በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሥርዓት አልበኝነት ሊወገድ ይችላል

ሥርዓት አልበኝነት ሊወገድ ይችላል

ሥርዓት አልበኝነት ሊወገድ ይችላል

“የወጣቶች ሥርዓት አልበኛ መሆን ሁልጊዜም ወጣቶች ለትላልቅ ሰዎችና ለአቋም መሥፈርቶቻቸው ያላቸውን ንቀትና ጥላቻ የሚገልጹበት መንገድ ተደርጎ ሲቆጠር ቆይቷል” ሲሉ ጄን ኖርመንና ማይረን ደብልዩ ሃሪስ የተባሉ ደራሲያን ተናግረዋል። ብዙ ወጣቶች ሁኔታውን ለመለወጥ ምንም ማድረግ አይቻልም የሚል አመለካከት ቢኖራቸውም “ከ3 ወጣቶች ውስጥ አንዱ ወላጆች ይበልጥ ትኩረት ሰጥተው ልጆቻቸውን ቢከታተሉ ኖሮ እንዲሁም በአሥራዎቹ የእድሜ ክልል የሚገኙ ልጆችም ያን ያህል የተሰላቹ ባይሆኑ ኖሮ በአሥራዎቹ እድሜ የሚገኙ ልጆች የሚፈጽሙት የሥርዓት አልበኝነት ድርጊት ሊገታ ይችላል ብሎ እንደሚያስብ” ጸሐፊዎቹ ተናግረዋል። ወጣቶችን በሥራ ማስጠመዱና የተሻለ ወላጃዊ ቁጥጥር ማድረጉ ሥርዓት አልበኝነትን የሚቀንስ ቢሆንም ጨርሶ ችግሩን ሊያስወግደው ይችላልን?

ብዙዎቹ ወጣቶች ብቻቸውን በሚሆኑበት ጊዜ ሰላማውያን ናቸው፤ በቡድን ወይም ሁለት በሚሆኑበት ጊዜ ግን የቂልነት ሥራ በመሥራት ትኩረት እንዲሰጣቸው ለማድረግ ይሞክሩ ይሆናል። ኔልሰን እንዲህ ያለ ወጣት ነበር፤ በአደገኛ ዕፆች ወይም በአልኮል መጠጦች ግፊት የሥርዓት አልበኝነት ድርጊት በመፈጸም ቁጣውንና ተቃውሞውን ይገልጽ ነበር። ጆሴ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስለ መሬት ክፍፍልና ስለ ሠራተኞች መብት በሰማው ስብከት ተነሳስቶ ተቃውሞውን ለመግለጽ በአድማዎችና በተደራጀ የሥርዓት አልበኝነት ድርጊቶች መካፈል እንዳለበት ተሰምቶት ነበር። ይሁን እንጂ ኔልሰንም ሆነ ጆሴ ከረብሸኝነት ወይም ከሥርዓት አልበኝነት እጅግ የተሻለ ነገር አግኝተዋል።

አንዳንድ የሥርዓት አልበኝነት መነሾዎች

አንዳንድ ወጣቶች በሥርዓት አልበኝነት ድርጊት ውስጥ የሚሳተፉበትን ምክንያት እስቲ በጥልቀት እንመርምር። ብዙ ወጣቶች ግራ የተጋቡ ከመሆናቸውም በላይ “በእነሱ አመለካከት ዓለም የተመሰቃቀለችና በእብዶች የተሞላች የእብደት ቦታ ነች።” ሆኖም ብዙዎች ከሚያስቡት በተለየ አንድ ዘገባ እንዲህ ብሏል:- “በአሥራዎቹ የእድሜ ክልል የሚገኙ ልጆች ሕይወታቸው ወዴት እያመራ እንዳለ ስለማያውቁ ይጨነቃሉ። እነዚህ ልጆች አዋቂዎች ከሚገምቱት በላይ የዓለም ጉዳይ ያሳስባቸዋል።” አውቆም ይሁን ሳያውቅ ሥርዓት አልበኛ የሚሆን ወጣት ሥር የሰደደ ጭንቀቱን፣ መፍትሄ ያላገኙ ችግሮቹን ወይም ያልተሟሉ ፍላጎቶቹን በዚህ መንገድ ለመግለጽ ይሞክር ይሆናል። በመግቢያው ላይ በተጠቀሰው ጥናት መሠረት “ለጥያቄው መልስ ከሰጡት ውስጥ አንዳቸውም ቢሆኑ፣ ሌላው ቀርቶ ከሥርዓት ውጪ የሆኑ ድርጊቶችን የሚፈጽሙትም ጭምር ሥርዓት አልበኝነትን በመደገፍ አልተከራከሩም ወይም ተገቢ አስመስለው ለማቅረብ አልሞከሩም።”

