በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከዓለም አካባቢ

ከዓለም አካባቢ

ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ አገሮች

ዩኒሴፍ፣ ከሰሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገሮች ላይ ያካሄደው ጥናት እንዳመለከተው “ከ5 ዓመት በታች ዕድሜ ካላቸው ልጆች መካከል የልደት ምሥክር ወረቀት ያላቸው 38 በመቶ የሚሆኑት ብቻ ናቸው።” ሆኖም በዚህ የዓለም ክፍል በሚገኙ አንዳንድ አካባቢዎች “ልጆች የጤና አገልግሎትና ትምህርት ለማግኘት እንዲሁም ወላጅ አልባ የሆኑ ልጆች የወላጆቻቸውን ንብረት ለመውረስ የልደት ምሥክር ወረቀት ሊኖራቸው ይገባል” ሲሉ የዩኒሴፍ የምሥራቅና የደቡባዊ አፍሪካ ምክትል ዳይሬክተር የሆኑት ኤልከ ቪሽ ገልጸዋል።

ጣሊያን

አንድ ጥናት እንዳመለከተው ከሆነ አብዛኞቹ ጣሊያናውያን ወጣቶች ከምንም በላይ የሚያስፈራቸው ነገር በኢንተርኔት አማካኝነት የሚደርስ ጥቃት ነው። ከ12 እስከ 17 ዓመት የዕድሜ ክልል ውስጥ ከሚገኙት መካከል 72 በመቶ የሚሆኑት ይህ ዓይነቱ ጥቃት በጣም እንደሚያስፈራቸው ተናግረዋል። ይህ አኃዝ አደንዛዥ ዕፅ ከሚፈሩ (55 በመቶ)፣ በትላልቅ ሰዎች እንደፈራለን ብለው ከሚፈሩ (44 በመቶ) ወይም የአባለ ዘር በሽታ ይይዘናል ብለው ከሚፈሩ (24 በመቶ) ወጣቶች ቁጥር ይበልጣል።

ጃፓን

ዘ ጃፓን ታይምስ እንደዘገበው ወጣት ጃፓናውያን በመሥሪያ ቤት የሚቀርብላቸውን የሥራ እድገት ለመቀበል ፈቃደኞች አይደሉም። አርባ በመቶ የሚሆኑት፣ የሥነ ምግባር ደንቦች አለመከበርና የማጭበርበር ድርጊቶች መስፋፋታቸው ያበሳጫቸዋል። ተቀጥረው የሚሠሩት ብዙዎቹ ሠራተኞች ለአለቆቻቸው ሐሳባቸውን በነፃነት መግለጽ ይከብዳቸዋል። በዕድሜ ትላልቅ የሆኑት ሠራተኞች በተቀጠሩበት መሥሪያ ቤት ለብዙ ጊዜ የሚቆዩ ሲሆን ወጣት ከሆኑት ሠራተኞች መካከል ግን 60 በመቶ የሚሆኑት ሥራቸው ላይ የሚቆዩት የተሻለ አጋጣሚ እስኪያገኙ ድረስ ብቻ ነው።

ብራዚል

ከ1980 እስከ 2010 ባሉት ዓመታት በብራዚል 800,000 የሚያህሉ ሰዎች በጦር መሣሪያ ተገድለዋል። ከሟቾቹ መካከል ከ450,000 በላይ የሚሆኑት ከ15 እስከ 29 በሚደርስ የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ናቸው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተፈጸሙ ወንጀሎች ላይ የተደረገው ጥናት አብዛኞቹ ግድያዎች የተፈጸሙት በቤት ውስጥ በተነሳ ጥል፣ ከጎረቤት ጋር በተፈጠረ ግጭት፣ በቅናት ስሜት ወይም በአሽከርካሪዎች መካከል በተፈጠረ ጠብ ምክንያት እንደሆነ ያሳያል።