕድሜ እንዲህ ከማያደርጉ ሰዎች በአማካይ በ14 ዓመት ይረዝማል።” እዚህ መደምደሚያ የተደረሰው በ20,000 ሰዎች ላይ ለ11 ዓመት በተደረገ ጥናት ላይ በመንተራስ ነው።—ዩሲ በርክሌይ ዌልነስ ሌተር፣ ዩናይትድ ስቴትስ

“ዘና ለማለት ከሁሉ የተሻለው መንገድ ማንበብ ነው። . . . ውጥረትን ከግማሽ በላይ ለመቀነስ ስድስት ደቂቃ ብቻ እንኳ [ማንበብ] ይበቃል።”—ኢንዲያ ቱዴይ ኢንተርናሽናል፣ ሕንድ

የተጣሉ “አሻንጉሊቶች”

ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ በዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ ያለውን ሁኔታ አስመልክቶ ሲናገር “ኢኮኖሚው እየወደቀ መምጣቱ በርካታ ባለንብረቶች ጀልባዎቻቸውን ጥለው እንዲሸሹ እያደረገ ነው” ብሏል። ባለንብረቶቹ ስማቸውን ከጀልባዎቻቸው ላይ ፍቀው ካጠፉና የምዝገባ ቁጥሩን ካስወገዱ በኋላ ትተዋቸው ይሄዳሉ። አሊያም ጀልባዎቻቸውን ያሰጥሟቸዋል፤ ይህን የሚያደርጉበት አንደኛው ምክንያት ከኢንሹራንስ ኩባንያቸው ገንዘብ ለመጠየቅ ሲሉ ነው። እዚህ ሁሉ ጣጣ ውስጥ የከተታቸው ነገር ምንድን ነው? ታይምስ እንደገለጸው “አንዳንዶቹ ቤቶቻቸውን ለመሥራት ከባንክ የተበደሩትን ገንዘብ መክፈል ካቃታቸው ሰዎች ጋር የሚመሳሰል ችግር ውስጥ ገብተዋል፤ ማለትም ዋጋ እያጣ ለሚሄድ ንብረት ከፍተኛ ገንዘብ መክፈል ስለማይፈልጉ ክፍያቸውን ለማቋረጥ ይመርጣሉ።” ጋዜጣው “ወጪያቸው የማይቻል ተፈላጊነታቸውን ያጡ አሻንጉሊቶች” ሲል የጠራቸውን እነዚህን ጀልባዎች አስመልክቶ እንዲህ ብሏል፦ “ያገለገሉ ዕቃዎች ገበያውን ማጥለቅለቃቸው ዋጋ እንዲወድቅ ስላደረገ ባለንብረቶቹ ጀልባዎቻቸውን መሸጥ አልቻሉም። ጀልባዎቹን በወደቦቹ ላይ ለሚያቆዩበት የቦታ ኪራይና ለጥገና በየወሩ በመቶ የሚቆጠር የአሜሪካ ዶላር የማውጣት አቅም የላቸውም። በሕጋዊ መንገድ እንዳያስወግዷቸው ደግሞ ለዚህ የሚያስፈልገው በብዙ ሺህ የሚቆጠር ገንዘብ የላቸውም።”

ዕድሜያቸው ለትምህርት ያልደረሱ ልጆች ለሰውነታቸው ቅርጽ ይጨነቃሉ

የአራት ዓመት ልጆች እንኳ “የሰውነታቸው ቅርጽ በኅብረተሰቡ ዘንድ ተቀባይነት ያለው ዓይነት እንዲሆን ለማድረግ ሲጥሩ ይስተዋላል” በማለት የሲድኒው ሰንዴይ ቴሌግራፍ ዘግቧል። ዕድሜያቸው ለትምህርት ባልደረሱ ልጆች የአመጋገብና የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ልማድ ላይ የተደረገ አንድ ጥናት እንደገለጸው ወንዶችም ሆኑ ሴቶች ልጆች የሰውነታቸው ቅርጽ ያሳስባቸዋል፣ ይኸውም ሴቶቹ ክብደታቸውን ስለ መቀነስ ወንዶቹ ደግሞ ጡንቻ ስለ ማውጣት ይጨነቃሉ። የጥናቱ አዘጋጆች እንደተናገሩት “ልጆቹ እያንጸባረቁ ያሉት በአብዛኛው በሰውነታቸው ቅርጽ የማይደሰቱትን የእናቶቻቸውን አመለካከት ይመስላል።”

በኢንተርኔት የሚገበያዩ ልጆች

በዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ ካሉት “ልጆች መካከል አንድ አምስተኛ የሚሆኑት ወላጆቻቸውን ሳያስፈቅዱ በኢንተርኔት እንደሚገበያዩና ዕቃ ከሚገዙት መካከል ግማሾቹ የወላጆቻቸውን ክሬዲት ካርድ እንደሚጠቀሙ” የለንደኑ ዘ ዴይሊ ቴሌግራፍ ዘግቧል። ብዙ ልጆች ግብይት ለመፈጸም የሚያገለግሉ ድረ ገጾችንና ወላጆቻቸው በኢንተርኔት ሲገበያዩ የሚጠቀሙበትን ፓስወርድ የሚያውቁ ሲሆን ይህም የወላጆቻቸውን ክሬዲት ካርድ ቁጥር በቀላሉ እንዲያገኙ ያስችላቸዋል። አብዛኞቹ ወላጆች ልጆቻቸው እነሱን ሳያስፈቅዱ በኢንተርኔት ይገበያያሉ ብለው አያስቡም። ወላጆች ልጆቻቸው ስለሚያውቁት ነገር ባላቸው ግምትና ልጆቹ በእርግጥ በሚያውቁት ነገር መካከል “አስደንጋጭ የሆነ ልዩነት” መኖሩን ዘገባው ይገልጻል። ወላጆች ልጆቻቸውን አለማወቃቸው ከሚያስከትልባቸው ችግሮች አንዱ ለመጭበርበር አደጋ መጋለጣቸው ነው። ጋዜጣው በኢንተርኔት የሚገበያዩ ወላጆችን ሲመክር እንዲህ ብሏል፦ “የክሬዲት ወይም የዴቢት ካርዳችሁን የሚመለከቱ ዝርዝር መረጃዎችን ኢንተርኔት ላይ አታስቀምጡ”፤ ተአማኒ የሆኑ ድረ ገጾችን ብቻ ተጠቀሙ፤ እንዲሁም “ስትጨርሱ ድረ ገጹን በተገቢው መንገድ ዝጉ።”