አንድ ወጣት አልፎ አልፎ የአድናቆት ወይም የማበረታቻ ቃላትን ይሰማ ይሆናል። የትምህርት አስፈላጊነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመሄዱና አብዛኛው የሥራ መስክ ደግሞ የላቀ እውቀትን ወይም ሙያዊ ችሎታን የሚጠይቅ በመሆኑ እሷ ወይም እሱ ፍርሃት ይሰማቸው ይሆናል። ከዚህም በላይ ወላጆች፣ መምህራን ወይም እኩዮች ነቃፊዎችና ብዙ የሚጠብቁ በመሆን እሱ ወይም እሷ ላላቸው ስብዕና ሳይሆን ለወጣቱ ስኬት ከፍተኛ ግምት የሚሰጡ ሊሆኑ ይችላሉ። ብዙዎች የሚያምፁት ወይም ሥርዓት አልበኞች የሚሆኑት በራሳቸው ስለሚናደዱ ነው። ታዲያ የወላጆች ፍቅርና ክትትል እንዲህ ያለውን ውጥረት በእጅጉ ሊቀንሰው አይችልም?

አንዳንድ ባለ ሥልጣናት በተለያዩ ነገሮች ላይ መጻፍንና ሌሎች ዓይነት የጥፋት ድርጊቶችን ለመቆጣጠር የሚያደርጉትን ጥረት ችላ ያሉት ቢመስልም ሁኔታው ያሳሰባቸው ሰዎች አሁንም ቢሆን መምህራንና የትምህርት ቤት ባለ ሥልጣናት ሥርዓት አልበኝነትን እንዲቆጣጠሩላቸው ይጠብቃሉ። የሕግ ተፈጻሚነትን አስመልክቶ ዘ ዎርልድ ቡክ ኢንሳይክለፒዲያ እንዲህ ይላል:- “ሥርዓት አልበኝነት በገንዘብ ወይም በእስራት ያስቀጣል። አንዳንድ መንግሥታት ልጆች ለሚፈጽሙት የሥርዓት አልበኝነት ድርጊት ወላጆቻቸው በኃላፊነት እንዲጠየቁ የሚያደርጉ ሕጎች አሏቸው። ሆኖም አብዛኞቹ የሥርዓት አልበኝነት ድርጊቶች በሕግ የሚያስቀጡ አይደሉም። እንደነዚህ ባሉ ሁኔታዎች ላይ ሕግን ተግባራዊ ማድረግ አስቸጋሪ ነው፤ በግለሰብ ደረጃ የሚፈጸሙ የጥፋት ድርጊቶች የሚያስወጡት ወጪ ደግሞ ሕጋዊ እርምጃ ለመውሰድ የሚያስችል አይደለም።” አንድ ዘገባ እንዳሳየው ከአጥፊዎቹ መካከል የሚያዙት 3 በመቶ የሚሆኑት ብቻ ናቸው።

እንዲህ ዓይነቱን ጥፋተኝነት ከሥረ መሠረቱ ለመዋጋት ከሁሉ የተሻለው መንገድ ተገቢ የሆነ የወላጅ ቁጥጥር ማድረግ ነው በሚለው ሐሳብ ትስማማ ይሆናል። ሆኖም የቤተሰብ ሕይወት ሲፈራርስ ኅብረተሰቡ ይቸገራል። በብራዚል ሳኦ ፓውሎ ዩኒቨርሲቲ የሚገኙት ፕሮፌሰር አና ሉኤዛ ቪዬራ ዲ ማቶስ የወጣቶች ችግር አንዳንድ መንስኤዎች “የወላጅ ቁጥጥር ማነስ፣ የደንብ አለመኖር፣ የሐሳብ ግንኙነት አለመኖር፣ ችላ መባልና ግዴለሽነት” መሆናቸውን ተናግረዋል።

