በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

ዓለምን መለወጥ የሚችለው ማን ነው?

ዓለምን መለወጥ የሚችለው ማን ነው?

“የዓለም ሕዝቦች ከመሪዎቻቸው መልስ ማግኘት ይሻሉ። የሚፈልጉት መፍትሔ እንጂ ያልተሳኩ ሙከራዎችን ወይም ሰንካላ ምክንያቶችን መስማት አይደለም።”​—የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ፣ ባን ኪሙን

የምንኖረው መጽሐፍ ቅዱስ “ለመቋቋም የሚያስቸግር በዓይነቱ ልዩ የሆነ ዘመን” ብሎ በሚጠራው ጊዜ ውስጥ ነው። (2 ጢሞቴዎስ 3:1) የምንሰማቸው ዜናዎች ስለ ጦርነት፣ ሽብርተኝነት፣ የኢኮኖሚ ቀውስና በቅርቡ ስለሚከሰት የአካባቢ ብክለት በሚገልጹ ዘገባዎች የተሞሉ ናቸው።

ታዲያ ወደፊትስ ሁኔታዎች ይሻሻሉ ይሆን? ሰብዓዊ መንግሥታት የዓለምን ችግሮች መፍታት ይችላሉ? ወይስ እርዳታ ለማግኘት ወደ ሌላ አካል ዞር ማለት ይኖርብናል?

መንግሥታት ምን ይላሉ?

በርካታ አገራት የአምላክ ድጋፍ እንዳላቸው ይናገራሉ። ለምሳሌ በዩናይትድ ስቴትስ፣ ሰዎች ለአገራቸው ታማኝ መሆናቸውን ለመግለጽ በሚደግሙት ሐሳብ ላይ “በአምላክ አገዛዝ ሥር ያለ አንድ ሕዝብ” የሚል ሐረግ ያለ ሲሆን በአገሪቱ ሳንቲሞችና የወረቀት ገንዘቦች ላይ ደግሞ “በአምላክ እንታመናለን” የሚሉት ቃላት ይገኛሉ።

የሚገርመው ነገር፣ በዩናይትድ ስቴትስ ብዙ ሰዎች በአምላክ መኖር እንኳ አያምኑም፤ የአምላክ ድጋፍ እንዳላቸው በሚናገሩ ሌሎች አገሮችም ቢሆን ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። በአምላክ መኖር የሚያምኑ ሰዎችም እንኳ አምላክ በሰው ልጆች ጉዳይ ውስጥ ጣልቃ የሚገባው እስከ ምን ድረስ እንደሆነ ያላቸው አመለካከት ይለያያል።

● አንዳንዶቹ አምላክ በሰው ልጆች ጉዳይ ውስጥ ጣልቃ የመግባት ፍላጎት ጨርሶ እንደሌለውና ሰው ራሱን በራሱ እንዲመራ እንደተተወ ይናገራሉ።

● ሌሎች ደግሞ አምላክ ሰዎችን የሚያስተዳድረው በሰብዓዊ መንግሥታት አማካኝነት እንደሆነና እነዚህ መንግሥታት ዓለምን ለመለወጥ የሚያደርጉትን ጥረት አምላክ እንደሚባርክላቸው ይናገራሉ።

ከእነዚህ ሐሳቦች አንዱ የአንተን አመለካከት ያንጸባርቃል?

እስቲ የሚከተለውን አስብ፦ የመጀመሪያው ሐሳብ ትክክል ከሆነ የምንገኘው እጅግ አሳሳቢ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ነው ማለት ነው። ሁለተኛው አባባል ትክክል ከሆነ ደግሞ እነዚህ ጥያቄዎች መልስ ያሻቸዋል፦ ‘አምላክ አንዱን አገር ከሌላው አስበልጦ ይመለከታል? ሁለት አገሮች ጦርነት ቢጀምሩና ሁለቱም ድል ለመቀዳጀት ልባዊ ጸሎት ቢያቀርቡ አምላክ የሚሰማው የማንን ጸሎት ነው?’ ወይስ ሁለቱንም አገሮች አይደግፍም?

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ያስተምራል?

