በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የሌሎችን ድጋፍ ጠይቁ

የሌሎችን ድጋፍ ጠይቁ

“በጉባኤያችን ውስጥ ግሩም ወዳጆች አሉን። አፍቃሪ ከመሆናቸውም ሌላ የሚያስፈልገንን ድጋፍ ያደርጉልናል። የቤተሰባችን አባላት እንደሆኑ ይሰማናል።”—ሊዛን፣ በአሥራዎቹ ዕድሜ የሚገኙ ሁለት ልጆች እናት

ተፈታታኝ ሁኔታ፦

ሁለት ትናንሽ ወንዶች ልጆች ያሏት አሊና “በጣም የሚደክመኝ ከመሆኑም ሌላ ጊዜ ጨርሶ አይበቃኝም፤ ከምንም በላይ ፈታኝ የሚሆኑብኝ ነገሮች እነዚህ ናቸው” በማለት ተናግራለች። አብዛኞቹ ነጠላ እናቶች እንደ አሊና ይሰማቸዋል። በመሆኑም በርካታ ነጠላ ወላጆች እርዳታ ሊሰጡ የሚችሉ የተወሰኑ ሰዎችን በአእምሯቸው ይይዛሉ፤ እገዛ በሚያስፈልጋቸው ጊዜ ምንም ሳይሳቀቁ እነዚህን ሰዎች ይጠይቋቸዋል።

የመፍትሔ ሐሳቦች፦

እምነት የሚጣልባቸው ዘመዶቻችሁንና ወዳጆቻችሁን ድጋፍ ጠይቁ። ልጆቻችሁን በመንከባከብም ይሁን በመጓጓዣና በቤት ጥገና ረገድ ሊረዷችሁ ወይም ስሜታዊ ድጋፍ ሊሰጧችሁ የሚችሉ ሰዎችን ስም ዝርዝር ለምን አታዘጋጁም? ያዘጋጃችሁትን ዝርዝር በየጊዜው እየተመለከታችሁ እንደ ሁኔታው ማስተካከያ አድርጉበት። በተጨማሪም መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ምን ዓይነት እርዳታ ሊሰጧችሁ እንደሚችሉ ለማጣራት ሞክሩ።

የይሖዋ ምሥክር የሆነችው ሬናታ ከእምነት አጋሮቿ ብዙ ድጋፍ አግኝታለች። እንዲህ ብላለች፦ “ምንጊዜም ሊረዱኝ ዝግጁ ናቸው። እኔና ዘጠኝ ዓመት የሆናቸው ሁለት ሴቶች ልጆቼ ጉንፋን ይዞን በነበረበት ወቅት ምግብ ማዘጋጀት አልቻልኩም። የጉባኤው አባላት ይህን እንደሰሙ በየቀኑ አንድ ሰው ምግብ ይዞልን እንዲመጣ ዝግጅት አደረጉ።” እንዲህ ዓይነቱ ደግነት በ⁠1 ዮሐንስ 3:18 ላይ ያሉትን “ልጆቼ ሆይ፣ በተግባርና በእውነት እንጂ በቃልና በአንደበት ብቻ አንዋደድ” የሚሉትን ቃላት ያስታውሰናል።

ሌላኛው ወላጅ እርዳታ ማበርከት ይችል ይሆን? አብዛኛውን ጊዜ ልጆቹን የማሳደግ ሕጋዊ መብት የሚሰጠው ለእናት ነው፤ በእርግጥ አባትየው ከልጆቹ ጋር መገናኘት እንዲችል ሕጉ ይፈቅድ ይሆናል፤ ሁኔታው እንዲህ ከሆነና አባትየው ኃላፊነት የሚሰማው እንዲሁም ከልጆቹ ጋር በተያያዘ እርዳታ ለማበርከት ፈቃደኛ ከሆነ በተወሰነ መጠን እንዲያግዝሽ ማድረግ ትችዪ ይሆናል። ደግሞም ልጆቹ ከአባታቸው ጋር ጊዜ ማሳለፍ ያስፈልጋቸዋል። *

ልጆቻችሁ የበኩላቸውን እርዳታ ማበርከት እንዲችሉ አሠልጥኗቸው። ዕድሜያቸውን ከግምት በማስገባት ለልጆቻችሁ ሥራ የምትሰጧቸው ከሆነ እናንተ ብቻ ሳትሆኑ እነሱም ይጠቀማሉ። ልጆች ሥራ መልመዳቸው ኃላፊነት የሚሰማቸው እንዲሆኑ የሚያሠለጥናቸው ከመሆኑም ሌላ የኋላ ኋላ በሕይወታቸው ውስጥ በጣም የሚጠቅማቸውን የሥራ ባሕል እንዲያዳብሩ ይረዳቸዋል።

^ አን.6 ክርስቲያን ወላጆች፣ ሁኔታው በሚፈቅደው መጠን እንዲሁም የልጆቻቸውን ጥቅም ከግምት በማስገባት የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶችን ተግባራዊ ማድረግ ይኖርባቸዋል። የፍርድ ቤት ውሳኔዎችን ማክበርም ተገቢ ነው።