በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ማስጠንቀቂያውን ልብ በሉ!

ማስጠንቀቂያውን ልብ በሉ!

ማስጠንቀቂያውን ልብ በሉ!

ሰኔ 3, 1991 በጃፓን ፉገን ተራራ ላይ ድንገት ኃይለኛ የፍንዳታ ድምፅ ከተሰማ በኋላ ከተራራው ከፍተኛ የእሳተ ገሞራ ጋዝና አመድ እየተትጎለጎለ መውጣት ጀመረ። ይህ እንደ እቶን እሳት የሚፋጅ ቅላጭ ከተራራው እየወረደ አካባቢውን አጥለቀለቀው። በዚህ ፍንዳታ 43 ሰዎች ሕይወታቸውን አጥተዋል። ለጥቂት ከሞት የተረፉትም ቢሆኑ ክፉኛ ተቃጥለዋል። አንዳንዶቹ “ውኃ፣ ውኃ” እያሉ ይጮኹ ነበር። የእሳት አደጋ ሠራተኞችና ፖሊሶች የተጎዱትን ሰዎች ለመርዳት ከፍተኛ ርብርቦሽ አድርገዋል።

ተራራው አናት ላይ ትፍ ቅላጭ ድንጋይ ሲወጣ መታየት የጀመረው ከሁለት ሳምንት በፊት ነበር። ስለዚህ የአካባቢው ባለ ሥልጣናትም ሆኑ ነዋሪዎች አደጋ እየመጣ እንዳለ በግልጽ ያዩ ነበር። አደጋው ከመድረሱ አንድ ሳምንት ከሚበልጥ ጊዜ በፊት አካባቢውን ለቅቀው እንዲወጡ ማሳሰቢያ ተሰጥቶ ነበር። እሳተ ገሞራው ከመፈንዳቱ ልክ ከአንድ ቀን በፊት ፖሊስ የዜና ዘጋቢዎች ወደ አካባቢው ከመቅረብ እንዲቆጠቡ አሳስቦ ነበር። ሆኖም የአደጋው ሰለባ የሆኑት 43 ሰዎች በዚያን ዕለት ከሰዓት በኋላ በአደጋው ቀጣና ውስጥ ነበሩ።

እነዚህ ሁሉ ሰዎች ወደዚያ አካባቢ እንዲሄዱ ያደፋፈራቸው ወይም እዚያ አካባቢ እንዲቆዩ ያደረጋቸው ምንድን ነው? ከአካባቢው ሸሽተው የነበሩ አንዳንድ ገበሬዎች ንብረታቸውንና እርሻቸውን አየት አድርገው ለመመለስ ሲሉ እንደገና ወደዚያ ስፍራ ሄደዋል። ሦስት የእሳተ ገሞራ አጥኚዎች ደግሞ ለማወቅ ካላቸው ጉጉት የተነሳ ወደ እሳተ ገሞራው በጣም ለመቅረብ ሞክረው ነበር። በርካታ ሪፖርተሮችና ፎቶግራፍ አንሺዎች የእሳተ ገሞራ ፍንዳታውን በቅርብ ለመከታተል ሲሉ የአደጋ ቀጣናውን አልፈው እስከ መሄድና በጣም እስከ መቅረብ ተዳፍረው ነበር። ጋዜጠኞቹን ይዘው የመጡ ሦስት የታክሲ ሹፌሮችም በቦታው ነበሩ። ፖሊሶችና የእሳት አደጋ ሠራተኞች ደግሞ ግዳጃቸውን በመወጣት ላይ ነበሩ። የአደጋ ቀጣናውን አልፈው የሄዱት ሁሉ የየራሳቸው ምክንያቶች ነበሯቸው፤ ዳሩ ምን ያደርጋል ሁሉም ሕይወታቸውን አጡ።

አንተስ በአደጋ ቀጣና ውስጥ ነህን?

ሁላችንም አስጊ እሳተ ገሞራ ባለበት አካባቢ አንኖር ይሆናል። ይሁን እንጂ መላውን ዓለም በሚያካልልና ሁላችንም በአደጋ ቀጣና ውስጥ እንድንሆን የሚያደርግ አንድ ዓለም አቀፍ ጥፋት ከፊታችን ቢደቀን ምን እናደርጋለን? የአስተማማኝ ትንቢታዊ መልእክት ምንጭ መሆኑን ያስመሰከረው አንድ መጽሐፍ ዓለም አቀፍ ጥፋት በመምጣት ላይ መሆኑን በመግለጽ ማስጠንቀቂያ ይሰጠናል። ይህን ጥፋት እንደሚከተለው በማለት ይገልጸዋል:- “ፀሐይ ይጨልማል፣ ጨረቃም ብርሃንዋን አትሰጥም፣ ከዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ፣ የሰማያትም ኃይላት ይናወጣሉ። . . . በዚያን ጊዜም የምድር ወገኖች ሁሉ ዋይ ዋይ ይላሉ።” (ማቴዎስ 24:​29, 30) ጽንፈ ዓለማዊ ይዘት ያላቸው የሰማይ አካላት ‘በምድር ወገኖች ሁሉ’ ላይ ተጽዕኖ እንደሚያሳድሩ ተገልጿል። በሌላ አነጋገር ይህ ትንቢት እያንዳንዳችንን ሊነካ ስለሚችል ጥፋት የሚገልጽ ነው።

ይህ የአስተማማኝ ትንቢት ምንጭ የሆነው መጽሐፍ፣ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። ደስ የሚለው ግን ከላይ በተጠቀሰው ጥቅስ ዙሪያ ያለው ሐሳብ ከዚህ ዓለም አቀፍ ጥፋት በፊት ያሉ ቅድመ ሁኔታዎችን በዝርዝር ይገልጻል። ትፍ ቅላጭ ድንጋይና ሌሎች የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ ጠቋሚ ሁኔታዎች መታየታቸው የሺማባራ ከተማ ባለሥልጣናት የአደጋ ቀጣና እንዲከልሉ እንዳደረጓቸው ሁሉ መጽሐፍ ቅዱስም ንቁዎች እንድንሆንና ከአደጋው ለመትረፍ ራሳችንን እንድናዘጋጅ የሚያደርጉ ሁኔታዎችን ይገልጽልናል። በፉገን ተራራ ከደረሰው አሳዛኝ ሁኔታ ትምህርት ልናገኝና ከፊታችን የሚጠብቀን ጥፋት ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ማስተዋል እንችላለን።

[በገጽ 2 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]

ሽፋን፦ Yomiuri/​Orion Press/​Sipa Press

[በገጽ 3 ላይ የሚገኝ የሥዕል ሥዕል]

Yomiuri/Orion Press/Sipa Press