በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከዓለም አካባቢ

ከዓለም አካባቢ

ከዓለም አካባቢ

“ሰዎች፣ ከማይፈልጓቸው ግለሰቦች ጋር ላለመነጋገር ሞባይል ስልኮችን እየተጠቀሙባቸው ነው፤ ከሞባይል ስልክ ተጠቃሚዎች መካከል 13 በመቶ የሚሆኑት አጠገባቸው ካለ ሰው ጋር ላለመነጋገር ሲሉ በሞባይላቸው እየተጠቀሙ እንዳለ ያስመስላሉ።”​—ፒው ሪሰርች ሴንተር፣ ዩናይትድ ስቴትስ

ያለፉት አምስት በጋዎች በአርክቲክ አካባቢ ከመቼውም ይበልጥ ዝቅተኛ የበረዶ መጠን የተመዘገበባቸው ወቅቶች ናቸው።​—ቢቢሲ ኒውስ፣ ብሪታንያ

“በአፍሪካ ውስጥ ለእርሻ አገልግሎት ሊውል ከሚችለው መሬት 47 በመቶ የሚሆነው ጥቅም ላይ አልዋለም።”​—ዘ ዊትነስ፣ ደቡብ አፍሪካ

“ባለፉት 10 ዓመታት ውስጥ ብቻ 10 አገሮች (ኔዘርላንድ፣ ቤልጅየም፣ ካናዳ፣ ስፔን፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ኖርዌይ፣ ስዊድን፣ ፖርቹጋል፣ አይስላንድ እና አርጀንቲና) ተመሳሳይ ፆታ ያላቸው ሰዎች በሕጋዊ መንገድ እንዲጋቡ ፈቅደዋል።”​—ፋሚሊ ሪሌሽንስ፣ ዩናይትድ ስቴትስ

“ግጭቱ” ጠባሳ ጥሎ አልፏል

በሰሜን አየርላንድ የተደረገ አንድ ጥናት እንዳመለከተው ከሆነ በአገሪቱ ሲካሄድ የቆየው የሃይማኖት ብጥብጥ ጠባሳ ጥሎ አልፏል። የአካባቢው ነዋሪዎች “ግጭቱ” በማለት የሚጠሩት ይህ ብጥብጥ ወደ ሠላሳ ለሚጠጉ ዓመታት የዘለቀ ሲሆን ሁለት ሦስተኛ በሚሆኑት የአገሪቱ ነዋሪዎች ላይ ሥነ ልቦናዊ ችግር አስከትሏል። በአልስተር ባምፎርድ ዩኒቨርሲቲ የአእምሮ ጤና እና ደኅንነት ማዕከል ይፋ እንዳደረገው በሰሜን አየርላንድ ከአሥር ሰዎች አንዱ በሆነ ወቅት ላይ ከአሠቃቂ ወይም ከከባድ አደጋ በኋላ በሚከሰት ጭንቀት ይሠቃያል፤ ዘ አይሪሽ ታይምስ ይህ ከየትኛውም አገር “የሚበልጥ ከፍተኛ አኃዝ” እንደሆነ ገልጿል። ጋዜጣው አክሎ ከአገሪቱ ሕዝብ ቁጥር “አንጻር ሲታይ ግጭቱ በዓለም ላይ አስከፊ ከሚባሉት ብጥብጦች ተርታ የሚመደብ ሲሆን ከ500 ሰዎች መካከል ለአንዱ ሞት ምክንያት ሆኗል” ብሏል።

አስቸጋሪ የአየር ንብረቶች​“በጣም እየተለመዱ የመጡ ክስተቶች”

በዩናይትድ ስቴትስ የሚታየው ያልተለመደ የአየር ሁኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል። እንደ ኃይለኛ ጎርፍ፣ ከባድ ድርቅና የበረዶ ውርጅብኝ ያሉ አስቸጋሪ የአየር ንብረቶች እንደ እንግዳ ነገር መቆጠራቸው ቀርቶ “በጣም እየተለመዱ የመጡ ክስተቶች” ሆነዋል። በቴክሳስ ቴክ ዩኒቨርሲቲ የአየር ንብረት ተመራማሪ የሆኑት ካትሪን ሄይሆ፣ ዩንየን ኦቭ ኮንሰርንድ ሳይንቲስትስ የተባለ ድርጅት ባዘጋጀው አንድ ስብሰባ ላይ ለሥራ ባልደረቦቻቸው እንዲህ ብለዋል፦ “ከአንዳንድ [የአየር ንብረት ለውጦች] ጋር የተላመድን ቢሆንም ገና ያለመድናቸው በርካታ አዳዲስ ለውጦች እየተከሰቱ ነው።” ሄይሆም ሆኑ ሌሎች ሊቃውንት ለአየር ንብረት መዛባትና ለአየሩ ቶሎ ቶሎ መለዋወጥ የሰው ልጆች አስተዋጽኦ እንዳደረጉ ይሰማቸዋል።