ኢየሱስ “ከዓመፃም ብዛት የተነሣ የብዙ ሰዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች” ሲል የተናገራቸው ቃላት በዚህ በጊዜያችን በትክክል ሲፈጸሙ ተመልክተናል። (ማቴዎስ 24:​12) ደግሞስ በ2 ጢሞቴዎስ 3:​1-4 ላይ ተመዝግበው የሚገኙት ቃላት እውነት መሆናቸውን የሚክድ ማን ነው? ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ። ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና፣ ገንዘብን የሚወዱ፣ ትምክህተኞች፣ ትዕቢተኞች፣ ተሳዳቢዎች፣ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፣ የማያመሰግኑ፣ ቅድስና የሌላቸው፣ ፍቅር የሌላቸው፣ ዕርቅን የማይሰሙ፣ ሐሜተኞች፣ ራሳቸውን የማይገዙ፣ ጨካኞች፣ መልካም የሆነውን የማይወዱ፣ ከዳተኞች፣ ችኩሎች፣ በትዕቢት የተነፉ፣ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ።” እንዲህ ዓይነት ባህርይ ባላቸው ሰዎች መካከል መኖሩ ብቻ እንኳ ለሥርዓት አልበኝነት አስተዋጽኦ ያደርጋል። ሆኖም እጃችንን ልንሰጥ አይገባም። በአጠቃላይ ሲታይ ማኅበረሰቦች ሥርዓት አልበኝነትን ማስወገድ ተስኗቸዋል፤ ይሁንና በግለሰብ ደረጃ የራሳቸውን የአኗኗር ዘይቤ በመለወጥ ባለጌ ወይም ግዴለሽ መሆናቸውን እርግፍ አድርገው የተዉ ሰዎች አሉ። በእነሱ ሁኔታ ላይ ሥርዓት አልበኝነት እንዲቆም ተደርጓል።

ለወጣቶች የሚሆን ግሩም መመሪያ

ሥርዓት አልበኛ የነበሩም ሆኑ ሌሎች ባሕርያቸውን እንዲቀይሩ የረዳቸው ምንድን ነው? አንዳንድ መምህራንና ወላጆች ባይዋጥላቸውም መጽሐፍ ቅዱስ ግሩምና ወቅታዊ መመሪያ ይሰጣል። መመሪያውን በመከተል ቀደም ሲል ሥርዓት አልበኛ የነበሩ ሰዎች “ክፉውን ለማድረግ ብዙ ሰዎችን አትከተል” የሚለውን ቀጥተኛ የአምላክ ሕግ ለመታዘዝ ተገፋፍተዋል። (ዘጸአት 23:​2) ብዙዎች ቀደም ሲል ስለማይገነዘቧቸው እምነቶችና መሠረተ ትምህርቶች በሚናገረው በአምላክ ቃል ውስጥ በሚገኘው እውነት የተሳቡ ሲሆን የተማሩትም ነገር በጎ ተጽእኖ አሳድሮባቸዋል። በሳኦ ፓውሎ የሚገኘውን ጆሴ የተባለውን ወጣት ተመልከት። ያደገው ምስሎችን ለአምልኮ መጠቀም አስፈላጊ መሆኑን እንዲያምን ተደርጎ ነበር። ጆሴ የአምላክ ስም ይሖዋ እንደሆነና በምስል ማምለክን ደግሞ እንደሚቃወም ሲያውቅ አምላክን ለማስደሰት ሲል ለውጦችን አደረገ።​—⁠ዘጸአት 20:​4, 5፤ መዝሙር 83:​18፤ 1 ዮሐንስ 5:​21፤ ራእይ 4:​11