1. ሰው ራሱን በራሱ እንዲያስተዳድር ተደርጎ አልተፈጠረም። መጽሐፍ ቅዱስ ‘ሰው አካሄዱን በራሱ አቃንቶ ሊመራ እንደማይችል’ ይናገራል። (ኤርምያስ 10:23) ታሪክ የዚህን አባባል እውነተኝነት ያረጋግጣል። የትኛውም ሰብዓዊ አስተዳደር ሌላው ቀርቶ ጥሩ ችሎታ ያላቸው ወይም በቅን ልቦና ተነሳስተው የሚያገለግሉ ሰብዓዊ መሪዎች እንኳ የተሻለ ዓለም ማምጣት አልቻሉም። ከዚህ ይልቅ ‘ሰው ሰውን መግዛቱ ጉዳት’ አስከትሏል።​—መክብብ 8:9

2. አምላክ የሚደርሱብንን መጥፎ ነገሮች ሲመለከት ያዝናል። ፈጣሪ ያለንበትን ሁኔታ የማያውቅ ወይም ስለ እኛ ደንታ የሌለው አምላክ አይደለም። እንዲያውም እኛን ለመርዳት እርምጃ ይወስዳል። እንዴት? ይህን የሚያደርገው “ፈጽሞ የማይፈርስ” በሆነው እሱ ባቋቋመው መንግሥት አማካኝነት ነው።​—ዳንኤል 2:44

3. የአምላክ መንግሥት እውነተኛ መስተዳድር ነው። ይህ መንግሥት፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ቅን ሰዎች አዘውትረው በሚጸልዩት ‘አባታችን ሆይ’ በሚለው ጸሎት ላይ የተጠቀሰው መንግሥት ነው። ሰዎች ይህን ጸሎት ሲጸልዩ “መንግሥትህ ይምጣ። ፈቃድህ በሰማይ እየሆነ እንዳለ ሁሉ በምድርም ላይ ይሁን” የሚል ልመና ለአምላክ ያቀርባሉ። (ማቴዎስ 6:10) የአምላክ መንግሥት፣ የአምላክ ፈቃድ በሰማይ ብቻ ሳይሆን በምድርም ጭምር እንዲፈጸም የሚያደርግ መሆኑን ልብ በል።

4. አምላክ በመንግሥቱ አማካኝነት ዓለምን የመለወጥ ችሎታ አለው፤ ደግሞም ይለውጠዋል። ይህን ማመን አስቸጋሪ ከሆነብህ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት የሆኑትን የሚከተሉትን ሐሳቦች ተመልከት።

● አምላክ ሰውን ከፈጠረው በኋላ ፍጹም ሕይወት እንዲመራ ሁኔታዎችን አመቻችቶለት ነበር።​—ዘፍጥረት 1:27-31

● በዛሬው ጊዜ በርካታ ችግሮች ያሉ ቢሆንም አምላክ ለምድር ያለውን ዓላማ አልለወጠም።​—መዝሙር 37:11, 29

● አምላክ፣ ለምድራችንም ሆነ ለሰው ልጆች ያወጣውን የመጀመሪያ ዓላማ ለማሳካት አንዳንድ እርምጃዎችን ወስዷል።​—ዮሐንስ 3:16

ስለ አምላክ መንግሥትም ሆነ ይህ መንግሥት ዓለምን የሚለውጠው እንዴት እንደሆነ ይበልጥ ማወቅ ትፈልጋለህ? የዚህ መጽሔት አዘጋጅ የሆኑት የይሖዋ ምሥክሮች ሊረዱህ ፈቃደኞች ናቸው። በሚቀጥለው ጊዜ ስታገኛቸው በሚከተሉት ጉዳዮች ላይ እንዲያወያዩህ ለምን አትጠይቃቸውም?

የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው?

የአምላክ መንግሥት ምን ለውጦችን ያመጣል?

የአምላክ መንግሥት እነዚህን ለውጦች የሚያመጣው መቼና እንዴት ነው?

ይህን አስተውለኸዋል?

● ሰብዓዊ መንግሥታት፣ ማከናወን የሚፈልጓቸውን ነገሮች በሙሉ መፈጸም ያልቻሉት ለምንድን ነው?​—ኤርምያስ 10:23

● አምላክ እንደሚያስብልን ያሳየው እንዴት ነው?​—ዮሐንስ 3:16

● የአምላክ መንግሥት ለምድራችንና በውስጧ ለሚኖሩ ሰዎች ምን ጥቅም ያስገኝላቸዋል?​—መዝሙር 37:11, 29

[በገጽ 27 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

ሰብዓዊ መንግሥታት የዓለምን ችግሮች መፍታት ይችላሉ? ወይስ እርዳታ ለማግኘት ወደ ሌላ አካል ዞር ማለት ይኖርብናል?