በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይሖዋ የሚያስባችሁ እንዴት ነው?

ይሖዋ የሚያስባችሁ እንዴት ነው?

ይሖዋ የሚያስባችሁ እንዴት ነው?

‘አምላኬ ሆይ፣ አስበኝ።’ ነህምያ እንዲህ ሲል በተደጋጋሚ ለአምላክ ልመና አቅ​ርቧል። (ነህምያ 5:​19፤ 13:​14, 31) ሰዎች በአስጨናቂ ሁኔታ ሥር ሲሆኑ ይህን በመሰለ የልመና ቃል አምላክን መማጸናቸው የተለመደ ነገር ነው።

ይሁን እንጂ ሰዎች አምላክ እንዲያስባቸው ሲጠይቁ ምን ማለታቸው ነው? አምላክ ስማቸውን ከማስታወስ የበለጠ ነገር እንዲያደርግላቸው እንደሚጠብቁ ግልጽ ነው። ከኢየሱስ አጠገብ ተሰቅለው ከነበሩት ወንጀለኞች አንዱ የነበረው ዓይነት ተስፋ እንደሚኖራቸው ምንም አያጠራጥርም። ይህ ሰው ከሌላው ወንጀለኛ በተለየ መንገድ ኢየሱስን “በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ” ሲል ተማጽኖታል። ኢየሱስ ማንነቱን እንዲያስታውስለት ብቻ ሳይሆን አንድ ነገር እንዲያደርግለት ማለትም ከሞት እንዲያስነሳው ፈልጎ ነበር።​—⁠ሉቃስ 23:​42

አምላክም አንድን ሰው ‘ሲያስብ’ አዎንታዊ እርምጃ እንደሚወስድ መጽሐፍ ቅዱስ በብዙ ቦታዎች ላይ ይገልጻል። ለምሳሌ ያህል ምድር ለ150 ቀናት በውኃ ከተጥለቀለቀች በኋላ “እግዚአብሔርም ኖኅን . . . አሰበ፤ እግዚአብሔርም በምድር ላይ ነፋስን አሳለፈ፣ ውኃውም ጎደለ።” (ዘፍጥረት 8:​1) ይህ ከሆነ ከብዙ መቶ ዓመታት በኋላ ሳምሶን ፍልስጥኤማውያን ዓይኖቹን አውጥተውና በሰንሰለት አስረውት በነበረበት ጊዜ “አምላክ ሆይ፣ እባክህ፣ አስበኝ፤ አምላክ ሆይ፣ ይህን አንድ ጊዜ ብቻ፣ እባክህ አበርታኝ” ሲል ጸልዮአል። ሳምሶን የአምላክን ጠላቶች መበቀል እንዲችል ይሖዋ ከተለመደው የሰው አቅም በላይ የሆነ ጥንካሬ በመስጠት አስቦታል። (መሳፍንት 16:​28-30) ለነህምያ ደግሞ ይሖዋ ጥረቱን ባርኮለት በኢየሩሳሌም እውነተኛው አምልኮ ዳግም ተቋቁሟል።

ሐዋርያው ጳውሎስ “በመጽናትና መጻሕፍት በሚሰጡት መጽናናት ተስፋ ይሆንልን ዘንድ አስቀድሞ የተጻፈው ሁሉ ለትምህርታችን ተጽፎአል” ብሏል። (ሮሜ 15:​4) ጥንት የነበሩት የአምላክ አገልጋዮች እንዳደረጉት ሁሉ ፈቃዱን ለማድረግ በመፈለግ ይሖዋን ካሰብን በየዕለቱ የሚያስፈልጉንን ነገሮች እንድናገኝ በመርዳት፣ ፈተናዎች ሲያጋጥሙን በመደገፍ እንዲሁም ለአምላክ አክብሮት በሌላቸው ሰዎች ላይ ቅጣት ሲያወርድ እኛን በማዳን ይሖዋ እንደሚያስበን ትምክህት ሊኖረን ይችላል።​—⁠ማቴዎስ 6:​33፤ 2 ጴጥሮስ 2:​9