ኔልሰን በዓመፀኛ ቡድኖችና አድማዎች በመካፈል ሕይወቱ በአሳዛኝ ገጠመኞች የተሞላ ከሚሆን ይልቅ ለወደፊቱ የሚሆን እርግጠኛ ተስፋ ያገኘ ሲሆን ይህ ደግሞ ትልቅ እፎይታ ሰጥቶታል። እንዲህ ይላል:- “በመጥፎ ጓደኝነትና በዕፅ ሱሰኝነት ምክንያት በቤተሰቦቼ ዘንድ እጠላ የነበርኩ ቢሆንም አሁን ግን በቤት ውስጥ ከፍተኛ አክብሮት የሚሰጠኝ ሰው ለመሆን ችያለሁ። ብዙውን ጊዜ አባቴ ታላላቅ ወንድሞቼን እንድመክራቸው ይጠይቀኛል። ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ከጀመርኩበት ጊዜ አንስቶ ሕይወቴ ዓላማ ያለው ስለሆነ ደስተኛ ሆኛለሁ።” እንዲሁም በዓመፅ በተሞላ አካባቢ ይኖር ለነበረ እንደ ማርኮ ላለ የከተማ ወጣት የአምላክ መንግሥት ምድርን ወደ ገነትነት እንደሚለውጣት ማወቅ በጣም የሚያስደስት ነገር ነበር።​—⁠ራእይ 21:​3, 4

በተጨማሪም ቀደም ሲል የዱሪዬዎች ቡድን አባል፣ የመንገድ ላይ ተደባዳቢና ሥርዓት አልበኛ የነበረውን ሰው ሁኔታ ተመልከት። የሙት ልጅ የነበረው ቫልተር አሳዛኝ የልጅነት ሕይወት ያሳለፈ ሲሆን በዚህ በተበላሸና ክፉ በሆነ ሥርዓት ውስጥ አምላክ ሕዝቦች እንዳሉት በማወቁ ተደስቶ ነበር። ርኅራኄ፣ አሳቢነትና ደግነት በማሳየት የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች ተግባራዊ ለማድረግ ከልባቸው ይጥራሉ። ቫልተር እንዲህ በማለት ያብራራል:- “ኢየሱስ ቃል በገባው መሠረት አሁን ‘ወንድሞች፣ እህቶች፣ እናቶችና አባቶች’ ያሉት ትልቅ ቤተሰብ አለኝ። ወደፊት በአምላክ የጽድቅ አገዛዝ ሥር ሰዎች በደስታና በአንድነት የሚኖሩበትን ጊዜ በጉጉት እጠባበቃለሁ።”​—⁠ማርቆስ 10:​29, 30፤ መዝሙር 37:​10, 11, 29

ከተቃውሞ የተሻለ ነገር

ቀደም ሲል ሥርዓት አልበኛ የነበሩት እነዚህ ሰዎች ለሰው አሳቢነትና ፍቅር ከማሳየት በተጨማሪ ‘ክፋትን መጥላት’ ተምረዋል። (መዝሙር 97:​10፤ ማቴዎስ 7:​12) አንተስ? እጅግ የተስፋፋው ሥርዓት አልበኝነት በሚያስከትለው ችግር እየተሰቃየህ ቢሆንም እንኳ የአምላክን ቃል ማጥናትህ ይሖዋ ሕያው፣ አሳቢና አፍቃሪ ሰማያዊ አባት መሆኑን እንድትገነዘብ ያደርግሃል። (1 ጴጥሮስ 5:​6, 7) የግል ድክመት ወይም ድህነት ቢኖርብህ እንኳ አምላክ በመንፈሳዊ እንድታድግ ሊረዳህ ይችላል። ይህ ደግሞ በራሱ አስደናቂ የሆነ ተሞክሮ ነው!

ይሖዋና ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉም ዓይነት ሰዎች የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት የመማር አጋጣሚ እንዲያገኙ ይፈልጋሉ። የአምላክ ቃል በአሁኑ ጊዜ ግለሰቦች ሥርዓት አልበኛ መሆናቸውን እንዲተዉ መርዳት ብቻ ሳይሆን መለኮታዊ የሆኑ መሠረታዊ ሥርዓቶችን ተግባራዊ በማድረግ ተጨማሪ እድገት እንዲያደርጉ ሊያነሳሳቸው ይችላል። በውጤቱም በንጽሕናውና በጥሩ ሥነ ምግባሩ የሚታወቀው ዓለም አቀፍ የወንድማማች ማኅበር አባላት ይሆናሉ፤ ይህም በዓለም ዙሪያ የሚገኘው የይሖዋ ምሥክሮች ጉባኤ ነው። በኤፌሶን 4:​24 ላይ ተመዝግቦ ከሚገኘው ሐሳብ ጋር በመስማማት እነዚህ ቅን ክርስቲያኖች “ለእውነትም በሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው [ለብሰዋል]።” በሕይወት ተርፈው ለዘላለም የሚኖሩት እነሱ ብቻ ስለሚሆኑ በቅርቡ ዓለማችን እነዚህን በመሳሰሉ ሰዎች የተሞላ ይሆናል።​—⁠ከሉቃስ 23:​43 ጋር አወዳድር።

ከሥርዓት አልበኝነት ነፃ የሆነ አዲስ ዓለም በእርግጥ ይመጣል

ሥርዓት አልበኝነት ሊወገድ ይችላል ብለህ በእርግጥ ታምናለህ? የሚቻል ከሆነ ይህን የመሰለው ሥር ነቀል ለውጥ እንዴት ሊመጣ ይችላል? የአምላክ መንግሥት በቅርቡ ይህን ክፉ ሥርዓት ያጠፋል። ምድርን የሚወርሱ ሰዎች የአምላክን የጽድቅ ሕጎች ሆን ብለው የሚጥሱ ከሆነ በዝምታ አይታለፉም። (ከኢሳይያስ 24:​5, 6 ጋር አወዳድር።) ‘በደለኞች በአንድነት ሲጠፉ’ ጽድቅን የሚወድዱ ይድናሉ። “እግዚአብሔር ይረዳቸዋል፣ ያድናቸዋልም፣ ከኃጢአተኞችም እጅ ያወጣቸዋል፣ ያድናቸዋልም፣ በእርሱ ታምነዋልና።”​—⁠መዝሙር 37:​38-40

ሥርዓት አልበኝነት ሙሉ በሙሉ ተጠራርጎ እንደሚጠፋ የተረጋገጠ ነው። እንዲሁም ወንጀል፣ ጭቆና፣ ሥቃይና ክፋት በሙሉ ይጠፋሉ። በአንፃሩ ደግሞ በአዲሱ ዓለም ውስጥ የሚኖረው ሕይወት ሰላም፣ እውነተኛ ጽድቅ፣ ጸጥታና ደኅንነት የሰፈነበት ይሆናል። ኢሳይያስ 32:​18 ቃል በቃል የሚፈጸመውን ነገር እንደሚከተለው በማለት ይገልጻል:- “ሕዝቤም በሰላም ማደሪያ በታመነም ቤት በጸጥተኛ ማረፊያ ይቀመጣል።” አዎን፣ ውብና ዓለም አቀፋዊ የሆነች ገነት አንዳቸው ለሌላው ፍቅርና አሳቢነት በሚያሳዩ ሰዎች የተሞላች ትሆናለች።

ቀደም ሲል ሥርዓት አልበኞች የነበሩ ሰዎች በሚልዮን ከሚቆጠሩ ሌሎች ሰዎች ጋር አንድ ላይ በመሆን ከይሖዋ አምላክ ጋር የጠበቀ ዝምድና ሊኖራቸው ችሏል። ከሥርዓት አልበኝነት ድርጊቶች ጋር ምንም ንክኪ የላቸውም። አንተስ አምላክ በቃሉ አማካኝነት በአዲስ ዓለም ውስጥ ወደሚኖረው ሕይወት እንዲመራህ ትፈቅድለታለህ? “አስተምርሃለሁ በምትሄድበትም መንገድ እመራሃለሁ፤ ዓይኖቼን በአንተ ላይ አጠናለሁ” በማለት ይሖዋ የተናገራቸውን ቃላት የመዘገበውን የጥንቱን መዝሙራዊ ልትኮርጅ ትችላለህ።​—⁠መዝሙር 32:​8

[በገጽ 7 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ወላጃዊ ክትትልና ፍቅር ወጣቶችን ይጠብቃል